كيفية صلاة النبي - صلى الله عليه وسلم -
የነቢዩ ﷺ ሰላት አሰጋገድ
የነቢዩ ﷺ ሰላት አሰጋገድ
የተከበሩ ሸይኽ
ዐብዱልዐዚዝ ቢን ዐብደላህ ቢን ባዝ
በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩህሩህ በጣም አዛኝ በሆነው
ምስጋና ሁሉ ለብቸኛው አላህ የተገባ ነው። የአላህ ሰላትና ሰላም የአላህ ባሪያ፣ መልክተኛና የኛ ነቢይ በሆኑት በሙሐመድ፣ በቤተሰቦቻቸውና በተከታዮቻቸውም ላይ ይስፈን፤ በመቀጠል፦
ይህች አጠር ያለች መልዕክት የነቢዩን (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈን) ሰላት አሰጋገድ የምታብራራ ሲሆን ለማዘጋጀት የፈለግኩትም ይህንን መልዕክት ያነበበ ሙስሊም ወንድና ሴት ሁሉ የርሳቸውን አሰጋገድ አርዓያነት ተከትሎ ለመስገድ እንዲጥር ነው። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈን) እንዲህ ስላሉ ነው፦ "እኔ ስሰግድ እንዳያችሁኝ አድርጋችሁ ስገዱ።" [1] ለአንባቢዎችም ይህንን የርሳቸውን አሰጋገድ በዚህ መልኩ አብራራለሁ:- () ቡኻሪ በቁጥር (605) ዘግበውታል።
1 - ዉዱእን አዳርሶ (አሳምሮ) ያድርግ: ይህም ውዱኡን አላህ ባዘዘው መልኩ ማድረጉ ነው። ጥራት የተገባውና የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል: {እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ወደ ሶላት በቆማችሁ (ለመቆም ባሰባችሁ) ጊዜ ፊቶቻችሁን፣ እጆቻችሁንም እስከ ክርኖች እጠቡ፡፡ ራሶቻችሁንም (በውሃ) አብሱ፡፡ እግሮቻችሁንም እስከ ቁርጭምጭሚቶች (እጠቡ)።} ([2]) [አልማኢዳ: 6] እስከ አንቀፁ መጨረሻ ድረስ ...
ነቢዩም (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፦ (ያለ ዉዱእ የተሰገደ ሰላት ተቀባይነት የለውም።) ([3]) () ሙስሊም በቁጥር (224) ላይ ዘግበውታል።
ሰላቱን አበላሽቶ ለሰገደው ሰውዬም የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ማለታቸው፦ (ወደ ሰላት የቆምክ (ሰላት መስገድ በፈልግክ) ጊዜ ዉዱእህን አሟልተህ አድርግ።) ([4]) () ቡኻሪ በቁጥር (5782) ዘግበውታል።
2 - ሰጋጁ ሊሰግደው ያሰበው ሰላት ግዴታም ይሁን ሱና ሰላቱን እንደሚሰግደው በልቡ አስቦ (ነይቶ)፤ የትም ስፍራ ቢሆን በሙሉ አካሉ ወደ ቂብላ ይዙር። ቂብላ የሚባለው ከዕባ ነው። ኒያን በምላሱ አይናገር። ኒያን በምላስ መናገር ያልተደነገገ ተግባር ነውና። እንደውም ነቢዩም (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሆኑ ባልደረቦቻው (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) ኒያን በምላሳቸው ስላልተናገሩ ኒያን መናገር አዲስ ፈጠራ ቢድዓ ነው። ሰጋጁ ኢማም (መሪ) ወይም ብቻውን የሚሰግድ ከሆነ ከፊት ለፊቱ ሱትራ (መከለያ) ያድርግ። በኢስላም ሊቃውንት ድርሳናት (መጽሐፍት) በግልፅ ተለይተው በተቀመጡ አንዳንድ አጋጣሚዎች ካልሆነ በቀር ወደ ቂብላ ዞሮ መስገድ የሶላት መስፈርት ነው።
3 - በዓይኑ ሱጁድ የሚያደርግበትን ስፍራ እየተመለከተ "አላሁ አክበር" (ትርጉሙ፡ አላህ ታላቅ ነው) በማለት የመክፈቻን ተክቢራ ይበል።
4 - ተክቢራ በሚል ወቅት ሁለት እጆቹን የትከሻው ትይዩ ድረስ ወይም የጆሮዎቹ ጫፍ ድረስ ያንሳቸው።
5 - ሁለት እጆቹን ደረቱ ላይ ያኑር፤ ቀኝ እጁን የግራ እጁ መዳፉ ጀርባ ላይ ወይም የእጁ አንጓ ወይም ክንዱ ላይ ያድርግ። ይህም ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለተረጋገጠ ነው።
6 - የመክፈቻን ዱዓ መቅራት ይወደዳል (ሱና) ነው። እርሱም: "አልላሁምመ ባዒድ በይኒ ወበይነ ኸጣያየ ከማ ባዐድተ በይነል-መሽሪቂ ወል-መግሪቢ አልላሁምመ ነቂኒ ሚነል ኸጣያ ከማ ዩነቀ-ሥ-ሠውቡል አብየዱ ሚነ ደነስ አልላሁምመግሲል ኸጣያየ ቢልማኢ ወሥ-ሠልጂ ወል-በረድ" ትርጉሙም፦ "አላህ ሆይ! በምሥራቅና በምዕራብ መካከል እንዳራራቅከው እኔንም ከወንጀሌ አርቀኝ፤ አላህ ሆይ! ነጭ ልብስ ከቆሻሻዎች እንደሚጸዳው እኔንም ከወንጀሌ አጥራኝ፤ አላህ ሆይ! እኔን ከወንጀሌ በውሃ እና በጤዛ በበረዶም እጠበኝ።" ([5]) [4] (ቡኻሪ በቁጥር (744) እና ሙስሊም በቁጥር (598) ዘግበውታል)
ከፈለገም ይህን በማለት ፈንታ ተከታዩን ይበል: (ሱብሓነከ አልላሁምመ ወቢሐምዲከ፤ ወተባረከ ኢስሙከ፤ ወተዓላ ጀዱከ፤ ወላኢላሃ ገይሩከ) ((ትርጉሙም: አላህ ሆይ! ጥራት ከምስጋና ጋር ላንተ የተገባ ነው፤ ስምህ የተባረከ ነው፤ ግርማህም ከፍ ያለ ነው፤ ካንተ በቀር በእውነት አምልኮ የሚገባው የለም።)) ([6]) ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) የተረጋገጡ የሆኑን ከዚህ ውጪ ያሉ የመክፈቻ ዱዓዎችን ቢልም ችግር የለውም። በላጩ ግን የርሳቸውን ፈለግ በተሟላ መልኩ ከመከተል አኳያ አንዳንዴ ይህንን ሌላ ጊዜ ደግሞ ሌላውን ማለቱ ነው። ቀጥሎም "አዑዙ ቢልላሂ ሚነሽሸይጧኒ ረጂም" "ቢስሚላሂ አርረሕማኒ አርረሒም" ይበልና የፋቲሓን ምዕራፍ ይቅራ። ይህም የአላህ መልክተኛ እንዲህ ስላሉ ነው፦ "የመጽሐፉን መክፈቻ (ፋቲሓን) ያልቀራ ሰው ሰላት የለውም።" ([7]) ፋቲሓን እንዳጠናቀቀም ድምፅ ከፍ በሚደረግባቸው ሰላቶች ከሆነ ድምፁን ከፍ በማድረግ፤ ድምፁን ዝግ በሚደረግባቸው ሰላቶች ካነበበ ደግሞ ድምፁን ዝግ በማድረግ - አሚን - ይበል። ከፋቲሓ ቀጥሎ ከቁርአን የገራለትን ይቅራ። በላጩ ግን በዝሁር፣ በዐስርና በዒሻእ ሶላት ከፋቲሓ ቀጥሎ መካከለኛ መለያ ያላቸውን ምዕራፍ (አውሷጢል ሙፈሶል) መቅራት፤ በፈጅር ሶላት ደግሞ ረጃጅም መለያ ያላቸውን (ጡዋሊል ሙፈሶል) ምዕራፎች መቅራት፤ በመግሪብ ሶላት ደግሞ አንዳንዴ በአጫጭሮቹ አንዳንዴም ከረጃጅሞቹ ምዕራፎች መቅራት ነው። ይህም ይህን በማስመልከት በመጡ ሐዲሦች አሟልቶ ለመተግበር ነው። () ሙስሊም በቁጥር (399) ዘግበውታል። () ቡኻሪ በቁጥር (756) ዘግበውታል።
7 - እጆቹን በትከሻዎቹ ወይም በጆሮዎቹ ትይዩ ከፍ አድርጎ ተክቢራ በማድረግ ያጎንብስ (ሩኩዕ ያድርግ)። የሩኩዕ አደራረጉም ጭንቅላቱን በወገቡ ትይዩ ቀጥ በማድረግ፣ ጣቶቹን ከፋፍቶ እጆቹ ጉልበቱ ላይ በማድረግ ነው። ሩኩዑ በሚያደርግበት ጊዜ ይረጋጋና "ሱብሓነ ረቢየል ዐዚም" (ትርጉሙ፡ ታላቅ የሆነው ጌታዬ ጥራት ተገባው) ይበል። በላጩ ሶስት ጊዜ ወይም ከዛ በላይ መደጋገሙ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ተከታዩንም ቢል ይወደድለታል: (ሱብሓነከ አልላሁምመ ወቢሐምዲከ፣ አልላሁምመግፊር ሊ) ([8]) ትርጉሙም (አላህ ሆይ! ከምስጋና ጋር ጥራት ይገባህ። አላህ ሆይ! ይቅር በለኝ።) () ቡኻሪ በቁጥር (817) እና ሙስሊም በቁጥር (484) ዘግበውታል።
8 - እጆቹን በትከሻዎቹ ወይም በጆሮዎቹ ትይዩ ከፍ በማድረግ ጭንቅላቱን ከሩኩዕ ቀና እያደረገ እንዲህ ይበል፦ (ሰሚዐሏሁ ሊመን ሐሚደህ) ትርጉሙም (አላህ ያመሰገነውን ሰሚ ነው።) ማለት ነው። ኢማም ወይም ብቻውን የሚሰግድ ከሆነ ከቆመ በኋላ እንዲህ ይበል: (ረብበና ወለከል ሐምዱ ሐምደን ከሢረን ጠዪበን ሙባረከን ፊህ፤ ሚልአ'ስሰማዋቲ ወሚልአል አርዲ ወሚልአ ማሺእተ ሚን ሸይኢን በዕዱ) ([9]) ትርጉሙም (ጌታችን ሆይ! ምስጋና ላንተ የተገባ ነው። ላንተ የበዛ፣ ምርጥ የሆነ፣ የተባረከ፣ ሰማያትን የሞላ ምድርንም የሞላና ከዚህም ሁሉ ኃላ ከነገሮች ሁሉ አንተ የፈለግከውን የሞላ ምስጋና የተገባህ ነህ።) ማለት ነው። () ቡኻሪ በቁጥር (711) እና ሙስሊም በቁጥር (598) ዘግበውታል።
ተከታይ ከሆነ ግን ቀና በሚልበት ወቅት (ሰሚዐሏሁ ሊመን ሐሚደህ) የሚለውን ትቶ "ረብበና ወለከል ሐምዱ ..." የሚለውን ቀደም ብሎ እስከተጠቀሰው እስከመጨረሻው ድረስ ይላል። እያንዳንዱ ሰጋጅ ማለትም ኢማሙም፣ ተከታዩም ሆነ ብቻውን የሚሰግደው ይህንንም ቢጨምር: (አህለሥ-ሠናኢ ወልመጅዲ፣ አሐቁ ማቃለል ዐብዱ ወኩሉና ለከ ዐብዱን አልሏሁምመ ላማኒዐ ሊማ አዕጠይተ፣ ወላ ሙዕጢየ ሊማ መነዕተ፣ ወላ የንፈዑ ዘልጀዲ ሚንከል ጀድ) ([10]) ትርጉሙም (የውደሳና የልቅና ባለቤት ነህ። ሁላችንም ላንተ ባሪያዎች ከመሆናችንም ጋር ባሪያው ከተናገራቸው እጅግ ተገቢው ንግግር "አላህ ሆይ! አንተ ለሰጠኸው ከልካይ የለውም። አንተ ለከለከልከውም ሰጪ የለውም። የልቅና ባለቤትም ልቅናው አይጠቅመውም፤ ልቅናም ካንተው ነው።) ማለት ነው። ከአላህ መልክተኛ የተረጋገጠ ስለሆነ ጥሩ ነው። () ሙስሊም በቁጥር (477) ዘግበውታል።
እያንዳንዱ ሰጋጅ ማለትም ኢማሙም፣ ተከታዩም ሆነ ብቻውን የሚሰግደው ልክ ከሩኩዕ በፊት ሲቆም እንዳደረገው እጆቹን ደረቱ ላይ ማኖሩ ይወደድለታል። ይህም በዋኢል ቢን ሑጅርና በሰህል ቢን ሰዕድ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) ሐዲሥ ይህንን የሚጠቁም ማስረጃ ስለተረጋገጠ ነው።
9 - ከቻለ መሬት ላይ ከእጆቹ በፊት ጉልበቱን እያስቀመጠ ተክቢራ አድርጎ ሱጁድ ይውረድ። ይህን ካልቻለ ግን ሱጁድ ሲወርድ የእጆቹን ጣቶች አጣብቆና ዘርግቶ የእግሮቹን ጣቶችና እጆቹን ወደ ቂብላ አዙሮ ይውረድ። ሱጁድ የሚወረደው በሰባት አካላት ነው: እነርሱም: አፍንጫውን ጨምሮ ግንባሩ፣ ሁለት እጆቹ፣ ሁለት ጉልበቶቹ እና የሁለቱ የእግር ጣቶች የውስጠኛቸው ክፍሎች ናቸው። እንዲህም ይበል፦ (ሱብሓነ ረቢየል አዕላ) ይበል። ትርጉሙም: (ከፍ ያልከው ጌታዬ ሆይ! ጥራት ይገባህ።) ማለት ነው። ይህንንም ሶስት ጊዜ ወይም ከዛ በላይ ማለት ሱና ነው። ይህንን ከማለቱም ጋር ተከታዩንም ቢጨምር ይወደድለታል: (ሱብሓነከ አልላሁምመ ረበና ወቢሐምዲከ፣ አልላሁምመግፊርሊ) ትርጉሙም (ጌታችን አላህ ሆይ! ከምስጋና ጋር ጥራት ይገባህ። አላህ ሆይ! ማረኝ።) ማለት ነው። ዱዓም ያብዛ ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: (በሩኩዕ ላይ ስትሆኑ ጌታን አልቁት፤ በሱጁድ ስትሆኑ ግን በዱዓእ ተበራቱ ዱዓችሁ ተቀባይነት የማግኘት እድሉ ሰፊ ነውና።) ([11]) () ሙስሊም በቁጥር (479) ዘግበውታል።
ጌታውንም የዱንያም (ምድራዊ) ይሁን የአኺራ (የመጪውንም ዓለም) መልካም ነገርን ይጠይቅ። ይህንንም መፈፀም ሰላቱ ግዴታም ሆነ ሱና ይወደዳል። ጡንቻዎቹን ከጎኖቹ፣ ሆዱን ከታፋዎቹ፣ ታፋዎቹን ከባቶቹ ያራርቅ። ክንዶቹንም ከመሬት ከፍ ያድርግ። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: (ሱጁድ ላይ ተስተካከሉ። አንዳችሁ ሱጁድ ላይ ክንዱን እንደ ውሻ አይዘርጋ።) ([12]) () ቡኻሪ በቁጥር (788) እና ሙስሊም በቁጥር (493) ዘግበውታል።
10 - ተክቢራ በማለት ጭንቅላቱን ያንሳ። ግራ እግሩን አንጥፎ ይቀመጥበት። ቀኝ እግሩን ደግሞ ይትከለው (ቀጥ ያድርገው)። እጆቹንም በታፋዎቹና ጉልበቶቹ ላይ በማኖር እንዲህ ይበል: (ረብቢግፊርሊ ወርሐምኒ ወህዲኒ ወርዙቅኒ ወዐፊኒ ወጅቡርኒ) ([13]) ትርጉሙም (ጌታዬ ሆይ! ማረኝ፣ እዘንልኝ፣ ምራኝ፣ ሲሳይን ለግሰኝ፣ ጤናዬን ስጠኝ፣ ጠግነኝ።) ማለት ነው። ሲቀመጥም ተረጋግቶ ይቀመጥ። () ቲርሚዚይ በቁጥር (284)፣ አቡዳውድ በቁጥር (850) እና ኢብኑ ማጃህ በቁጥር (898) ዘግበውታል።
11 - ሁለተኛውን ሱጁድ ተክቢራ በማድረግ ይውረድ። በመጀመሪያው ሱጁድ ላይ ያደረገውን አምሳያም በድጋሚ ያድርግ።
12 - ተክቢራ በማድረግ ጭንቅላቱን ቀና ያድርግ። በሁለቱ ሱጁዶች መካከል የተቀመጠውን ያህል ትንሽን ጊዜ ይቀመጥ። ይህም ጀልሰተል ኢስቲራሓ (የእረፍት መቀመጥ) ተብሎ ይጠራል። ይህንን ማድረጉም የሚወደድ ነው። ቢተወውም ችግር የለውም። በዚህ ወቅትም የሚለው ምንም አይነት ዱዓም ሆነ ዚክር የለም። ቀጥሎ ከቻለ ሁለቱ ጉልበቶቹን ተደግፎ ወደ ሁለተኛው ረከዓ ለመቆም ይንቀሳቀሳል። ጉልበቱን ተደግፎ መነሳት ካልቻለ መሬቱን ተደግፎ ይነሳል። ቀጥሎ ፋቲሓንና ከፋቲሓ በኋላ የገራለትን ምዕራፍ ይቀራል። ቀጥሎም በመጀመሪያው ረከዐ የፈፀማቸውን ተግባራት አምሳያ ይፈፅማል።
13 - የሚሰግደው ሰላት እንደ ፈጅር፣ ጁሙዓ እና የዒድ ሶላት የመሳሰሉ ባለ ሁለት ረከዓ ሰላቶች ከሆነ ከሁለተኛው ረከዓ ሁለተኛው ሱጁድ ከተነሳ በኋላ ቀኝ እግሩን በመትከልና (ቀጥ በማድረግና) ግራ እግሩን በማነጠፍ ይቀመጣል። ቀኝ እጁንም ከመጠቆሚያ ጣቱ በቀር ያሉትን ሁሉንም ጣቶቹን በመጨበጥ በቀኝ ታፋው ላይ ያኖራል። በመጠቆሚያ ጣቱም የአላህን አሃዳዊነትን ለመግለፅ ይጠቁምባታል። ትንሿ ጣቱንና የቀለበት ጣቱን በመጨበጥ በአውራ ጣቱና በመሃል ጣቱ ክብ በመስራት በመጠቆሚያ ጣቱ ቢጠቁምም ጥሩ ነው። ሁለቱም አይነት የመጠቆም አፈፃፀሞች ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) መፈፀማቸው ተረጋግጠዋልና። አንዳንዴ አንዱን አንዳንዴ ሌላኛውን መፈፀሙ በላጭ ነው። ግራ እጁን በግራ ታፋውና ጉልበቱ ላይ ያኑር። ቀጥሎ እዛው በዚህ መልኩ እንደተቀመጠ ተሸሁድ ይበል። "ተሸሁድ" የሚባለውም፦ “አት‐ተሒያቱ ሊላሂ ወስ‐ሶላዋቱ ወጥ‐ጠይ‐ዪባቱ፣ አስ‐ሰላሙ ዐለይከ አይዩሀን-ነቢይዩ ወረሕመቱልላሂ ወበረካቱሁ፤ አስሰላሙ ዐለይና ወዐላ ዒባዲላሂ አስሷሊሒነ፣ አሽሀዱ አንላኢላሀ ኢልለልላህ ወአሽሀዱ አንነ ሙሐመደን ዐብዱሁ ወረሱሉሁ።” “ትርጉሙም: ክብርና ልዕልና እንዲሁም ሶላቶችና መልካም ነገሮች ሁሉ ለአላህ ናቸው። አንቱ ነቢዩ ሆይ! የአላህ ሰላም፣ እዝነቱና በረከቶች በእርሶ ላይ ይስፈን፤ ሰላም በእኛና በአላህ ደጋግ ባሮችም ላይ ይስፈን፤ ከአላህ ሌላ በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ እመሰክራለሁ፤ ሙሐመድም የአላህ ባርያና መልዕክተኛው መሆናቸውንም እመሰክራለሁ።” ማለት ነው። ቀጥሎም እንዲህ ይበል: "አልላሁመ ሰሊ ዐላ ሙሐመድ ወዐላ አሊ ሙሐመድ ከማ ሰለይተ ዐላ ኢብራሂም ወዐላ አሊ ኢብራሂም ኢንነከ ሐሚዱን መጂድ ወባሪክ ዐላ ሙሐመድ ወዐላ አሊ ሙሐመድ ከማ ባረክተ ዐላ ኢብራሂም ወዐላ አሊ ኢብራሂም ኢንነከ ሐሚዱን መጂድ" ([14]) ትርጉሙም፡ (አላህ ሆይ! በኢብራሂምና በቤተሰቦቻቸው ላይ ውዳሴህን እንዳወረድክ ሁሉ በሙሐመድና በቤተሰቦቻቸው ላይም ውዳሴህን አውርድ፤ አንተ ምስጉንና የላቅክ አምላክ ነህና። አላህ ሆይ! በኢብራሂምና በቤተሰቦቻቸው ላይ በረከትህን እንዳሰፈንክ ሁሉ በሙሐመድና በቤተሰቦቻቸው ላይም በረከትህን አዉርድ። አንተ ምስጉንና የላቅክ አምላክ ነህና።) ማለት ነው። () ቡኻሪ በቁጥር (797)፣ ሙስሊም በቁጥር (402) ዘግበውታል።
ከአራት ነገሮችም እንዲህ በማለት በአላህ ይጠበቅ: "አልላሁምመ ኢንኒ አዑዙ ቢከ ሚን ዐዛቢ ጀሀነም፡ ወሚን ዐዛቢል ቀብር፡ ወሚን ፊትነቲል መሕያ ወልመማት፡ ወሚን ሸርሪ ፊትነቲል መሲሒ ደጃል" ([15]) ትርጉሙም: (አሏህ ሆይ! እኔ ከጀሀነም ቅጣት፤ ከቀብር ቅጣትም፤ ከህይወትም ከሞትም ፈተና እንዲሁም ከመጥፎው የመሲሑ ደጃል ፈተናም ባንተው እጠበቃለሁ።) ማለት ነው። () ቡኻሪ በቁጥር (1311)፣ ሙስሊም በቁጥር (588) ዘግበውታል።
ቀጥሎ ከአለማዊም ሆነ አኺራዊ መልካም ነገሮች የፈለገውን ዱዓ ያድርግ። ለወላጆቹ ወይም ከነርሱ ውጪ ላሉ ሙስሊሞች ዱዓ ቢያደርግም ችግር የለውም። ይህን ሁሉ መፈፀሙ ተወዳጅ የሚሆንለትም በግዴታም ሆነ በሱና ሶላት ነው። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ለኢብኑ መስዑድ (አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና) ተሸሁድን ባስተማሩት ሐዲሥ ውስጥ በሁሉም ሰላቶች ላይ እንዲፈፅም በሚጠቁም መልኩ: (ከዛም የሚያስደስተውን ዱዓ በመምረጥ ዱዓ ያድርግ።) ([16]) ስላሉ ነው። በሌላ ዘገባም: (ከዚያም የሻውን ዱዓ መርጦ ያድርግ።) ([17]) ብለዋል። () ነሳኢይ በቁጥር (1298) ዘግበውታል። () ሙስሊም በቁጥር (402) ዘግበውታል።
ይህም አንድ ሰው በዱንያም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ለማግኘት የሚያደርገውን (ዱዓ) ሁሉ እንደሚያጠቃልል (የሚያመለክት) ነው። ቀጥሎ ወደቀኙና ወደግራው እየዞረ "አስሰላሙ ዐለይኩም ወረሕመቱሏሂ" እያለ ያሰላምታል።
14 - የሚሰግደው ሶላት እንደ መግሪብ ባለ ሶስት ረከዓ ሰላት ከሆነ ወይም እንደ ዝሁር፣ ዐስርና ዒሻእ ባለ አራት ረከዓ ሶላት ከሆነ (ከሁለተኛው ረከዓ ሁለተኛው ሱጁድ ከተነሳ በኋላ) ቀደም ብሎ የተጠቀሰውን ተሸሁድ እና በነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ላይ ሰላዋት ያወርዳል፤ ቀጥሎም ጉልበቶቹን ተደግፎ "አላሁ አክበር" በማለት (ለሶስተኛ ረከዓ) ይቆማል። እንደቆመም እጆቹን በትከሻዎቹ ወይም በጆሮዎቹ ትይዩ ከፍ ካደረጋቸው በኃላ መልሶ ቀደም ተብሎ በተጠቀሰው መልኩ ደረቱ ላይ ያኖራቸዋል። ፋቲሓንም ብቻ ይቀራል። አንዳንድ ጊዜ በዝሁር ሶላት በሶስተኛውና አራተኛው ረከዓ ላይ ከፋቲሓ በተጨማሪ ሌላ ምዕራፍ ቢቀራ አቡ ሰዒድ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ይህንን የሚጠቁም መረጃ ስለተገኘ (ስለተረጋገጠ) ችግር የለውም። ከመጀመሪያው ተሸሁድ በኋላ በነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ላይ ውዳሴ ማውረድን ቢተው የተወው ግዴታ ሳይሆን ተወዳጅ ነገር ስለሆነ ችግር የለውም። ቀጥሎ መግሪብ ሶላት ከሆነ የሚሰግደው ከሶስተኛው ረከዓ ሁለተኛው ሱጁድ በኋላ ዝሁር፣ ዐስር ወይም ዒሻ ሶላት ከሆነ ደግሞ የሚሰግደው ከአራተኛው ረከዓ ሁለተኛ ሱጁድ በኋላ ቀደም ተብሎ ባለ ሁለት ረከዓ ሲሰግድ በተጠቀሰው መልኩ ተሸሁድን ይበልና ወደ ቀኙ እና ወደ ግራው በመዞር ያሰላምት። ሶስት ጊዜም እስቲግፋር ይበል። ቀጥሎም እንዲህ ይበል: "አልላሁምመ አንተስ-ሰላም ወሚንከስ-ሰላም ተባረክተ ያ ዘል-ጀላሊ ወል-ኢክራም" ([18]) (ትርጉሙም፡ አላህ ሆይ! አንተ "አስ-ሰላም" ነህ። ሰላምም ከአንተው ነው የሚመጣው። የልዕልና የልግስና ባለቤት የሆንከው ጌታዬ ሆይ! የበላይነትህም እጅግ ከፍ ያለ ነው።) ኢማም ከሆነ ይህንን የሚለው ወደ ሰዎች ከመዞሩ በፊት ነው። ቀጥሎ ሰውነቱን ወደ ሰዎች ካዞረ በኋላ እንዲህ ይበል: - "ላ ኢላሀ ኢለላህ ወሕደሁ ላ ሸሪከ ለሁ፡ ለሁል-ሙልኩ ወለሁል-ሐምዱ ወሁወ ዐላ ኩሊ ሸይኢን ቀዲር፤ ላ ሐውላ ወላ ቁወተ ኢላ ቢላህ፤ አልላሁምመ ላ ማኒዐ ሊማ አዕጠይተ፣ ወላ ሙዕጢየ ሊማ መነዕተ፤ ወላ የንፈዑ ዘልጀዲ ሚንከልጀዱ፤ ላ ኢላሀ ኢለሏህ ወላ ነዕቡዱ ኢላ ኢያህ ለሁን-ኒዕመቱ ወለሁል-ፈድሉ ወለሁሥ-ሠናኡል ሐሰን ላ ኢላሀ ኢለላህ ሙኽሊሲነ ለሁድ-ዲን ወለው ከሪሀል-ካፊሩን" ([19]) (ትርጉሙም፡ ከአላህ በስተቀር በእውነት አምልኮ የሚገባው አምላክ የለም፤ አጋር የለውም። ንግሥናም ምስጋናም የእርሱ ብቻ ነው። እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው። በአላህ ካልሆነ በስተቀር ብልሃትም ሆነ ሃይል የለም። አላህ ሆይ! አንተ ለሰጠኸው ከልካይ የለውም። አንተ ለከለከልከው ሰጪ የለውም። የልቅና ባለቤት ልቅናው አይጠቅመውም። ልቅናም ካንተ ነው። ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ የለም። ከርሱም ሌላ አንገዛም። ፀጋው የርሱ ብቻ ነው። ችሮታውም የርሱ ብቻ ነው። መልካም ውዳሴም የሚገባው ለእርሱ ብቻ ነው። ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ የለም። ከሓዲዎች ቢጠሉም (እኛ) ሃይማኖታችንን ለርሱ ያጠራን ነን።) ማለት ነው። () ሙስሊም በቁጥር (591) ዘግበውታል። () ሙስሊም በቁጥር (402) ዘግበውታል።
ሰላሳ ሶስት ጊዜ ተስቢሕ (ሱብሓነሏህ/ ለአላህ ጥራት ተገባው)፣ ተሕሚድም እንደዛው (አልሐምዱሊላህ/ ምስጋና ሁሉ ለአላህ ተገባው)፣ ተክቢርም እንደዛው (አላሁ አክበር/ አላህ ታላቅ ነው) ይበል። መቶ መሙያውንም: (ላ ኢላሀ ኢለላህ ወሕደሁ ላ ሸሪከ ለሁ፡ ለሁል-ሙልኩ ወለሁል-ሐምዱ ወሁወ ዐላ ኩሊ ሸይኢን ቀዲር) ይበል። አየቱል ኩርሲይን፣ ቁልሁወሏሁ አሐድን፣ ቁል አዑዙ ቢረቢል ፈለቅን፣ ቁል አዑዙ ቢረቢንናስን ከሁሉም ሶላት በኋላ ይቅራ። እነዚህን ሶስቱን ምዕራፎች ከፈጅር እና መግሪብ ሶላት በኋላ ሶስት ሶስት ጊዜ ደጋግሞ መቅራት እንደሚወደድ የሚጠቁሙ ሐዲሦች ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለመጡ ይወደዳል። እነዚህን ሁሉ ዚክሮች ማለት ግዴታ ሳይሆን ሱና (ተወዳጅ ተግባር) ነው።
ሁሉም ሙስሊም ወንድና ሴት ከዝሁር ሶላት በፊት አራት ረከዓ ከዝሁር ሶላት በኋላ ሁለት ረከዓ፣ ከመግሪብ ሶላት በኋላ ሁለት ረከዓ፣ ከዒሻ ሶላት በኋላ ሁለት ረከዓ፣ ከፈጅር ሶላት በፊት ሁለት ረከዓ መስገዱ የተደነገገ ተወዳጅ ተግባር ነው። የነዚህ አጠቃላይ የረከዓ ቁጥርም አስራ ሁለት ነው። እነዚህ ረከዓዎች ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጉዞ ላይ ሳይሆን ሀገራቸው ባሉበት ወቅት ዘውትር ይሰግዷቸው ስለነበር "ረዋቲብ" በመባል ይጠራሉ። ጉዞ ላይ በሚሆኑበት ወቅት ግን ከፈጅር በፊት ከሚሰገደውን ሁለት ረከዓና ከዊትር ውጪ ያሉትን ሱና ሶላቶችን ይተዉዋቸው ነበር። እነዚህን ግን ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሀገር ቤትም ይሁን ጉዞ ላይ እያሉ ዘውትር ይሰግዷቸው ነበር። እነዚህን ረዋቲብ ሱናዎች እና ዊትርን ቤት ውስጥ መስገድ በላጭ ነው። መስጂድ ውስጥ ቢሰግዳቸውም ግን ችግር የለውም። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: (ከግዴታ ሶላት ውጪ የሰውዬው በላጩ ሶላት ቤት ውስጥ የሚሰግደው ሶላት ነው።) ([20]) () ቡኻሪ በቁጥር (6860) ዘግበውታል።
እነዚህን የረዋቲብ ረከዓዎች ዘውትር መስገድ ጀነት ከሚያስገቡ ምክንያቶች መካከል አንዱ ነው። ይህንንም በማስመልከት ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: (በቀኑና በምሽቱ ክፍለ ጊዜ ውስጥ አስራ ሁለት ረከዓዎችን የሰገደ ሰው ጀነት ውስጥ በነርሱ ምክንያት ለርሱ ቤት ይገነባለታል።) ([21]) () ሙስሊም በቁጥር (728) ዘግበውታል።
ከዐስር በፊት አራት ረከዓ፣ ከመግሪብ በፊት ሁለት ረከዓ፣ ከዒሻ በፊት ሁለት ረከዓ ቢሰግድም መልካም ነው። ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ይህንን መፈፀማቸውን የሚጠቁም ሐዲሥ ተረጋግጧልና። ከዝሁር በፊትም በኋላም አራት ረከዓ ቢሰግድም መልካም ነው። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: (ከዝሁር በፊት አራት ረከዓዎች ላይና ከዝሁር በኋላ አራት ረከዓዎች ላይ የተጠባበቀ (የሰገደ) ሰው አላህ እሳትን በርሱ ላይ እርም አድርጎለታል።) ([22]) ማለትም ከረዋቲቡ ሱና ሶላቶች ላይ ሁለት ረከዓ ከዝሁር በኋላ ይጨምር ማለት ነው። ምክንያቱም ከረዋቲብ ሱና መካከል ከዝሁር በፊት አራት ረከዓና ከዝሁር በኋላ ሁለት ረከዓ መስገድ ነው። ከዝሁር በኋላ ከሚሰግደው ላይ ሁለት ረከዓን ቢጨምር በኡሙ ሐቢባ (አላህ መልካም ስራዋን ይውደድላትና) ሐዲሥ የተጠቀሰውንም ምንዳ ያገኛል ማለት ነው። () አሕመድ በቁጥር (25547)፣ ቲርሚዚይ በቁጥር (393) እና አቡዳውድ በቁጥር (1077) ዘግበውታል።
ለመልካም የመገጠም ባለቤቱ አላህ ነው። የአላህ ሶላትና ሰላም በነቢያችን ሙሐመድ ቢን ዐብዲላህ፣ በቤተሰቦቻቸውና ባልደረቦቻቸው እንዲሁም እስከፍርዱ ቀን በመልካም በተከተሏቸው ላይ ሁሉ ይስፈን።