آداب السفر وأحكامه
የጉዞ ስነስርዓትና ህግጋቶቹ ምስጋና የአለማት ጌታ ለሆነው አላህ የተገባ ነው። ሶላትና ሰላም በነብያችን ሙሐመድ፣ በቤተሰቦቻቸውና በባልደረቦቻቸውም ላይ ሁሉ ይስፈን።
የጉዞ ስነስርዓትና ህግጋቶቹ ምስጋና የአለማት ጌታ ለሆነው አላህ የተገባ ነው። ሶላትና ሰላም በነብያችን ሙሐመድ፣ በቤተሰቦቻቸውና በባልደረቦቻቸውም ላይ ሁሉ ይስፈን።
በመቀጠልም፦
ይህ የጉዞ ስነስርዓትና ህግጋትን በተመለከተ የሚያትት አጠር ያለ መልዕክት ነው። አንድ ተጓዥ አብዛኛው ጊዜ የሚያስፈልጉትን ጉዳዮች ለማብራራትም ጥረት አድርገናል።
አላህን ብቻ ለተከበረው ፊቱ ጥርት ተደርጎ የተዘጋጀ እንዲያደርግልንና ለመላው ሙስሊሙ ማህበረሰብ ጠቃሚ እንዲያደርግልን እንጠይቀዋለን።
የእስላማዊ አስተምህሮቶችን በተለያዩ ቋንቋዎች አገልግሎት ማህበር የዕውቀት ዘርፍ ኮሚቴ
የመጀመሪያው: የጉዞ ስነስርዓት
ሐጅ ለማድረግ ወይም ለሌላ አምልኮዎች ጉዞ የሚያደርግ ሰው የሚከተሉት ነጥቦች ላይ ትኩረት ሊያደርግ ይገባል:
1 - የሐጅና ዑምራ ጉዞዎች ቅዱስ ጉዞዎች ስለመሆናቸው ምንም ጥርጥር የሌለው ጉዳይ ቢሆንም ስለሚሄድበት ወቅት፣ መጓጓዣ፣ ስለሚያካሂደው ጓደኛ፣ ወዳሰበው ቦታ የሚወስዱ በርካታ መንገዶች ካሉ ስለሚሄድበት የመንገድ አቅጣጫ (ሰግዶ) የላቀውን አላህን ያማክር። የእውቀትና የመልካም ባለቤት የሆኑን ሰዎችንም በዚህ ጉዳይ ያማክር። አላህን የሚያማክርበት ሁኔታ አፈፃፀሙም: ሁለት ረከዓ ይሰግዳል ቀጥሎ ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) የመጣውን ዱዓ ያደርጋል።
2 - ሐጅና ዑምራ የሚያደርግ ሰው በሐጁና በዑምራው የላቀውን የአላህን ፊት ማሰቡና ወደርሱ መቃረብን ማሰቡ ግዴታ ነው። እንዲሁም የዱንያን ስባሪ ጥቅም ከማሰብ ወይም ፉከራን ከማሰብ ወይም (ሐጅ እገሌ መባልን የመሰለ) ቅጥያ ስም ማግኘትን ከማሰብ ወይም ይዩልኝና ይስሙልኝን ከማሰብ መጠንቀቅ ይገባዋል። ይህ ስራው እንዲበላሽና ተቀባይነት እንዲያጣ ከሚያደርጉ ምክንያቶች መካከል አንዱ ነውና። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል: {«እኔ አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው ማለት ወደኔ የሚወረድልኝ ቢጤያችሁ ሰው ብቻ ነኝ፡፡ የጌታውንም መገናኘት የሚፈልግ ሰው፤ መልካም ሥራን ይሥራ፡፡ በጌታውም መገዛት አንድንም አያጋራ» በላቸው፡፡} [አልከህፍ:110] በሐዲሠል ቁድሲይም እንደተላለፈው: ("እኔ በሽርክና ከመጋራት ከተብቃቁ ሁሉ እጅግ የተብቃቃሁ ነኝ። አንድን ሥራ ሠርቶ በውስጡ ከእኔ ጋር ሌላን አካል ያጋራ እንደሆነ እርሱንም ሆነ የሽርክ ተግባሩን እተወዋለሁ።") [1] (1) ሙስሊም በቁጥር (2985) ዘግበውታል
3 - የሐጅና ዑምራን ጉዞ የሚጓዝ ሰው መፈፀሙ ግዴታ የሆነበትን ነገር እንዳይተው ወይም ክልክል የሆነበትን ነገር እንዳይፈፅም ከመጓዙ በፊት የዑምራና የሐጅን ህግጋትንና የጉዞ ህግጋትን መገንዘብ ይገባዋል። ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: (አላህ መልካም ለሻለት ሰው ሃይማኖቱን ያስገነዝበዋል።) [2] [2] ቡኻሪ በቁጥር (3116) እና ሙስሊም በቁጥር (100) ዘግበውታል
4 - የሐጅ ወይም የዑምራ ጉዞ የሚያደርግ ሰው ለሐጁና ዑምራው ሐላል የሆነ ገንዘብን መምረጥ አለበት። ምክንያቱም አላህ መልካም ነው ከመልካም ውጪም አይቀበልም። በተጨማሪም ሐራም የሆነ ገንዘብ የዱዓን ተቀባይነት የሚያሳጣ አንዱ ምክንያት ነውና።
5 - ከሁሉም ወንጀሎችና ሐጢዓቶች ተውበት ማድረግ፤ ገንዘብ ነክም ይሁን ክብር ነክ ወይም ከዛ ውጪ ባሉ ጉዳዮች ሰዎች ላይ የሰራው ግፍ ካለ መመለስና ይቅርታቸውን መጠየቅ ይኖርበታል።
6 - አንድ ጉዞ የሚወጣ ሰው፤ ሰው ዘንድ ያለውንም ሰው ላይ ያለበትንም ኑዛዜውን መጻፉ ይወደድለታል። ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: (የሚናዘዘው ነገር ያለው ማንኛውም ሙስሊም፤ ኑዛዜውን በጽሑፍ አዘጋጅቶ እርሱ ዘንድ ሳያስቀምጥ ሁለት ሌሊት እንኳ ማደር ተገቢ አይደለም።) [3] ኑዛዜውንም በሰዎች ያስመስክር፤ በርሱ ላይ ያሉበትን እዳዎችንም ይክፈል፤ እርሱ ዘንድ የተቀመጡ አደራዎችንም ወይ ለባለቤቶቻቸው ይመልስ ወይም ደሞ እርሱ ዘንድ እንዲቆይ ያስፈቅዳቸው። (3) ቡኻሪ በቁጥር (2738) እና ሙስሊም በቁጥር (1627) ዘግበውታል
7 - አንድ ጉዞ የሚወጣ ሰው ለጉዞው መልካም ጓደኛ መምረጡ ይወደድለታል። የሚመርጠው ጓደኛ የሸሪዓ ዕውቀት ፈላጊ እንዲሆን ጥረት ያድርግ። ይህም ጉዞው ላይ፣ ሐጁ ላይና ዑምራው ላይ ለስህተት እንዳይጋለጥና መልካሙን እንዲገጠም ከሚያደርጉት ምክንያቶች መካከል አንዱ ነው። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: (ሰውዬው በጓደኛው ሃይማኖት ላይ ነውና እያንዳንዳችሁ የሚጎዳኘውን ሰው ይመልከት።) [4] ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህም ብለዋል: (ከአማኝ በቀር አትጎዳኝ፤ አላህን ከሚፈራ ሰው በቀር ምግብህን አይብላ።) [5] [8] አቡ ዳውድ በቁጥር (4833) ዘግበውታል [5] አቡ ዳውድ በቁጥር (4832) ቲርሚዚይም በቁጥር (2395) ዘግበውታል
8 - ተጓዥ የሆነ ሰው ቤተሰቡን፣ ቅርብ ዘመዶቹን፣ ጎረቤቶቹንና ባልደረቦቹን መሰናበት ይወደድለታል። ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: «ጉዞ መውጣት የፈለገ ሰው ትቷቸው ለሚሄዳቸው እንዲህ ይበል: "አስተውዲዑኩሙሏህ አለዚ ላዩዲዑ ወዳኢዐሁ"» [ትርጉሙም: እናንተን (እንዲጠብቃችሁ) አደራውን ለማያጠፋው አላህ አደራ እሰጠዋለሁ።] [6] ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ባልደረቦች መካከል አንዱ ጉዞ መውጣት በፈለገ ጊዜም እርሳቸው እንዲህ በማለት ይሰናበቱት ነበር: «አስተውዲዑሏሃ ዲነክ ወአማነተክ ወኸዋቲመ ዐመሊክ» (ትርጉሙም: ሃይማኖትህን፣ እምነትህንና የስራህን ፍፃሜ ለአላህ አደራ እሰጠዋለሁ።) [7] ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጉዞ ከሚወጡ ሰዎች መካከል ከርሳቸው ምክር ፈልጎ ለሚመጣ ሰው እንዲህ ይሉ ነበር: «ዘወደከሏሁ ተቅዋ ወገፈረ ዘንበክ ወየሰረ ለከ አል‐ኸይረ ሐይሡ ማኩንተ» (ትርጉሙም: አላህ ፍራቻውን ያስሰንቅህ፤ ወንጀልህንም ይማርልህ፤ የትም ሆነህ መልካምን ያግራልህ።) [8] አንድ ጉዞ መውጣት የፈለገ ሰውዬ ወደ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በመምጣት "የአላህ መልክተኛ ሆይ! ምከሩኝ" አለ፤ እርሳቸውም: ("አላህን በመፍራትና በየሁሉም ከፍታ ላይ ስትወጣ ተክቢራ (አላሁ አክበር) እንድትል እመክርሃለሁ።" አሉት። በሄደም ጊዜ "አላህ ሆይ! መሬትን ሰብስብለት (አሳጥርለት) ጉዞውንም አቅልልለት" አሉ።) [9] [6] ጦበራኒይ በቁጥር (823) ዘግበውታል [7] ኢማሙ አሕመድ በሙስነዳቸው በቁጥር (4524) ዘግበውታል [8] ቲርሚዚይ በቁጥር (3444) ዘግበውታል [7] ኢማሙ አሕመድ በሙስነዳቸው በቁጥር (9724) ዘግበውታል
9 - ጉዞ ሲወጣ ከራሱ ጋር ቃጭል፣ የሙዚቃ መሳሪያዎችና ውሻ አብሮ አይያዝ። ይህም አቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ የአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: (መላእክቶች ውሻም ይሁን ቃጭል ያለበትን ጉዞ አይጎዳኙም።) [10] (10) ሙስሊም በቁጥር (2113) ዘግበውታል
10 - ከአንድ በላይ ሚስቶች ኑረውት ለጉዞ አንዷን ብቻ ይዞ መውጣት ከፈለገ በመካከላቸው እጣ ይጥላል። እጣው የደረሳት ማንኛዋም ሚስቱ አብራው ወደ ጉዞው ትሄዳለች። ይህም ዓኢሻህ (አላህ መልካም ስራዋን ይውደድላትና) እንዲህ ስላለች ነው: «የአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጉዞ መውጣት የፈለጉ ጊዜ በባለቤቶቻቸው መካከል እጣ ይጥሉ ነበር። እጣ የደረሳት ማንኛዋም ባለቤታቸው ከርሳቸው ጋር አብራ ለጉዞ ትወጣ ነበር።» [11] (11) ቡኻሪ በቁጥር (2593) እና ሙስሊም በቁጥር (2770) ዘግበውታል
11 - ከተቻለ ለጉዞ የሚወጣው ሀሙስ እለት በቀኑ መጀመሪያ ላይ ቢሆን ይወደድለታል። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለፈፀሙት ነው። ከዕብ ቢን ማሊክ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ አሉ: «የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከሐሙስ ቀን በስተቀር በሌላ ቀን ለጉዞ እምብዛም አይወጡም ነበር።» [12] (12) ቡኻሪ በቁጥር (2949) ዘግበውታል
12 - ለጉዞም ይሁን ከዛ ውጪ ወደ ሆነ ቦታ ሲወጣ ከቤት ሲወጣ የሚባለውን ዱዓ ማድረጉ ይወደድለታል: ሲወጣ እንዲህ ይላል: (ቢስሚላሂ ተወከልቱ ዐለላሂ፤ ወላ ሐውለ ወላቁወተ ኢላ ቢላህ፤ አልላሁመ ኢንኒ አዑዙ ቢከ አን አዲለ አው ኡደለ አው አዚለ አው ኡዘለ አው አዝሊመ አው ኡዝለመ አው አጅሀለ አው ዩጅሀለ ዐለየ) ትርጉሙም (በአላህ ስም በአላህ ላይ ተመክቼ እወጣለሁ። ኃይልም ይሁን ብልሃት በአላህ ፈቃድ ካልሆነ በቀር የለም። አላህ ሆይ! እኔ ከመጥመም ወይም ከማጥመም ወይም ወንጀል ላይ ከመውደቅ ወይም ሌላን ወንጀል ላይ ከመጣል ወይም ከመበደል ወይም ከመብበደል ወይም የመሃይማን ስራ ከመስራት ወይም የመሃይማን ስራ እኔ ላይ ከሚሰራብኝ ባንተ እጠበቃለሁ።) ማለት ነው። [13] [13] አቡ ዳውድ በቁጥር (5094) ዘግበውታል
13 - እንስሳውን ወይም መኪናውን ወይም ፕሌኑን ወይም ከዛ ውጪ ባሉ መሳፈሪያዎች ላይ ሲሳፈር እንዲህ ብሎ የጉዞን ዱዓ ማድረጉም ይወደድለታል: "አላሁ አክበር አላሁ አክበር አላሁ አክበር ከዚያም እንዲህ ይበል: {ሱብሓነልለዚ ሰኽኸረ ለና ሀዛ ወማ ኩና ለሁ ሙቅሪኒን ወኢና ኢላ ረቢና ለሙንቀሊቡን} [አዝዙኽሩፍ:14] አልላሁመ ኢንና ነስአሉከ ፊ ሰፈሪና ሀዛ አልቢርረ ወትተቅዋ፣ ወሚነል ዐመሊ ማ ተርዷ፣ አልላሁመ ሀውዊን ዐለይና ሰፈረና ሀዛ፣ ወጥዊ ዓና ቡዕደሁ፣ አልላሁምመ አንተስ -ሷሒቡ ፊ ሰፈር፣ ወልኸሊፈቱ ፊልአህል፣ አልላሁምመ ኢንኒ አዑዙ ቢከ ሚን ወዕሣኢ [14] ሰፈር፣ ወከኣበቲል መንዘር [15]፣ ወሱኢል ሙንቀለብ[16] ፊልማሊ ወልአህል ..." [17] (ትርጉሙም: አላህ ታላቅ ነው። አላህ ታላቅ ነው። አላህ ታላቅ ነው። እኛ የማንችለው ሆነን ሳለ ይህንን ለኛ ያገራልን ጌታ ጥራት ይገባው። እኛም ወደ ጌታችን ተመላሾች ነን። አላህ ሆይ! እኛ በዚህ ጉዟችን በጎን ነገርና ፍራቻን፣ ከስራም የምትወደውን እንጠይቅሃለን። አላህ ሆይ ይህንን ጉዟችንን አቅልልልን፣ ርቀቱንም ሰብስብልን። አላህ ሆይ! እኛን በጉዟችን የምትጎዳኘን፣ በቤተሰቦቻችን ጉዳይም የምትተካን አንተው ነህ። አላህ ሆይ! እኔ ከጉዞ መከራ፣ መጥፎ በሆነ ገፅታ ከመታየትና ወደ ቤተሰቦቼና ንብረቶቼ መጥፎ አመላለስን ከመመለስ በአንተ እጠበቃለሁ።) ማለት ነው። [14] ወዕሣኢ-ስ-ሰፈር ማለት: የጉዞ መከራ ማለት ነው። አልኢፍሷሕ ዐን መዓኒ ሲሓሕ (4/284) [15] ("ከአበቲል መንዘር" የተባለው): መጥፎ ገፅታ፣ በሀዘን የተጎሳቀለ ማንነት ማለት ነው። አልኢፍሷሕ ዐን መዓኒ ሲሓሕ (4/284) [16] (አልሙንቀለብ) ማለት መመለስ ማለት ነው። አልኢፍሷሕ ዐን መዓኒ ሲሓሕ (4/284) [17] ኢማሙ አሕመድ በሙስነዳቸው በቁጥር (6374 ዘግበውታል
14 - ያለ ጓደኛ ብቻውን ባይጓዝ ይመረጣል። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: «ሰዎች በብቸኝነት ውስጥ ያለውን (ጉዳት) እኔ የማውቀውን ያህል ቢያውቁ ኖሮ፣ ማንም ጋላቢ በሌሊት ብቻውን አይጓዝም ነበር።» [18] (18) ቡኻሪ በቁጥር (2998) ዘግበውታል
15. ተጓዦች ከመካከላቸው አንዱን መሪያቸው አድርገው ይሹሙ፤ ይህም አንድነታቸውን ይበልጥ የሚሰበስብ፣ ለስምምነት ይበልጥ የሚያመች፣ እንዲሁም ዓላማቸውን ለማሳካት የሚያጠናክር በመሆኑ ነው። ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: (ሶስት ሰዎች ለጉዞ ከወጡ አንዱን መሪያቸው ያድርጉ!) [19] [19] አቡ ዳውድ በቁጥር (2608) ዘግበውታል
16 - አላህ በርሱ ላይ ግዴታ ያደረገበትን አምልኮ ለመወጣት፣ ክልክሎችን ለመራቅ፣ የላቀ ስነምግባርን ለመላበስ፣ እገዛውንና እርዳታውን የሚፈልግ ሰውን ለማገዝ፣ እውቀትን ለሚፈልግ ሰው እውቀትን ለመስጠት ጉጉት ሊኖረው ይገባል። በገንዘቡም ቸር መሆን ይገባዋል። ገንዘቡን ለነፍሱ ጥቅምና ለወንድሞቹ ጥቅምና ፍላጎት ፈሰስ ማድረግ ይገባዋል።
17 - መንገድ በወጣበት ያላሰበው ጉዳይ አጋጥሞት ነገሮች ሊወሳሰቡበት ስለሚችሉ የጉዞ በጀቱንና ስንቁን ማብዛት ይገባዋል።
18 - እነዚህን ሁሉ ሲፈፅምም የሚለመድና የሚላመድ ሰው እንዲሆን ፊቱን ፈታ አድርጎ፣ ነፍሱ ተደስታና ጓደኞቹንም ደስተኛ ለማድረግ እየጣረ መፈፀም ይገባዋል።
19 - ከጓደኞቹ ለሚያጋጥመው ሻካራ ባህሪና የሐሳብ አለመስማማት በትዕግስት ሊያልፍ ይገባል። እንዲሁም በመካከላቸው የተከበረና በልባቸውም ከፍ ያለ ቦታ እንዲኖረው፣ በተሻለችው መንገድ ሊይዛቸው ይገባል።
20 - ተጓዦች አንድ ስፍራ ላይ እረፍት ሲወስዱ እርስ በርሳቸው ተጠጋግተው መቀመጥ ይወደድላቸዋል። የተወሰኑ ሶሓቦች አንድ አካባቢ ላይ ሲያርፉ ወደ ሸለቆዎችና ወደ ተራራ ስር ተበታትነው ያርፉ ነበር። ነቢዩም (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ አሏቸው: «ይህ ወደ ሸለቆና ወደ ተራራ ስር ተበታትናችሁ ማረፋችሁ ከሸይጧን ነው።» [20] ከዛን ጊዜ በኋላ ልብስ ቢዘረጋላቸው ሁሉንም በቅቷቸው በሚያስቀምጥ ደረጃ እርስ በርሳቸው ተጠጋግተው ይቀመጡ ነበር። [20] ኢማሙ አሕመድ በሙስነዳቸው በቁጥር (17736) ዘግበውታል
21 - ከጉዞም ይሁን ከሌላ ቦታ ወደ አንድ ስፍራ በሚያርፍ ወቅት ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ተረጋግጦ የመጣውን ዱዓ ማድረጉ ይወደድለታል: (አዑዙ ቢከሊማቲላሂ አትታማት ሚን ሸሪ ማ ኸለቅ) ትርጉሙም (ከፍጡራኑ ክፋት ሙሉ በሆኑ የአላህ ቃላት እጠበቃለሁ።) ማለት ነው። [21] እርሱ ይህንን ካለ ከዛ ስፍራ ለቆ እስኪንቀሳቀስ ድረስ ምንም ጉዳት አያጋጥመውም። (21) ሙስሊም በቁጥር (2708) ዘግበውታል
22 - ከፍ ወዳሉ ቦታዎች ላይ ሲወጣ ተክቢራ ማለት፣ ዝቅ ወዳሉ ስፍራዎችና ወደ ሸለቆ ሲወርድ ደግሞ ተስቢሕ ማለቱ ይወደድለታል። ጃቢር (አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና) እንዲህ ብሏል: «ከፍ ወዳሉ ቦታዎች ስንወጣ ተክቢራ፣ ስንወርድ ደሞ ተስቢሕ እንል ነበር።» [22] ተክቢር በሚሉበት ወቅትም ድምፅን ከፍ ማድረግ አይገባም። ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: (እናንተ ሰዎች ሆይ! ለነፍሳችሁ እዘኑ። እናንተ የምትጠሩት ደንቆሮንም ሆነ ሩቅ የሆነን አይደለምና። እርሱ ከእናንተ ጋር ነው፤ እርሱ ሰሚ፤ ቅርብ ነው።) [23] (22) ቡኻሪ በቁጥር (2994) ዘግበውታል (23) ቡኻሪ በቁጥር (2993) ዘግበውታል
23 - ከሚጓዝባቸው ወቅቶች መካከል ምሽት ላይ በተለይም በምሽቱ መጀመሪያ ላይ ጉዞ ቢያደርግ ይወደድለታል። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: «የምሽት ጉዞን አደራ ተጓዙ። ምድር በምሽት ትሰበሰባለችና።» [24] [24] አቡ ዳውድ በቁጥር (2571) ዘግበውታል
24 - በጉዞ ወቅት ዱዓ ማብዛት ይወደድለታል። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: «ተቀባይነታቸው ጥርጥር የሌለባቸው ሦስት ዱዓዎች አሉ፦ የተበዳይ ዱዓ፣ ጉዞ ላይ ያለ ሰው የሚያደርገው ዱዓና ወላጅ ለልጁ የሚያደርገው ዱዓ ናቸው።» [25] [25] ኢማሙ አሕመድ በሙስነዳቸው በቁጥር (10771) ዘግበውታል
***
ሁለተኛ: የጠሀራ አፈፃፀም በጉዞ ወቅት:
ጉዞ ላይ ያለ ሰው ለጠሃራው ትኩረት መስጠት ግዴታው ነው። ትንሹ ሐደሥ ሲያጋጥመው ዉዱእ ያድርግ ጀናባ ሲያጋጥመው ደግሞ ገላውን ይታጠብ።
ውሃ ካላገኘ ወይም ያለው ውሃ ለመብሉና ለመጠጡ የሚፈልገው ያህል ትንሽ ውሃ ብቻ ከሆነ ተየሙም ያድርግ።
የተየሙም አፈፃፀም: በሁለት እጆቹ መሬቱን ይመታ እና በነርሱ ፊቱንና መዳፎቹን ያብሳል።
የተየሙም ጦሃራ ጊዜያዊ ጦሃራ ነው። ልክ ውሃ እንዳገኘ የተየሙሙ ጠሃራ ይበላሽና ውሃውን መጠቀሙ ግዴታው ይሆናል። ጀናባ አጋጥሞት ተየሙም ካደረገ በኋላ ከዚያም ውሃ ቢያገኝ ገላውን ታጥቦ ጀናባውን ማንሳት ግዴታው ይሆናል። ተፀዳድቶ ተየሙም ቢያደርግ እና ከዚያም ውሃ ቢያገኝ ዉዱእ ማድረግ ግዴታው ይሆናል። በሐዲሥ እንዲህ የሚል ተዘግቧል: "አንድ ሙስሊም ለአስር አመት ውሃ ባያገኝ እንኳ ንፁህ አፈር የሙስሊም ዉዱእ ማድረጊያ (ሆኖ የሚቆጠር) ነው። ውሃ ያገኘ ጊዜ ግን አላህን ይፍራ! ሰውነቱን በውሃ ያስነካው።" [26] [26] ኢማሙ አሕመድ በሙስነዳቸው በቁጥር (10068) ዘግበውታል
በሁለት ኹፎች ላይ ማበስ በቁርአን፣ በሐዲሥና በአህሉ ሱና ዑለሞች ስምምነት ባጠቃላይ የተደነገገ ነው።
በሁለት ኹፎች ላይና በነርሱ ተመሳሳይ ብይን ያለው ነገር ላይ ለማበስ የሚከተሉት መስፈርቶች መሟላት አለባቸው:
1 - ኹፎቹ ወይም ካልሲዎቹ ንፁህና ፍቁድ መሆን አለባቸው፤
2 - ዉዱእ ያለው ሆኖ ሊለብሳቸው ይገባል፤
3 - ኹፎቹ ዉዱእ ሲያደርግ የግዴታ ማጠብ የሚገባውን የእግር ክፍል የሚሸፍኑ መሆን አለባቸው፤
4 - የሚያብሰው ትንሹ ሐደሥ ሲያጋጥመው ብቻ መሆን አለበት። ጀናባን ወይም ገላ መታጠብን የሚያስገድዱ ነገሮች ሲያጋጥሙት ኹፉ ላይ ማበስ አይፈቀድለትም።
5 - የሚያብሰውም በሸሪዓ በተገደበለት ወቅት ውስጥ መሆን አለበት። እርሱም ሀገሩ ተቀማጭ ለሆነ ሰው አንድ ቀን ከነሌሊቱ ሲሆን ጉዞ ላይ ላለ ሰው ደግሞ ሶስት ቀን ከነሌሊቱ ነው። ይህ የጊዜ ገደብ የሚጀምረውም በትክክለኛው የዑለሞች አቋም መሰረት ዉዱእ ካጠፋ በኋላ መጀመሪያ ማበስ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ሀገሩ ተቀማጭ የሆነ ሰው ልክ በሃያ አራተኛ ሰአቱ ጊዜ ገደቡ ሲጠናቀቅበት ጉዞ ላይ ያለ ሰው ደግሞ ልክ በሰባ ሁለተኛ ሰአቱ ይጠናቀቅበታል።
የማበስ ፈቃዱ ከሶስት ነገሮች መካከል አንዱ ከተከሰተ ይበላሻል:
1 - ጀናባን የመሰለ ገላ መታጠብን የሚያስገድድ ነገር ከተከሰተ የግድ መታጠብ ስላለበት የማበስ ፍቃዱ ይበላሻል።
2 - ካበሰ በኋላ ካወለቃቸው፤
3 - በሸሪዓ የተገደበው የጊዜ ገደብ ከተጠናቀቀም የማበስ ፍቃዱ ይበላሻል።
***
ጉዞ ላይ ሶላትን የማሳጠር ህግጋት:
ጉዞ ላይ ሞልቶ ከመስገድ ይልቅ አሳጥሮ መስገድ በላጭ ነው። ነገር ግን ጉዞ ላይ ያለ ሰው ባለ አራት ረከዓ ሶላቶችን አራት ረከዓ አድርጎ ሞልቶ ቢሰግድ ሶላቱ ትክክለኛ ናት። ይሁን እንጂ በላጭ የሆነውን ተቃርኗል።
ጉዞ ላይ ያለ ሰው በሚኖርበት መንደር ወይም ከተማ ካሉ አጠቃላይ ቤቶች አልፎ ሲወጣ ማሳጠር ይችላል። ይህም የአብዛኛው ዑለማዎች አቋም ነው።
የሶላት ወቅት ከገባ በኋላ ቢጓዝ ወቅቱ ከመውጣቱ በፊት ስለሆነ ጉዞ የጀመረው ማሳጠር ይችላል።
ጉዞ ላይ ያለ ሰው በሚያስፈልገው ወቅት በዝሁርና በዐስር መካከል፣ በመግሪብና በዒሻ መካከል ሰብስቦ መስገዱ ሱና ነው። ጉዞውን ሳያርፍ እየገሰገሰ ከቀጠለ አስቀድሞ ወይም አዘግይቶ ለርሱ ምቹ በሆነው ወቅት ሰብስቦ ይሰግዳል።
ሰብስቦ መስገዱ ጉዞ ላይ ላለው ሰው አስፈላጊ ካልሆነ በቀር (በየወቅቱ ነጣጥሎ እንጂ) ሰብስቦ አይስገድ። ለምሳሌ አንድ ስፍራ ላይ አርፎ የሁለተኛው ሶላት ወቅት ከገባ በኋላ እንጂ መንቀሳቀስ በማይፈልግበት ሁኔታ ላይ ከሆነ በላጩ ሰብስቦ አለመስገዱ ነው። ምክንያቱ ደግሞ መሰብሰቡ ምንም ስለማያስፈልገው ነው። ለዛም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በመሰናበቻ ሐጅ ወቅት ሚና ባረፉ ጊዜ ስላላስፈለጋቸው ሰብስበው አልሰገዱም።
ሱና ሶላቶችን በተመለከተ ጉዞ ላይ ያለ ሰው ሀገሩ የተቀመጠ ሰው የሚሰግደውን ሱና ሶላቶች ይሰግዳል። የዱሓ ሶላትን፣ የለይልና የዊትር ሶላትን ሌሎችንም ከዝሁር፣ ከመግሪብና ከዒሻ ቀብሊያና ባዕዲያ ሶላት ውጪ ያሉ ሱና ሶላቶችን መስገድ ይችላል። ከፈጅር ቀብሊያ ውጪ ያሉ ቀብሊያና በዕዲያ ሶላቶችን ግን ሱናው አለመስገዱ ነው።
ጉዞ ላይ እንደፕሌን፣ መኪና፣ መርከብና ሌሎችም መጓጓዣዎች ላይ ሱና ሶላቶችን መስገድ ይፈቀዳል። ግዴታ ሶላት ከሆነ ግን ከአቅሙ በላይ እስካልሆነ ድረስ የግድ መውረድ ይኖርበታል።
ጉዞ ላይ የሆነ ሰው ሀገሩ ተቀማጭ ከሆነ ሰው ኋላ መስገዱ ይበቃለታል። ነገር ግን ጉዞ ላይ ያለው ሰው ከኢማሙ ጋር አብሮ ለመስገድ ያገኘው ሁሉንም ረከዓ ይሁን ወይም አንድ ረከዓና ከዛ በታች ቢሆንም ኢማሙ የመጨረሻው ተሸሁድ ላይ እያለ ከማሰላመቱ በፊት ቢጀምር እንኳ ልክ እንደ ኢማሙ ሶላቱን ሞልቶ ነው የሚሰግደው። ከዑለሞች ሁለት የተለያዩ አቋሞች መካከል ትክክለኛውና ሚዛን የሚደፋው ይሄ ነው።
***
አራተኛ: ከሐጅ፣ ከዑምራ ወይም ከጉዞ የመመለስ ስነስርዓት:
ለመመለስ መፍጠን ይገባዋል። ያለአስፈላጊ ጉዳይ ጉዞ ላይ መቆየት አይገባውም። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: «ጉዞ ከስቃይ አንዱ ቁራጭ ነው። ከእናንተ አንዱን ምግብ፣ መጠጥና እንቅልፉን (በስርዓቱ እንዳያገኝ) ይከለክለዋል። ስለዚህ፣ የጉዞ ዓላማውን ከፈጸመ፣ ፈጥኖ ወደ ቤተሰቡ ይመለስ።» [27] (27) ቡኻሪ በቁጥር (1804) እና ሙስሊም በቁጥር (1927) ዘግበውታል
ወደ ሃገሩ መመለስ በፈለገ ጊዜ መጓጓዣው ላይ እንደወጣ የጉዞን ዱዓ ይቅራና ይህንን ይጨምርበት: «አዪቡን፣ ታኢቡነ፣ ዐቢዱነ ሊረቢና ሓሚዱን) ትርጉሙም (ተመላሾች ነን፣ ተፀፃቾች ነን፣ ጌታችንን አምላኪዎችና አመስጋኞች ነን።» [28] (28) ቡኻሪ በቁጥር (1797) እና ሙስሊም በቁጥር (1342) ዘግበውታል
ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከጉዞ በሚመለሱ ወቅት እንደሚሉ የተረጋገጠውን ውዳሴ ከጉዞ በሚመለስ ወቅት ማለቱ ይወደዳል። እርሳቸው ከዘመቻ ወይም ከሐጅ ወይም ከዑምራ በሚመለሱ ወቅት ከፍ ያለ ቦታ ላይ በወጡ ቁጥር ሶስት ጊዜ ተክቢራ ይሉ እና ቀጥለውም እንዲህ ይሉ ነበር : (ላኢላሃ ኢለሏሁ ወሕደሁ ላ ሸሪከ ለሁ፣ ለሁልሙልኩ፣ ወለሁል ሐምዱ፣ ወሁወ ዐላ ኩሊ ሸይኢን ቀዲር፣ አዪቡነ ታኢቡነ ዐቢዱነ ሳጂዱነ ሊረቢና ሓሚዱን፣ ሰደቀሏሁ ወዕደህ፣ ወነሶረ ዐብደህ፣ ወሀዘመል አሕዛበ ወሕደህ) ትርጉሙም (ከአላህ በቀር በእውነት የሚመለክ የለም፤ ብቸኛና አጋር የለውም። ንግስና ለርሱ የተገባ ነው። ምስጋናም ለርሱ የተገባ ነው። እርሱም በሁሉም ነገር ላይ ቻይ ነው። ተመላሾች፣ ተፀፃቾች፣ አምላኪዎች፣ ሰጋጆች፣ ለጌታችን አመስጋኞች ነን። አላህ ቃሉን በእውነት ሞላ፣ ባሪያውንም ረዳ፣ የጥመት ጭፍራንም ብቻውን አሸነፈ።) [29] (29) ቡኻሪ በቁጥር (4116) ዘግበውታል
ሀገሩን በተመለከተ ወቅት እንዲህ ማለቱ ይወደድለታል: "ኣይቡነ፤ ታኢቡነ፤ ዓቢዱን ሊረቢና ሐሚዱን" (ትርጉሙም፡ ጌታችንን እያመሰገንን ተፀፃቾችና፤ ተውባ አድራጊዎች፤ ሆነን ተመለስን።) [30] ይህንንም ሀገሩ እስኪገባ ድረስ ይደጋግመው። ይህም የሚያደርገው ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለፈፀሙት ነው። (30) ቡኻሪ በቁጥር (1797) እና ሙስሊም በቁጥር (1342) ዘግበውታል
ከቤተሰቡ ለረጅም ጊዜያት ርቆ ሲመለስ አስፈላጊ ሁኖ ወይም በምሽት እንደሚደርስ ቀድሞ አሳውቋቸው ካልሆነ በቀር በምሽት አይግባ። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለከለከሉ ነው። ጃቢር ቢን ዐብደላህ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ አሉ: "ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሰውዬው ወደ ቤተሰቡ በምሽት መግባቱን ከለከሉ።" [31] የዚህንም ጥበብ ሌላኛው ዘገባ እንዲህ በሚል አብራርቶታል: (ፀጉሯ ቅባት ሳይነካው ከርሞ የተንጨባረረባት [32] እንድታበጥር፣ ባሏ ርቆ የከረመባት (የምትላጨውን) እንድትላጭ ነው።) [33] በሌላ ዘገባ ደግሞ «የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) አንድ ሰው ቤተሰቦቹን በክህደት ለመጠርጠር ወይም ነውራቸውን ለመሰለል አስቦ በሌሊት (ድንገት) መምጣቱን ከልክለዋል።» [34] (31) ሙስሊም በቁጥር (715) ዘግበውታል [32] (ሸዕሣ) ማለት ፀጉሯ ቅባትና መበጠርን ካየ ጊዜያትን ያስቆጠረች ማለት ነው። (ኢስቲሕዳድ) ማለት ስለትን ለመላጨት መጠቀም ማለት ነው። (ሙገየባህ) ማለት ባሏ ከርሷ የራቀ ማለት ነው። "አትተሕሪር ፊ ሸርሒ ሶሒሕ ሙስሊም - አልአስበሃኒይ" (292 ገፅ) [33] ነሳኢይ በቁጥር (9099) ዘግበውታል [34] ሙስሊም በቁጥር (715) ዘግበውታል
ከጉዞ ወደ ሃገሩ የሚገባ ሰው በቅድሚያ ቤቱ አካባቢ የሚገኝ መስጂድ በመግባት ሁለት ረከዐ ይስገድ። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለፈፀሙት ነው።
አንድ ጉዞ የወጣ ሰው ከጉዞው ሲመለስ የራሱና የጎረቤቱ ልጆች አቀባበል ሲያደርጉለት እዝነት ሊያሳያቸውና በጎ ነገር ለነርሱ ማድረጉ ይወደድለታል። ከኢብኑ ዐባስ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) እንደተላለፈው እንዲህ አለ: «ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) መካ የገቡ ጊዜ የበኒ ዐብዱል ሙጦሊብ ህፃናቶች አቀባበል አደረጉላቸው። ከህፃናቶቹ መካከልም አንዱን ከፊታቸው አንዱን ከኋላቸው ተሸከሙ።» ዐብደላህ ቢን ጀዕፈር (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ አሉ: «ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከጉዞ ሲመለሱ እኛ (ልጆች) እየወጣን እንቀበላቸው ነበር። እኔና ሐሰን ወይም ሑሰይን ልንቀበላቸው ወጥተን ነበር፤ እሳቸውም አንዳችንን ከፊትለፊታቸው፣ ሌላኛችንን ደግሞ ከኋላቸው (በእንስሳቸው ላይ) አንግበው (አፈናጠው) መዲና እስክንገባ ድረስ ይዘውን ገቡ።» [35] [35] ሙስሊም በቁጥር (2428) ዘግበውታል
ስጦታ መሰጣጠት ልብን ስለሚያፋቅር፣ መቃቃርን ስለሚያስወግድ ይወደዳል። መቀበሉና የስጦታውን ውለታ መመለስም ይወደዳል። ስጦታውን ከመቀበል የሚከለክለው ሸሪዓዊ ምክንያት እስከሌለ ድረስ ስጦታውን መመለስ ይጠላል። ለዚህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል: «ስጦታ ተሰጣጡ፤ ትዋደዳላችሁ።» [36] ስጦታ መሰጣጠት በሙስሊሞች መካከል ውዴታን ከሚያመጡ ምክንያቶች መካከል አንዱ ነው። [36] አል'በይሃቂይ በ«አስ-ሱነኑ አል-ኩብራ» (11946) ዘግበውታል
አንድ ጉዞ የወጣ ሰው ወደ ሃገሩ የገባ ጊዜ በመተቃቀፍ ሰላምታ መለዋወጡ ይወደድለታል። ይህም ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ባልደረቦች የተረጋገጠ ጉዳይ ነው። አነስ (አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና) እንዲህ አለ: «በሚገናኙበት ወቅት በመጨባበጥ ሰላምታ ይለዋወጡ ነበር። ከጉዞ የገቡ ጊዜ ግን በመተቃቀፍ ነበር ሰላምታ የሚለዋወጡት።» [37] [37] ጦበራኒይ በ"አልአውሰጥ" በቁጥር (97) ዘግበውታል
የአሏህ ሶላትና ሰላም በነቢያችን ሙሐመድ ላይ ይስፈን።