مخالفات الحج والعمرة والزيارة
በሐጅ፣ በዑምራና በዚያራ ወቅት የሚስተዋሉ ተቃርኖዎች
በሐጅ፣ በዑምራና በዚያራ ወቅት የሚስተዋሉ ተቃርኖዎች
በልዩ ልዩ ቋንቋዎች የኢስላማዊ ይዘት አገልግሎት ማህበር የሊቃውንት ኮሚቴ
ከዑምራ ጋር ተያያዥ የሆኑ ስህተቶችና ተቃርኖዎች
የመጀመሪያው: ሰዎች በኢሕራም ወቅት የሚሰሯቸው ስህተቶችና ተቃርኖዎች:
1. ኢህላልን መተው (ድምፅን ከፍ አድርጎ ተልቢያ አለማለት)። ይህ ማለት አንድ ሰው ኢሕራም ሲጀምር ሊፈጽመው ያሰበውን የሐጅ ወይም የዑምራ አይነት ድምፁን ከፍ አድርጎ አለመግለጹ ነው።
ሱናው ግን ድምፅን ከፍ አድርጎ መናገር ነው።
2. አንዳንድ ሰዎች ኢሕራም ማለት ልብሱ (ሽርጥና ኩታ መልበስ) እንደሆነ አድርገው ማሰባቸው።
ኢሕራም ማለት፡ ወደ ሐጅ ወይም ዑምራ ስርአት ለመግባት መወሰን (ኒያ) ነው። ምልክቱም ድምፅን ከፍ አድርጎ ተልቢያን ማለት ነው። ሐጅን ወይም ዑምራን አስቦ (ነይቶ) ተልቢያ የጀመረ ሰው ኢሕራም አድርጓል።
3. አንዳንድ ሰዎች ለኢሕራም ገላ መታጠብ ግዴታ ነው ብለው ያስባሉ።
ነገር ግን ሱና ነው። በተወውም ሰው ላይ ምንም ወንጀል የለበትም።
4. አንዳንድ ሰዎች ኢሕራም በሚደረግበት ወቅት ሁለት ረከዓ መስገድ ግዴታ ወይም በየትኛውም ሁኔታ ላይ ቢሆንም የግድ ሊፈፀም የሚገባ ራሱን የቻለ ሱና ነው ብለው ያስባሉ።
እውነታው ግን ከኢሕራም በፊት መስገድ የተደነገገ ነው። ነገር ግን ራሱን የቻለ ሶላት የለውም። ግዴታ ሶላት ወይም ማንኛውም የተደነገገ ሶላት ከሰገደ በኋላ ኢሕራም ማድረግ ይበቃዋል።
5. አንዳንድ ሰዎች ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ ላይ መቆምና ወደ መስጂድ መውረድ ግዴታ እንደሆነ ያስባሉ።
ይህ ግን ግዴታ አይደለም። የኢሕራም ልብሱን ለብሶ ዝግጁ የሆነ፤ በኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ (በሚቃት) በኩል ያለፈና መጓጓዣው ውስጥ እያለ ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ ወይም በርሱ ትይዩ የሆነ ስፍራ ሲደርስ ተልቢያ ያደረገ ይህ ይበቃዋል። ለምሳሌ ፕሌን ውስጥ ያለ ሰው ከኢሕራም ማድረጊያ ስፍራው ትይዩ ሲሆን ወይም የኢሕራም ስፍራውን እንዳያልፈው ሲባል ለመድረስ ትንሽ ሲቀረው ተልቢያ በማለት ኢሕራም ያደርጋል።
6. የኢሕራምን ልብስ ሽቶ መቀባት።
ትክክኛው ግን ሰውነትን ብቻ ሽቶ በመቀባት መብቃቃት ነው።
አንዳንድ ሰዎች ኢሕራም በሚያደርጉ ወቅት የብልትን ፀጉር መላጨት፤ ጥፍርን መቆረጥና የብብትን ፀጉር መላጨት ግዴታ ወይም የኢሕራም ሱና ነው ብለው ያስባሉ።
ይህ ግን አስፈላጊ ከሆነ ብቻ የሚፈፀም ከኢሕራም ጋር ምንም ግንኙነት የሌለው አጠቃላይ ሱና ነው።
8. (ከሚቃት) የኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ ከመድረስ በፊት ኢሕራም ማድረግ።
ይህ ሱናን የሚፃረር ነው። ነገር ግን ፕሌን ውስጥ ያለ ሰው በፕሌኑ ፍጥነት ምክንያት ከኢሕራም ማድረጊያ ስፍራው ትይዩ የሚሆንበት ቦታ እንዳያመልጠው ትንሽ ቀደም ብሎ ኢሕራም ማድረግ ይፈቀድለታል። እንዲሁም ከኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ ትይዩ የሚሆንበት ጊዜ ላይ በእንቅልፍ ምክንያት ኢሕራም ሳያደርግ እንዳያመልጠው ቢፈራ እንደ አስፈላጊነቱ ቀደም ብሎ ኢሕራም ማድረግ ይፈቀድለታል።
9. የሐጅ ወይም የዑምራን ስነ ስርዓት መፈፀም የፈለገ ሰው ባለማወቅ ወይም በመዘናጋት ወይም ፕሌን ውስጥ ስላለ የኢሕራም ማድረጊያን ስፍራ ያለኢ ሕራም ማለፍ።
ዑምራን ወይም ሐጅን ነይቶ ከኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ ኢሕራም ሳያደርግ ያለፈ ሰው መፈፀም ያለበት ግዴታ ወደ ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራው ተመልሶ ኢሕራም ማድረግ ነው። ልክ እንደዚሁ በማንኛውም ምክንያት ፕሌን ውስጥ ኢሕራም ሳያደርግ ጅዳ አየር ማረፊያ የወረደ ሰው ወደ አንዱ ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ በመውጣት ከዛ ኢሕራም ማድረግ ግዴታው ነው። ይህ ግዴታ የማይመለከታቸው: (በሚቃት) ኢሕራም በማድረጊያ ስፍራ በኩል የማያልፍ ወይም የማይቅጣጭ ሰው ነው። ይህም ከዛው ከጅዳ ኢሕራም ያደርጋል። ለምሳሌ የሱዳን ሰዎች በፕሌን ወይም መርከብ ሲመጡ የኢሕራም ማድረጊያ ስፍራን አይቅጣጩም። ነገር ግን በመጡበት መንገድ በኩል የየለምለምን ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ ወይም የጁሕፋን ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ እንደሚቅጣጩ ካወቁ ከላይ እንደተጠቀሰው ወደ ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራ መመለስ ግዴታ ይሆንባቸዋል።
10. የተሰፋ ልብስ ስለመከልከሉ ባለ የተሳሳተ ግንዛቤ የተነሳ፣ ስፌት ያለበትን ጫማ ወይም ቀበቶ ለመልበስ ይቸገራሉ (ይጨነቃሉ)።
ይህ ግን ትክክል አይደለም። የተሰፋ በማለት የተፈለገው: ሱሪና ቀሚስን ይመስል በሰውነት መጠን ልክ ተከፋፍሎ የተሰፋውን በተለመደው መልኩ መልበስ ነው የተከለከለው።
11. ሴት ልጅ ጓንት፣ ቡርቃ ወይም ኒቃብ መልበሷ።
ሴት ልጅ ባዳ ወንዶች ዘንድ ስትሆን ማድረግ ያለባት ግዴታ ፊቷንና እጆቿን ከኒቃብና ጓንት ውጪ ባለ ልብስ መሸፈን ነው። ይህም ነቢዩ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና ኢሕራም ያደረገች ሴት እንዳትለብሳቸው ስለከለከሉ ነው።
12. አንዳንድ ሰዎች ሴት ልጅ በኢሕራም ወቅት የምትለብሰው ጥቁር ወይም አረንጓዴ ወይም ነጭ ከለር የሆነ የተለየ ልብስ እንዳለ ማሰባቸው።
ይህም ትክክል አይደለም። ኢሕራም ያደረገች ሴት በጌጥ ሳትገላለጥ የፈለገችውን ልብስ መልበስ ይፈቀድላታል።
13. አንዳንድ ሰዎች የኢሕራም ልብስን መቀየር ወይም ማውለቅ እንደማይፈቀድ ማሰባቸው።
ትክክለኛው ግን ኢሕራም ያደረገ ሰው ልብሱን መለወጥ ወይም ማጠብና ከዚያም ድጋሚ መልበስ ይፈቀድለታል።
14. የኢድጢባዕ አለባበስን (አንድ እጅን አውጥቶ መልበስ) ከኢሕራም መጀመሪያ እስከ መጨረሻ ማድረግ።
ትክክለኛው ግን የኢድጢባዕ አለባበስ የሚደነገገው በዑምራ ጦዋፍ ወቅት ወይም በጦዋፈል ቁዱም ወቅት ብቻ ነው።
15. ምንም ሸሪዓዊ አስገዳጅ ነገር ሳይከሰት ኢሕራምን መተውና ከኢሕራም መፈታት።
ኢሕራም ላይ ያለ ሰው የሐጁን ወይም የዑምራውን ስነ ስርዓት አሟልቶ እስኪፈፅም ድረስ በኢሕራሙ ላይ መቆየቱ ግዴታው ነው። ነገር ግን መፈታትን የሚያስገድድ ሸሪዓዊ ምክንያት ካጋጠመው ይፈታል። እርሱም ከመንገድ መቋረጥ (መታገድ) ነው። ይህ ካጋጠመውም መፈታት ይፈቀድለታል። ኢሕራም በሚያደርግበት ወቅት ከታገደ እንደሚፈታ መስፈርት አድርጎ ከሆነ ምንም የማድረግ ግዴታ አይኖርበትም። ምንም መስፈርት ካላደረገ ግን ፊድያ (ማካካሻ) የማረድ፤ ፀጉሩን የመላጨት ወይም የማሳጠርና የመፈታት ግዴታ ይኖርበታል።
***
ሁለተኛ: ሰዎች በጦዋፍ ወቅት የሚፈፅሟቸው ስህተቶችና ተቃርኖዎች
1. በሐዲሥ ያልመጣ የሆነ መስጂደል ሐራም በሚገባበት ወቅት ወይም ከዕባን በሚመለከቱ ወቅት የሚባልን ዱዓ ማድረግ።
ሱናው ግን ከነቢዩ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና በመጣው ዱዓ ላይ ብቻ መቆጠብ ነው።
2. ጦዋፍ ከመጀመር በፊት ኒያን በአፍ መናገር።
ኒያ ማድረጊያ ቦታ ቀልብ ነው። ኒያን በአፍ መናገር አልተደነገገም።
3. ለጥንቃቄ በሚል ጦዋፍን ከሐጀረል አስወድ በፊት ለመጀመር ማሰብ።
ይህም ወሰን ማለፍ ነው።
4. ጦዋፍን ከሐጀረል አስወድ አለፍ ብሎ መጀመርና ያንን ዙርም እንደ ሙሉ ዙር መቁጠር።
ይህም ስህተት ነው። ይህንን ካደረገም ያ ዙር አይቆጠርለትም።
5. ሐጀረል አስወድን በሚቅጣጩበት ወቅት ልክ ሶላት ላይ እጅ ከፍ እንደሚደረገው ማድረግ ወይም ሶስት ጊዜ ደጋግሞ እጅን ከፍ ማድረግ።
ሱናው በቀኝ እጁ ወደ ሐጀረል አስወድ አንድ ጊዜ ብቻ መጠቆም ነው።
6. ሐጀረል አስወድን በሚቅጣጩበት ወቅት ረጅም ሰዓት መቆም።
ሱናው ረጅም ወቅት አለመቆም ነው።
7. ሐጀረል አስወድ ዘንድ ደርሶ ለመሳም ከባድ መገፋፋትን መፈፀም።
ሱናው አለመገፋፋት ነው። ያለመገፋፋት መድረስ ከቻለ ይስማል፤ ያለበለዚያ ወደርሱ በእጁ ይጠቁማል።
8. ተክቢራ ሳይል ሐጀረል አስወድን ካለፈ በኋላ ወደ ሐጀረል አስወድ በእጁ ለመጠቆም ወይም ተክቢራ ለማለት በሚል መመለስ ወይም ሐጀረል አስወድን ካለፉ በኋላ ተክቢራ ማለት።
ይህ ሁሉ ስህተት ነው። ይህም ቦታውን ካላገኘ ያመለጠ ሱና በመሆኑ ነው። እርሱን ለመፈፀም መመለስ ሱና አይደለም። ረስቶም ይሁን ሆን ብሎ ተክቢራን በተወ ሰው ላይ ምንም ወንጀል የለበትም።
9. ሁሉንም ዙሮች የተለዩ በሆኑ ዱዓዎች መገደብ።
ይህም ምንም ማስረጃ የለውም። ሱናው ጦዋፍ የሚያደርገው ሰው አለማዊም ይሁን የመጪው አለም ጉዳይ ላይ የፈለገውን ዱዓ ማድረጉ ነው። [1] ተስቢሕም ወይም ተሕሚድም ወይም ተህሊልም ወይም ተክቢርም ወይም ቁርአን መቅራትም ይሁን የተደነገገ በሆነ ማንኛውም ዚክር አላህን ማውሳት ነው።
10. በሁሉም የጦዋፍ ዙሮች ሶምሶማ ማድረግ (ፈጣን እርምጃ መራመድ)።
ሱናው በመጀመሪያዎቹ ሶስት ዙሮች ብቻ ሶምሶማ ማድረግ (ፈጣን እርምጃ መራመድ) ነው።
11. ያለምንም በቂ ምክንያት በጦዋፉ ወቅት ካዕባን በግራ ማድረግን ተግባራዊ አለማድረግ።
ሱናው ካዕባን በግራ በኩል ማድረግ ነው። ይህንን በመፃረር ዙሪያ መዘናጋት አይገባም። እንደመገፋፋትና የመሳሰሉት ይህን እንዳይተገብር ያደረገው በቂ ምክንያት ካለው ግን ምንም ችግር የለውም።
12. ሩክነል የማኒን መሳም ወይም መሳም ባቃተው ወቅት ወደርሱ በእጁ መጠቆም።
ሱናው በእጅ መዳበስ ብቻ ነው እንጂ አይስምም፤ በእጁ መዳበስ ካቃተውም ወደርሱ እጁን አይጠቁምም።
13. ሁሉንም የከዕባ ማዕዘናትን መሳምና መዳበስ ወይም ግድግዳዎቿን መተሻሸት፤
ይህም ከሱናው ተፃራሪ ነው። ሐጀረል አስወድን ከመሳምና ሩክነል የማኒን ከመዳበስ ውጪ የተደነገገ ነገር የለምና።
14. ሩክነል የማኒና ሐጀረል አስወድን የሚዳበሱት ለአምልኳዊ አፈፃፀም ሳይሆን ከነርሱ በረከትን ፍለጋ እንደሆነ አድርጎ ማሰብ፤
ይህ ሁሉ አለማወቅና ጥመት ነው። መጥቀምና መጉዳት ያለው በአላህ እጅ ብቻ ነው። ከዑመር - አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና - እንደተላለፈው እርሱ ወደ ሐጀረል አስወድ በመምጣት ሳሙትና እንዲህ አሉ: " እኔ የማትጎዳና የማትጠቅም ድንጋይ እንደሆንክ አውቃለሁ። ነቢዩ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና ሲስሙህ ባላይ ኖሮ አልስምህም ነበር።" (1) ቡኻሪ በቁጥር (1597) ዘግበውታል።
15. ሌሎች ጦዋፍ አድራጊዎችን በሚወሰውስ መልኩ ድምፅን ከፍ አድርጎ ዱዓ ማድረግ፤
ሱናው ሌሎችን እንዳይወሰውስ በርሱና በጌታው መካከል ብቻ ጌታውን መማፀንና ማውሳት ነው።
16. በጦዋፍ ወቅት (ቪዲዮ/ፎቶ) በመቅረፅና ከጎኑ ካለው ሰው ጋር በማውራት መጠመድ፤
ጦዋፍ ለሚያደርግ ሰው የተደነገገለት በተመስጦ፣ በመተናነስና ልቡን በመሰብሰብ ጌታውን እንዲያወሳ ነው።
17. ሐጀረል አስወድ ዘንድ መድረሱን ከማረጋገጡ በፊት ጦዋፍን ማጠናቀቅ፤
ጦዋፍ የሚያደርግ ሰው በሐጀረል አስወድ ትይዩ መድረሱን እስኪያረጋግጥ ወይም እስኪያመዝን ድረስ ሰባተኛው ዙሩንም መሙላት ይጠበቅበታል።
18. የጦዋፍ ሁለት ረከዓ የግድ ቀጥታ ከመቃም ኢብራሂም ኋላ ወይም ወደርሱ ተጠግቶ መሆን አለበት ብሎ ማመን፤ ለዚህም መገፋፋትና በሐጅ ወቅት ጦዋፍ አድራጊዎችን ማወክና የጦዋፍ ጉዟቸው ላይ እንቅፋት መሆን፤
ይህ እሳቤም ስህተት ነው። ከጦዋፍ በኋላ የሚሰገዱት ሁለት ረከዓዎችን መስጂዱ ውስጥ በሚገኝ ማንኛውም ስፍራ መፈፀም ይበቃል። ሰጋጁም ቢርቅ እራሱ መቃም ኢብራሂምን በርሱና በከዕባ መሃል ማድረግ ይችላል። መስጂደል ሐራም ሜዳው ላይም ወይም ኮሪደሩ ላይ መስገድ ይችላል። በዚህ ከመታወክም ይገላገላል፤ በእርጋታና በተመስጦ መስገድንም ያገኛል።
19. የጦዋፍን ሁለት ረከዓዎችና ከሶላቱ በኋላ የሚደረግ ዱዓን ማርዘም፤
ሱናው ቀለል አድርጎ መስገድ ነው። ከነቢዩ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና የመጣ ምንም ነገር ስለሌለም ከሶላቱ በኋላ ምንም ዱዓ አለማድረግ ነው።
20. የጦዋፍን ሁለት ረከዓዎች የኢድጢባዕ አለባበስ እንደለበሱ መፈፀም፤
ሱናው ጦዋፉን ካጠናቀቀ በኋላ በቀጥታ ኩታውን ወደ ትከሻዎቹ መመለስ ነው።
***
ሶስተኛ: ሰዎች በሶፋና መርዋ መካከል ሲሮጡ የሚፈፅሟቸው ስህተትና ተቃርኖዎች:
1. በሰዒይ ወቅት የኢድጢባዕ አለባበስን መልበስ።
ቀደም ብለን እንደገለጽነው የኢድጢባዕ አለባበስ በጦዋፍ ወቅት ብቻ የሚለበስ ነው።
2. ሰዒይ ከመጀመር በፊት ኒያን በአፍ መናገር።
ቀደም ብለን እንደገለጽነው የኒያ ቦታው ልብ ውስጥ ነው። በምላስ መናገሩ ያልተደነገገ ተግባር ነው።
3. ሰዒይን ከመርዋ መጀመር።
ይህ ስህተት ነው። ይህን ያደረገ ሰው ከመርዋ የጀመረው ዙር አይቆጠርለትም።
4. አንዳንድ ሰዎች አንድ ዙር ማለት ሄዶ መመለስ ነው ብለው ስለሚያስቡ አስራ አራት ዙር ሰዒይ ያደርጋሉ።
ይህም ስህተት ነው። ከሶፋ ወደ መርዋ መጓዝ አንድ ዙር ሲሆን፣ ከመርዋ ወደ ሶፋ መመለስ ደግሞ ሌላ ዙር ነው። የሚጀመረው ከሶፋ ሲሆን የሚጠናቀቀው መርዋ ላይ ነው።
5. ግዴታ ነው ብሎ በማሰብ ወደ ሶፋ ተራራ ጫፍ መውጣት።
ይህ መስፈርት ለመሆኑ ምንም ማስረጃ የለም።
6. ልክ ሶላት ላይ ተክቢራ ሲያደርግ እንደሚያደርገው እጆችን ከፍ ማድረግና በእጆች ጥቆማ ማድረግ።
ትክክለኛው ወደ ቂብላ በመዞርና ከነቢዩ (ﷺ) የተገኙ ዱዓዎችን በማድረግ መብቃቃት ነው።
7. ሴቶች በሁለቱ (አረንጓዴ) የመሮጫ ምልክቶች መካከል ልክ እንደ ወንዶች በሀይለኛ መሮጣቸው።
በዑለሞች ሁሉ ስምምነት (ኢጅማዕ) ከመገላለጥ ለመጠበቅ ሲባል ለርሷ የተደነገገው በመራመድ ላይ ብቻ እንድትቆጠብ ነው።
8. እያንዳንዱን የሰዒይ ዙር በተወሰነ ( ልዩ በሆኑ) ዱዓ መመደብ።
ለዚህ ምንም ማስረጃ የለም። ይልቁንም ያለ ምንም ገደብ የፈለገውን ዱዓ ያድርግ። [2]
9. በሰዒይ ቦታ (መስዓ) ላይ የሰዎችን ትኩረት በሚበታትን መልኩ ድምጽን ከፍ ማድረግ።
ሱናው ሌሎችን እንዳይወሰውስ በሚል በጌታውና በነፍሱ መካከል በሆነ ድምፅ ጌታውን ማውሳትና ዱዓ ማድረግ ነው።
10. በሁሉም የሰዒይ ዙር በሶፋና በመርዋ መካከል መፍጠን።
ሱናው በደንብ መፍጠን ያለበት በሁለቱ አረንጓዴ ምልክቶች መካከል ብቻ ነው።
11. ሰዒይን ካጠናቀቁ በኋላ ሁለት ረከዓ መስገድ።
ለዚህ ምንም ማስረጃ ስለሌለው መፈጸሙ አልተደነገገም።
12. ከሐጅ ወይም ከዑምራ ስርአት (ኑሱክ) ውጪ ሰዒይን በራስ ተነሳሽነት ( እንደ ተጠዉዕ) መፈጸም።
ሰዒይ ከሐጅና ዑምራ ውጪ በራስ ተነሳሽነት (ተጠዉዕ) መፈፀሙ ልተደነገገም።
***
አራተኛ: ሰዎች ፀጉራቸውን በሚላጩበት ወይም በሚያሳጥሩበት ወቅት የሚፈፅሟቸው ተቃርኖዎችና ስህተቶች:
1. በመላጨት ወይም በማሳጠር ወቅት ፀጉርን ሙሉ ጭንቅላት ላይ ከማዳረስ መዘናጋት።
ሱናው ሙሉ ጭንቅላትን አዳርሶ መላጨት ወይም ማሳጠር ነው።
2. መስጂደል ሐራም ውስጥ ተላጭቶ ወይም አሳጥሮ ፀጉሩን እዚያው መጣል።
መስጂደል ሐራምን ማላቅና ንጽህናውን ለመጠበቅ መጣር ግዴታ ነው።
3. መላጨትን ወይም ማሳጠርን ወደ መርሳት ወይም ትቶ በሌላ ነገር መጠመድ እስኪያደርስ ድረስ እጅግ በጣም ማዘግየት።
የተደነገገው ጦዋፍና ሰዒን እንዳጠናቀቁ ወዲያውኑ መፈጸም ነው።
4. ከመላጨት ወይም ከማሳጠር በፊት ኢሕራም ያደረገ ሰው የሚከለከላቸውን ነገሮች መፈፀም።
ግዴታው ከተላጨ ወይም ካሳጠረ በኋላ ካልሆነ በስተቀር ከኢሕራም ክልከላዎች ምንም ነገር አለመፈጸም ነው።
***
ከሐጅ ጋር ተያይዞ የሚፈፀሙ ተቃርኖዎችና ስህተቶች:
የመጀመሪያው: በተርዊያ ቀን (በዙልሒጃ ስምንተኛው ቀን) ሰዎች የሚፈፅሟቸው ጥሰቶችና ስህተቶች
1. አንዳንድ ሰዎች የተርዊያ ቀን ኢሕራም ማድረግ የተደነገገው መስጂደል ሐራም ውስጥ ወይም የከዕባ አሸንዳ ስር ነው ብለው ያስባሉ።
ሱናው በመካም ይሁን በሚና ካለበት ቦታ ሆኖ ኢሕራም ማድረግ ነው።
2. ኢሕራምን ከዙህር ሶላት በኋላ ለማድረግ ማዘግየት።
ሱናው የሐጅን ኢሕራም ከዙህር ሶላት በፊት በረፋድ ወቅት ማድረግ ነው።
3.ሚና ማደር እየቻሉም ሚና ማደርን መተው።
ነቢዩ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና ስለፈፀሙት ሐጅ ለሚያደርግ ሰው ሱናው እስከቻለ ድረስ ሚና ማደር ነው።
4. ሚና እያለ ሶላቶችን ሰብስቦ በአንድ ወቅት መስገድ፤
ነቢዩን የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና በመከተል ሱናው ሚና እያለ ሶላቶችን ማሳጠር ነው እንጂ መሰብሰብ አይደለም።
***
ሁለተኛ፡ በዓረፋ ቀን ሰዎች የሚፈፅሟቸው ተቃርኖዎችና ስህተቶች፡
1. ለጥንቃቄ በሚል፣ ከስምንተኛው ቀን የተወሰነውን ክፍል ዓረፋ ላይ መቆም።
ይህ ከተከለከለው ድንበር ማለፍ (ጉሉው) እና ራስን ማስቸገር (ተከሉፍ) ይመደባል።
2. በስምንተኛው ቀን ወይም የዘጠነኛው ቀን ምሽት ወደ ዓረፋ በመውጣት እዛ ማደር።
ይህ የሱናው ተቃራኒ ነው። እንዲሁም በሚና የማደርን ሱና የሚያጠፋም ነው።
3. ከዓረፋ ክልል ውጪ መቆም።
ሐጅ የሚያደርግ ሰው ማድረግ ያለበት ግዴታ የዓረፋ ክልል ውስጥ ለመቆም መታገል ነው።
4. የግዴታ ነሚራ መስጂድ ውስጥ ከኢማሙ ጋር መስገድ አለብን በሚል እሳቤ መስጂድ ውስጥ ለመቆየት ከባድ መገፋፋትን መፍጠር።
ይህ ግን ግዴታ አይደለም። ለዚህ ብሎ መገፋፋትም አልተደነገገም።
5. ዱዓእ በሚያደርግበት ወቅት ወደ (ኢላል) ተራራ መዞር።
ሱናው ወደ ቂብላ መዞር ነው።
6. ወደ ኢላል ተራራ መውጣት ግዴታ ነው ብሎ ወይም ይህንን የሐጅ አንዱ ስራ ነው ብሎ ወይም ይህ ከሌሎች የዓረፋ ስፍራዎች የተለየ ደረጃ ወይም መለዮ አለው ብሎ ማመን።
ለዚህም ምንም ማስረጃ የለውም። እንደውም የነቢዩን የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና መመሪያ የተፃረረ ነው።
7. የ(ኢላል) ተራራን የራሕማ ተራራ ወይም (የዱዓ ተራራ) ብሎ መጥራት።
ትክክለኛው ግን ስሙ (ኢላል) ነው። የራሕማ ወይም የዱዓ ተራራ ብሎ ለመጥራት የሚያስችል ምንም ማስረጃ የለም።
8. የዓረፋ ተራራ ላይ ወዳለው ጉልላት (ቁባ) መግባት፤ የአደም ቁባ ብሎ መጥራት ውስጡ መስገድና ከዕባ ጦዋፍ እንደሚደረገው እርሱን ጦዋፍ ማድረግ።
ይህ ሁሉ የተከለከለው ቢድዓ ውስጥ የሚመደብ ነው። ወደ ሺርክም ሊደርስ ይችላል።
9. ዓረፋ ክልል ውስጥ ባለው "የራሕማ ተራራ" ላይ በተተከለው ምሰሶ በረከትን መፈለግ (ተበሩክ) እና እርሱ ላይ ስምን መፃፍ።
ይህ ሁሉ የተከለከለው ቢድዓ ውስጥ የሚመደብ ነው። ወደ ሺርክም ሊደርስ ይችላል።
10. የዓረፋ ተራራ ላይ ወይም የኑር ተራራ ላይ በሚገኙ ሽንቁሮች ውስጥ ብር መክተት ወይም ፀጉር ወይም ጥፍር ወይም ልብስና የመሳሰሉትን ማኖር፤ ይህን ማድረጋቸውም ወደዚህ ስፍራ ድጋሚ እንደሚያመጣቸው ማመን።
ይህ ሁሉ የተከለከለው ቢድዓ ውስጥ የሚመደብ ነው። ወደ ሺርክም ሊደርስ ይችላል።
11. አንዳንድ ሰዎች ነቢዩ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና የቆሙበት ስፍራ ላይ መቆም ግዴታ ነው ብለው ማመናቸውና ለዛም ከአቅም በላይ መታገል።
ትክክሉ ግዴታ አይደለምም። ለርሱ መታገልም አልተደነገገም።
12. ወቅትን ማባከን፤ ዱዓና ዚክርን በመተው በማይጠቅም ነገር መጠመድ።
13. ዱዓ ለመጀመር ፀሐይ ልትገባ እስክትቀርብ ድረስ ወይም እስከቀኑ መጨረሻ ድረስ ማዘግየት።
14. ለዱዓ ለመቆም ከአቅሙ በላይ መታገል ይህንንም ሱና ብሎ ማሰብ ወይም ዓረፋ መቆም የሚባለው ለዱዓ መቆም ነው ብሎ ማሰብ።
ትክክሉ በዓረፋ መቆም ማለት ዓረፋ ክልል ውስጥ ቆሞም ይሁን ወይም ቁጭ ብሎ፤ እየጋለበም ይሁን በእግሩ እየተራመደ በዛ ወቅት ቦታው ላይ መገኘቱ ነው።
15. ፀሐይ ከመግባቱ በፊት ዓረፋን ለቆ መውጣት።
ይህ የነቢዩን የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና ሱና የሚቃረን ስለሆነ ክልክል ነው።
16. ፀሐይ ከገባ በኋላ ያለምክንያት ዓረፋን ለቆ ከመውጣት መዘግየት።
ምክንያት እስከሌለ ድረስ ፀሐይ ከገባ በኋላ በቀጥታ ዓረፋን ለቆ ለመውጣት መቻኮል ሱና ነው።
17. አንዳንዶች የዓረፋ መቆምን በጁሙዓ ቀን መፈፀም ከሰባ ሐጅ ጋር ይስተካከላል ብለው ማመናቸው።
ለዚህ ግን ምንም ማስረጃ የለም።
***
ሶስተኛ: ሰዎች ወደ ሙዝደሊፋ በሚጓዙበትና እዛው በሚያድሩበት ወቅት የሚፈፅሟቸው ተቃርኖዎች እና ስህተቶች:
1. ከዓረፋ ወደ ሙዝደሊፋ በሚንቀሳቀሱበት ወቅት መቻኮልና ሰዎችን በመኪና ማስበርገግ።
ሱናው በእርጋታ፤ በስክነትና ምንም ሰውን ሳያውኩ መጓዝ ነው።
2. አንዳንድ ሰዎች ሙዝደሊፋ ለማደር መታጠብ የተደነገገ አድርገው ማሰባቸው።
ይህ መደንገጉን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም።
3. አንዳንድ ሰዎች እየጋለበ ያለ ሰው ወደ ሙዝደሊፋ በእግሩ እየተራመደ ለመግባት መውረድ ይወደድለታል ብለው ማሰባቸው።
ይህ መደንገጉን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም።
4. የሙዝደሊፋ ክልል ውስጥ ያለ መሆኑን ሳያረጋግጡ መውረድ።
5. ሙዝደሊፋ መጀመሪያ እንደወረዱ ሶላት ለመስገድ መቻኮልን መተው።
ሱናው ሙዝደሊፋ እንደደረሱ በፍጥነት ሶላት ለመስገድ መቻኮል ነው።
6. ሙዝደሊፋ እንደገቡ በቅድሚያ ጠጠር በመሰብሰብ መጠመድና ጠጠር ለመሰብሰብ መጣር ይህንንም የተደነገገ አድርጎ ማሰብ።
ይህን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም።
7. መግሪብና ዒሻን ሶላት ወቅታቸው እስኪወጣ ድረስ ማዘግየት፤ ወቅታቸው የሚወጣውም የሌሊቱ አጋማሽ ላይ ነው።
ግዴታው ሙዝደሊፋ ሳይደርስ እንኳ ቢሆን የመግሪብና የዒሻን ሶላት ከሌሊቱ አጋማሽ በፊት መስገድ ነው።
8. የሙዝደሊፋን ምሽት በሶላት ወይም በአምልኮ ወይም በዛዛታና በጨዋታ ማሳለፍ።
ሱናው ነቢዩን የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና በመከተል የዒድ ቀን ለሚጠብቁት ተግባራት እንዲያግዘው ለመተኛትና ለማረፍ መቻኮል ነው።
9. ደካሞችና እነርሱን የሚንከባከቡ (የሚጎዳኙ) ሰዎች ከሌሊቱ አጋማሽ በፊት ሙዝደሊፋን ለቀው መውጣታቸው።
ግዴታው ከሌሊቱ አጋማሽ በኋላ ካልሆነ በቀር አለመውጣታቸው ነው።
10. አቅመ ደካማ ያልሆኑና አብረዋቸውም ደካሞች የሌሉ ሰዎች ከንጋት በፊት (ሙዝደሊፋን) ለቀው መውጣታቸው።
ግዴታው እስከ ፈጅር ድረስ ሙዝደሊፋ መቆየት ነው።
11. ፀሐይ እስክትወጣ ድረስ ከሙዝደሊፋ ለቆ ሳይወጡ መዘግየት።
ሱናው ፀሐይ ከመውጣቷ በፊት ሙዝደሊፋን ለቆ መውጣት ነው።
***
አራተኛ: በእርድ ቀን ተግባራት ላይ ሰዎች የሚፈፅሟቸው ተቃርኖዎችና ስህተቶች
1. አንዳንዶች ጠጠር ለመወርወር ገላን መታጠብ የተደነገገ አድርገው ማሰባቸው።
ይህ መደንገጉን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም።
2. የሚወረወረውን ጠጠር ማጠብ።
ይህ መደንገጉን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም።
3. ከሙዝደሊፋ የተለቀመ ጠጠር ካልሆነ በቀር በሌላ ጠጠር መወርወር አይበቃም ብሎ ማመን።
ይህን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም። ጠጠሮቹን ከፈለገው ስፍራ መልቀም ይችላል።
4. ከጠጠር ውጪ ያለን ነገር መወርወር ወይም ትላልቅ ድንጋዮችን መወርወር።
ይህ የነቢዩን የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና መመሪያ የተቃረነ ነው።
5. ጠጠር በሚወረውር ወቅት መቆጣትና የምንወረውረው ወደ ሸይጧን ነው ብሎ ማመን።
ወደ መወርወሪያ በሚጓዝበት ወቅት በህብረት እጅ ለእጅ ተያይዞና እርስበርስ ተሳስሮ መጓዝ እንዲሁም ሰዎችን ማወክ።
7. በሚወረውርበት ወቅት የሚያወሳው ዚክር (ውዳሴ) ላይ ከተደነገገው ዚክር ውጪ ያለን መጨመር።
በላጩ ተክቢራን ብቻ በማለት መቆጠብ ነው።
8. ሰባቱን ጠጠሮች በአንድ ጊዜ መወርወር።
እንዲህ ካደረገ አንድ ጊዜ ብቻ እንደወረወረ ተደርጎ ነው የሚቆጠረው፤ ግዴታው እያንዳንዱን ጠጠር አንድ በአንድ ነጣጥሎ መወርወር ነው።
9. ጠጠሮቹን ሳይወረውር ጉድጓዱ ውስጥ ሂዶ መጣል።
ይህ አይበቃም። የተደነገገው በትንሹ ቢሆን እንኳ መወርወር ተብሎ በሚጠራ ያህል መወርወር ነው።
10. በሚወረውር ወቅት የቆመውን ግድግዳ ለመምታት አስቦ መወርወርና ዋናው በመወርወር የተፈለገው እርሱን መምታት መሆኑን ማሰብ።
የተደነገገው የቆመውን ግድግዳ ባይነካ እንኳ ጉድጓዱ ውስጥ መጣል ነው።
11. ከሩቅ ሆኖ መወርወርና ጠጠሩ የሚወረወርበት ጉድጓድ ውስጥ ማረፉን አለማረጋገጥ።
12. ጀምረተል ዓቀባ ዘንድ ከወረወሩ በኋላ ለዱዓ መቆም።
ይህ ያልተደነገገ ነው። ይህ መደንገጉን የሚጠቁምም ምንም ማስረጃ የለም።
13. ከእርድ ቀን በፊት የተመቱዕና የቂራንን እርድ ማረድ።
ይህንን የፈፀመ ሰው አይበቃለትም። እርዱንም በሸሪዓ በተወሰነለት ወቅት ድጋሚ ማረድ ግዴታው ይሆንበታል። ለማረድ የተወሰነው ቀን ከዒድ ቀን እስከ አያመ ተሽሪቅ መጨረሻ ድረስ ነው።
14. ከማረድ ይልቅ ለእርድ የሚያወጣውን ብር ሶደቃ ለመስጠት መፈለግ።
ይህንን የፈፀመም አይበቃለትም። ማረዱም ግዴታው ይሆናል።
15. የተወሰነውን የጭንቅላቱን ክፍል ብቻ መላጨት ወይም ማሳጠር።
ሱናው ጭንቅላትን ባጠቃላይ መላጨት ወይም ማሳጠር ነው።
16. ጦዋፈል ቁዱምን በማድረጉ ምክንያት ጦዋፈል ኢፋዷን ከማድረግ መብቃቃቱ ወይም ጦዋፈል ኢፋዷን ዓረፋ ከመቆምና ሙዝደሊፋ ከማደር በፊት አስቀድሞ ማድረግ።
ይህንን የፈፀመ ሰው አይበቃለትም። ጦዋፈል ኢፋዷ ከሐጅ ማዕዘናት መካከል አንዱ ነውና። እርሱ ካልተፈፀመ ሐጁ ትክክለኛ አይሆንም። እርሱንም ዓረፋ ከቆሙና ሙዝደሊፋ ካደሩ በኋላ ካልሆነ በቀር መፈፀም አይፈቀድም።
***
አምስተኛ: ሰዎች በሚና ቀናት (በአያመ ተሽሪቅ) ተግባራት የሚፈፅሟቸው ተቃርኖዎችና ስህተቶች
1. የሚወረውር ሰው በመተካትና በመወከል መሳነፍ።
በመሰረቱ ለመወከልና ለመተካት የሚያበቃ ቦታ የሚሰጠው ሸሪዓዊ ምክንያት ከሌለ በቀር አንድ ሐጅ አድራጊ በራሱ ነው መወርወር ያለበት።
2. ሌላ ሰው እንዲወረውርለት የወከለ ሰው የሐጅ ተግባራትና ቀናት ከመጠናቀቃቸው በፊት መጓዙ።
ይህ ስህተት ነው። ማድረግ ያለበት የሐጅ ተግባራት እስኪጠናቀቁ ድረስ እዛው ባለበት በሚና ወይም ባለበት ስፍራ መቆየት ነው። ከዚያም የመሰናበቻ ጦዋፍ አድርጎ ከዚያም ይሄዳል።
3. በአያመ ተሽሪቅ ቀናቶች ፀሃይ ወደ መግቢያዋ ከመዘንበሏ (ከዝሁር) በፊት መወርወር።
ሱናው ከዝሁር ወቅት በኋላ መወርወር ነው።
4. በሚወረውርበት ወቅት ሶስቱን ጠጠር መወርወሪያ ስፍራዎችን በቅደም ተከተላቸው አለመወርወር።
በቅደም ተከተል መወርወር ግዴታ ነው። በቅድሚያ "ጀምረተል ኡላ" (የመጀመርያው) ዘንድ ይወረውራል ቀጥሎ "ዉስጧ" (መካከለኛው) ዘንድ ቀጥሎ "ኩብራ" (ትልቁ) ማለትም "ጀምረተል ዓቀባ" ዘንድ ይወረውራል። በተቃራኒው የወረወረ ወይም አቃርኖ የወረወረ በቅደም ተከተል ድጋሚ የመወርወር ግዴታ አለበት። "ጀምረተል ኡላ (ሱግራ)" ዘንድ የወረወረው ይቆጠርለታል ከርሱ ቀጥሎ ያለውን ግን ይደግማል።
5. ጀምረተል ዓቀባ (የመጨረሻው) ዘንድ ከወረወረ በኋላ ለዱዓ መቆም።
ሱናው ጀምረተል ኡላና ዉስጧ (የመጀመርያውና የመካከለኝው) ዘንድ ከወረወረ በኋላ ብቻ ለዱዓ መቆም ነው።
***
ስድስተኛ: ሰዎች በመሰናበቻ ጦዋፍ (ጦዋፈል ወዳዕ) ወቅት የሚፈፅሟቸው ተቃርኖዎች እና ስህተቶች
1. ጠጠር ከወረወረ በኋላ ቀጥታ ወደ ሃገሩ ለመጓዝ ጦዋፈል ወዳዕን ከመጨረሻው ቀን ጠጠር ውርወራ አስቀድሞ ማድረግ።
ይህ ስህተት ነው። ይህንን የፈፀመ ሰው ያለወቅቱ ስላደረገ አይበቃለትም። ጠጠር ከወረወረ በኋላም መድገሙ ግዴታው ነው።
2. ጠጠር የሚወረውርለትን ወክሎ ተወካዩ ጠጠር ከመወርወሩ በፊት ጦዋፍ ማድረግ።
ትክክለኛው ተወካዩ ጠጠር እስኪወረውርለት ድረስ መጠበቅና እንደወረወረለትም ጦዋፈል ወዳዕን ያደርጋል።
3. ጀርባ ሰጥቶ ላለመሄድ ሲል ካዕባን ለማላቅ ፊቱን ሆን ብሎ ወደ ካዕባ አድርጎ ወደ ኋላ መሄድ።
ይህ መደንገጉን የሚጠቁም ምንም ማስረጃ የለም። ምርጡ መመሪያ የሙሐመድ የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና መመሪያ ነው።
4. ከመስጂደል ሐራም በሚወጣ ወቅት ለዱዓ መቆም።
ይህ ምንም ማስረጃ የለውም።
5. ጦወፈል ወዳዕን ካጠናቀቁ በኋላ ሸሪዓዊ ቦታ ከሚሰጠው ምክንያት ውጪ መካ ውስጥ ረጅም ቆይታ ማድረግ።
ማድረግ ያለበት ግዴታ ከጦዋፈል ወዳዕ በኋላ ከመካ ለመውጣት መቻኮል ነው። ጓደኞችን ለመጠበቅ ወይም ለጉዞ የሚያስፈልገውን እቃ ለመግዛትና ለመሳሰሉት መቆየት ግን ችግር የለውም።
ያለበቂ ምክንያት ረጅም ወቅት ከቆየ ጦዋፈል ወዳዕን የመድገም ግዴታ ይኖርበታል።
የነቢዩን መስጂድ ከመዘየር ጋር ተያይዘው የሚፈፀሙ ስህተቶችና ተቃርኖዎች
1. የመልክተኛውን (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ቀብር በሚዘየርበት ወቅት በረከትን በመፈለግ ግድግዳዎችንና የቆሙ ብረቶችን (ፖሎችን) መተሻሸት፤ አጥሮቹ ላይ ገመዶችንና የመሳሰሉትን መቋጠር።
በረከት የሚፈለገው በአዲስ መጤ (በቢድዓ) ሳይሆን አላህና መልክተኛው (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በደነገጉት መንገድ ነው።
2. ኡሑድ ተራራ ላይ ወደሚገኙ ዋሻዎች መሄድ፤ በተመሳሳይ መካ ውስጥ ወደሚገኙት ወደ ሒራ ዋሻና ወደ ሠውር ዋሻ መሄድ እዛም ጨርቅ ማሰር፤ እዛም አላህ ያልፈቀደውን ዱዓ ማድረግና ለዚህም ብሎ ችግሮችን መጋፈጥ።
እነዚህ የተጠቀሱት ባጠቃላይ ንፁህ በሆነው ሸሪዓ መሰረት የሌላቸው አዲስ መጤ ቢድዓ ናቸው።
3. የአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ፋና አለባቸው ብለው የሚሞግቱትን ለምሳሌ ግመላቸው ያረፈችበትን ስፍራ፤ የኻቲምን ኩሬ ወይም የዑሥማንን ኩሬና የመሳሰሉትን አንዳንድ ስፍራዎች መዘየር፤ በረከትን ፍለጋም አፈርን ከነዚህ ስፍራዎች መውሰድ።
4. የበቂዕ መቃብር ስፍራንና የኡሑድ ሰማዕታት መቃብር ስፍራን በሚዘይርበት ወቅት ሟቾቹን መለመን፤ ወደ አላህ ለመቃረብና በሟቾቹ በረከትን ለማግኘት ብር ወደ መቃብሩ መወርወር።
እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ከትላልቅ ስህተቶች የሚመደቡ ናቸው። ይልቁንም የእውቀት ባለቤቶች እንደጠቀሱት የአላህ መጽሐፍና የመልክተኛው (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሱናም እንደሚያሳየው ከትላልቁ ሺርክ የሚመደብ ነው። አምልኮ ለአላህ ብቻ ነው የሚሰጠው ከአምልኮ መካከል ለምሳሌ ዱዓ፣ እርድ፣ ስለትና የመሳሰሉትን አንዳቸውንም ከአላህ ውጪ ለሆነ አካል መስጠት አይፈቀድምና። ይህም አላህ እንዲህ ስላለ ነው: "አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ አጥሪዎች፤ ቀጥተኞች ሆነው ሊግገዙት እንጂ ያልታዘዙ ሲሆኑ (ተለያዩ)" [አል-በይናህ፡ 5]
የአላህ ሶላትና ሰላም በነቢያችን ሙሐመድ ላይ ይስፈን።