أحكام الهدي والأضاحي والتذكية

أحكام الهدي والأضاحي والتذكية

ሀድይ፣ ኡዱሒያና እርድን የተመለከቱ ህግጋት

Language: lang_am
Prepared by: በመስጂደል ሐረም እና በመስጂድ አን-ነበዊይ የእስላማዊ አስተምህሮቶችን በተለያዩ ቋንቋዎች አገልግሎት ማህበር የዕውቀት ዘርፍ ኮሚቴ
Version: 1.2
Translations 18
Amharic Bengali English Persian +14
Attachments 7
PDF
Audio
Video
+3

ሀድይ፣ ኡዱሒያና እርድን የተመለከቱ ህግጋት

መግቢያ

ምስጋና ለአለማት ጌታ ለአላህ የተገባ ነው። የአላህ ሰላትና ሰላም የዓለማት እዝነት ተደርገው በተላኩት ነቢይ፣ በቤተሰቦቻቸው፣ በባልደረቦቻቸውና እስከ ዕለተ ትንሳኤ የርሳቸውን ሱንና (ፈለግ) በተከተሉና በመመሪያቸው በተመሩ ላይ ሁሉ ይስፈን። ከዚህ በመቀጠል:

ይህቺ አጠር ያለች መልእክት አንድ ሙስሊም ስለ ስለ ሀድይ (ለሐጅና ዑምራ የሚቀርብ መስዋዕት)፣ ኡዱሒያና ስለ እርድ ህግጋት እጅግ በጣም የሚያስፈልገውን ነጥቦች አካታ የያዘች ናት። ያጠናቀርነውም ሁለቱን የተከበሩ ሐረሞች ለሚዘይሩ ወንዶችና ሴቶች ሲሆን ሃይማኖታቸውን በዕውቀትና በግልፅ መረጃ ላይ ሆነው እንዲይዙ በማሰብ ነው። ቸርና ለጋስ የሆነው አላህ ጠቃሚ ሊያደርጋት፣ ለርሱ ብቻ የተሰራች በጎ ስራ ያደርግልን ዘንድ እንማፀነዋለን። እነሆ ቢለምኑት ደግ ተስፋ ቢያደርጉበት ቸር እርሱ ነውና።

የእስላማዊ አስተምህሮቶችን በተለያዩ ቋንቋዎች አገልግሎት ማህበር የዕውቀት ዘርፍ ኮሚቴ

የሀድይ (መስዋእት) እና የኡዱሒያ ህግጋት

ሀድይ (ለሐጅና ዑምራ የሚቀርብ መስዋዕት) ማለት: ከሶስቱ የቤት እንስሶችም (ግመል፣ ከብት፣ ፍየልና በግ) ሐረም ውስጥ መስዋዕት ለማድረግ የሚነዳ እርድ ሁሉ የሚገለፅበት ቃል ነው። ይህን ስያሜ የተሰጠውም ወደ አላህ መስዋእት ለማድረግ ስለሚነዳ ነው።

ኡድሒያ ወይም ኢድሒያ ማለት: ወደ አላህ ለመቃረብ ታስቦ በዒድ ዕለት እና በአያም አትተሽሪቅ (የዙልሒጃ ወር አስራ አንደኛ፣ አስራ ሁለተኛና አስራ ሦስተኛ ቀናት) የሚታረድ ነው።

ሀድይ እና ኡድሒያ የተደነገጉ እንደሆኑ ሙስሊሞች ባጠቃላይ ተስማምተውበታል።

በላጩ ሀድይ (መስዋእት): ለብቻው ሙሉውን አርዶ ከሰጠ ግመል ቀጥሎ ከብት ነው። ይህም ዋጋው ከፍ ያለና በስጋው መብዛት ድሃዎች ስለሚጠቀሙ ነው። ቀጥሎ በግና ፍየል ነው።

ከየሁሉም እንስሳ በላጩ ደግሞ የሰባውን ማረድ ነው። ቀጥሎ ዋጋው ከፍ ያለውን። ይህም የላቀው አላህ እንዲህ ስላለ ነው: "(ነገሩ) ይህ ነው፡፡ የአላህንም የሃይማኖት ምልክቶች የሚያከብር ሰው እርሷ ከልቦች የሆነች ጥንቃቄ ናት።" [ሱረቱ አል-ሐጅ : 32]

የሚታረዱት እንስሶችም በግ ከሆነ የሸረፈ ማለትም ስድስት ወር የሞላው ካልሆነ አይበቃም። ከበግ ውጪ ደግሞ: ግመል ከሆነ አምስት አመት የሞላው፣ ከብት ከሆነ ሁለት አመት የሞላው፣ ፍየል ከሆነ ደግሞ አንድ አመት የሞላው ካልሆነ አይበቃም።

ለሀድይ (መስዋዕት) ሲሆን ለአንድ ሰው በቂ የሚሆነው አንድ በግ ወይም ፍየል ነው። ለኡዱሒያ ሲሆን ግን አንድ በግ ወይም ፍየል ለአንድ ሰውና ለቤተሰቡ በቂ ይሆንለታል። አንድ ግመልና አንድ ከብት ለሀድይም ሆነ ለኡዱሒያ ለሰባት ሰው ይበቃቸዋል። ይህም ጃቢር ቢን ዐብደላህ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ እንዲህ ስላሉ ነው: "በሑደይቢያ ዓመት ከአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጋር አንድ ግመልን ለሰባት አርደናል፤ አንድ በሬንም ለሰባት አርደናል።" በሌላ ዘገባ: "ሐጅን ኢሕራም አድርገን ከአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጋር ወጣን። የአላህ መልክተኛም (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በግመልና በበሬ እርድ እንድንጋራ አዘዙን። ከኛ መካከል ለሰባት ለሰባት እየሆንን አንድ ግመል እንድናርድ አዘዙን።" በሌላ ዘገባም: "ከአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጋር ሐጅ አደረግን። (ከፊሎቻችን) አንድ ግመል ለሰባት፣ (ከፊሎቻችን ደሞ) አንድ በሬ ለሰባት አረድን።" [1] [1] (ሙስሊም ዘግበውታል)

እንዲሁም አቡ አዩብ አልአንሷሪይ (አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና) ባስተላለፉት ሐዲሥ አቡ አዪብ በአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ዘመን ኡዱሒያ በምን መልኩ ነበር የምታርዱት ተብለው የተጠየቁ ጊዜ እንዲህ በማለት መልሰዋል: "ሰውዬው ለራሱና ለቤተሰቡ አንድ በግ ወይም ፍየል ኡዱሒያን ያርድ ነበር። ለራሳቸውም ይበሉ ነበር። ሌላውንም ያበሉ ነበር። ሰዎች በመኩራራት አሁን ያሉበት ደረጃ (ለአንድ ቤተሰብ ከአንድ በላይ በግ ወይም ፍየል ማረድ) ላይ ከመድረሳቸው በፊት ኡዱሒያን የምናርደው በዚህ መልኩ ነበር።" [2] [2] (ቲርሚዚይ እና ኢብኑ ማጀህ ዘግበውታል)

አንድ ግመልን ወይም በሬን ለሰባት ከማረድ ለብቻው አንድ በግ ወይም ፍየል ማረዱ ይበልጣል።

ለሀድይም ይሁን ለኡዱሒያ ከበሽታ፣ ከአካለ ጎዶሎነትና ከክሳት የጠራ የሆነ እንስሳ ካልሆነ በቀር አይበቃም። ግልፅ በሆነ መልኩ አንድ አይኑ ወይም ሁለት አይኑ የታወረ፣ መቅኔዋ የተሟጠጠ ከሲታ፣ ከጤነኞቹ ጋር እኩል መጓዝ የማትችል አንካሳ፣ ጥርሶቿ ከሥሩ የወለቀ ወላቃ፣ በእርጅና ምክንያት ጡቶቿ ወተት ከመያዝ የደረቁ፣ በሽታዋ በግልፅ የሚስተዋል በሽተኛ እንስሳ ማረድ አይበቃም (አይቆጠርም)። በራእ ቢን ዐዚብ (አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና) ባስተላለፉት ሐዲሥ እንዲህ ብለዋል: «የአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በመካከላችን ቆሙና እንዲህ አሉ: "አራት አይነት እንስሶች ለኡዱሒያ አይበቁም። እውርነቷ ግልፅ የሆነ እውር፣ በሽታዋ ግልፅ የሆነ በሽተኛ፣ አንካሳነቷ ግልፅ የሆነ አንካሳና መቅኔ የሌላት ከሲታ ናቸው።"» [3] [3] (አቡዳውድ፣ ቲርሚዚይ፣ ነሳኢይና ኢብኑ ማጀህ ዘግበውታል)

ኢምም ቲርሚዚይ አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ ብለዋል: "ምሁራን ዘንድ ሲሰራበት የቆየው በዚሁ መልኩ ነው።" [4] [4] (ቲርሚዚይ ዘግበውታል)

የተመቱዕ ሀድይ እርድ እና የኡዱሒያ እርድ ወቅት በትክክለኛው የዑለማዎች አቋም ከዒድ ሶላት በኋላ ጀምሮ እስከ መጨረሻው አያመ ተሽሪቅ ድረስ ነው።

ያረደው የተመቱዕ ወይም የቂራን ሀድይ እርድ ከሆነ እንዲሁም ከኡዱሒያው እርድ መብላቱ ይወደዳል። ሶስት ቦታ ከፍሎም መመፅወትና ስጦታ መስጠት ይወደዳል። ይህም አላህ እንዲህ ስላለ ነው: {ከርሷም ብሉ። ችግረኛ ድሃንም አብሉ።} [ሱረቱል ሐጅ: 28]

(በሐጅ ወቅት ለተፈጠረ) ጉድለት መጠገኛ የሚታረድ ሀድይን በተመለከተ ግን: ማለትም በኢሕራም የተከለከሉን ክልከላዎች በመፈፀም ወይም የሐጅን ግዴታዎች በመተው ምክንያት የሚታረድ እርድ ከሆነ ከርሱ ምንም መብላት አይፈቀድም።

የኡድሒያን እርድ ማረድ የፈለገ ሰው የዙልሒጃ አስሩ ቀናት ሲገቡ ጀምሮ የኡድሒያውን እርድ እስኪያርድ ድረስ ከፀጉሩም ይሁን ከጥፍሩ ምንም አይቆርጥም። ይህም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው: "የዙልሒጃ አስሩ ቀናት የገቡ ጊዜና አንዳችሁ የኡድሒያን እርድ ማረድ ከፈለገ እርዱን እስኪያከናውን ድረስ ከፀጉሩም ይሁን ከጥፍሩ ምንም አይቁረጥ።" [5] [5] (ሙስሊም ዘግበውታል)

ከጥፍሩ ወይም ከፀጉሩ የቆረጠ ሰው አላህን ምህረት ይጠይቃል እንጂ ምንም የሚያወጣው ፊድያ (ማካካሻ) አይኖርም።

የሀድይ፣ የኡዱሒያና የሌሎችም እርዶች አስተራረድ በሚከተለው መልኩ ነው:

1 - ሙስሊም ሆኖ ነገሮችን የለየና የአይምሮ ጤነኛ የሆነ ሰው ካልሆነ በቀር ማረድ አይበቃለትም። ወይም (የሚያርደው) ከመጽሐፉ ሰዎች መሆን አለበት። አራጁ የሚያርድበትን ኒያ ለይቶ ማወቅ አለበት። ከአላህ ውጪ ለሆነ አካልም አይረድ። እርዱንም ከአላህ ውጪ የሆነን አካል በመጥራት አይረድ። ሲያርድም የአላህን ስም ይጥራ። ከጥርስና ከጥፍር ውጪ ባሉ ስለታማ መሳሪያዎች ይረድ። ደሙንም ባረደበት ቦታ ያፍስስ። አራጁ የግድ በሸሪዓ እንዲያርድ የተፈቀደለት መሆን አለበት። [6] [6] የኡዱሒያ ህግጋት በሸይኽ ሙሐመድ ቢን ዑሠይሚን (ገፅ 56 - 87)

2 - የኡዱሒያውን እርድ ይምረጥ። የተሟላ የሆነን የኡዱሒያ እንስሳ ለማረድም ጥረት ያድርግ። በርግጥም «የአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ለኡዱሒያ ሁለት ቡራቡሬና ቀንዳም የሆኑ ሙክቶችን በእጃቸው አረዱ። "ቢስሚላህ አላሁ አክበር" አሉና እግራቸውን አንገቱ ላይ አድርገው አረዱት።» [7] [7] (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል)

3 - የሚታረደውን እንስሳ በመልካም መልኩ ማረድ ያስፈልጋል። በሚያርደው ወቅት ቶሎ የሚገላግለውን መንገድ ሁሉ ይጠቀም። ከነዚህም መካከል: እርዱ ስለታማ በሆነ መሳሪያ መሆን አለበት። የተፈለገው እንስሳውን ሳያሰቃዩ በተሟላ መልኩ ነፍሱን ማውጣት ስለሆነ የሚታረደው ስፍራ ላይ በሃይልና በፍጥነት (በስለቱ) ማረድ አለበት። ሸዳድ ቢን አውስ (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ ስላሉ ነው: «ሁለት ነገሮችን ከአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሸምድጃለሁ። እርሳቸው እንዲህ ብለዋል: "አላህ በሁሉም ነገሮች ላይ ኢሕሳን (አሳምሮ ማድረግን) ጽፏል (ደንግጓል)። የገደላችሁም ጊዜ አገዳደላችሁን አሳምሩ፤ ያረዳችሁም ጊዜ አስተራረዳችሁን አሳምሩ። አንዳችሁ ቢላውን ይሞርድ እርዱንም ይገላግለው።" [8] [8] (ሙስሊም ዘግበውታል)

የምትታረደው እንስሳ እየተመለከተችው ቢላውን መሞረድ ይጠላል። ከኢብኑ ዑመር (አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና) እንደተላለፈው እንዲህ ብለዋልና: «ነቢዩ -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና - ቢላ መሞረድን አዘዋል። ሲሞረድ ከእንስሶች ደበቅ እንዲደረግም አዘዋል። እንዲህም ብለዋል: "አንዳችሁ ያረደ ጊዜ በሃይልና በፍጥነት ይረድ።"» [9] [9] (አሕመድና ኢብኑ ማጀህ ዘግበውታል)

4 - የኡድሒያው እርድ ግመል ከሆነ ግራ እጇ ታስሮ በቆመችበት ይወጋታል። ዐብደላህ ቢን ዑመር አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና ባስተላለፉት ሐዲሥ እንዲህ ስላሉ ነው: «ኢብኑ ዑመር አንድ ሰውዬ ግመሉን ሊያርዳት አንበርክኮ ሳለ መጡ። እንዲህም አሉት: "ታስራ እንድትቆም አድርጋትና ውጋት። የሙሐመድ -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና - ሱንና ይህ ነው።"» [10] [10] (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል)

5 - ለኡድሒያ የሚታረደው ከግመል ውጪ ከሆነ በግራ ጎኗ አጋድሞና እንዲመቸው እግሩን አንገቷ ላይ አሳርፎ ያርዳታል። አነስ አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና እንዲህ ስላሉ: «የአላህ መልክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ለኡዱሒያ ሁለት ቡራቡሬና ቀንዳም የሆኑ ሙክቶችን በእጃቸው አረዱ። "ቢስሚላህ አላሁ አክበር" አሉና እግራቸውን አንገቱ ላይ አድርገው አረዱት።» [11] [11] (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል)

6 - በእርድ ወቅት ቢስሚላህ ማለት ይገባል። ይህም ግዴታ ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏልና: (በአንቀጾቹም አማኞች እንደ ሆናችሁ (ሲታረድ) የአላህ ስም በእርሱ ላይ ከተወሳበት እንስሳ ብሉ፡፡) [ሱረቱል አንዓም: 118] አላህ እንዲህም ብሏል: "በእርሱም ላይ የአላህ ስም ካልተጠራበት ነገር አትብሉ፡፡ እርሱም በእርግጥ አመጽ ነው፡፡ ሰይጣናትም ወደ ወዳጆቻቸው (በክትን በመብላት) ይከራከሯችሁ ዘንድ ያንሾካሽካሉ፡፡ ብትታዘዙዋቸውም እናንተ በእርግጥ አጋሪዎች ናችሁ፡፡" [ሱረቱል አንዓም: 121] ነቢዩም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና - እንዲህ ብለዋልና: "ደምን ያፈሰሰና ሲታረድ የአላህ ስም የተወሳበትን በጥርስና በጥፍር እስካልሆነ ድረስ የታረደው ብሉ።" [12] [12] (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል)

በሚያርድ ወቅት ቢስሚላህ ካለ በኋላ አሏሁ አክበር ማለቱ ይወደዳል። ጃቢር አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና እንዲህ ብለዋልና: በዒድ መስገጃ ስፍራ ከአላህ መልክተኛ -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና - ጋር ተገኝቻለሁ። ኹጥባቸውን ያጠናቀቁ ጊዜ ከሚንበራቸው ወረዱ። ሙክትም መጣላቸው። የአላህ መልክተኛ -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና - በእጃቸው አረዱትና እንዲህ አሉ: «ቢስሚላሂ ወሏሁ አክበር ይህ ሙክት ለኔና ከኡመቴ የኡድሒያን እርድ ላላረደ ነው።» [13] [13] (አቡዳውድና ቲርሚዚይ ዘግበውታል። አልባኒም ሶሒሕ ብለውታል)

7 - የትንፋሽ መተላለፊያውን፣ የምግብ መተላለፊያውንና በአንገቱ ጎን ያሉትን ሁለቱን የደም መተላለፊያ ቧንቧዎችን በመቁረጥ ደሙን ማፍሰስ ይገባል፤ ኢማም ኢብኑ ባዝ አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ ብለዋል: (የግመል፣ የከብት፣ የፍየልና የበግ ሸሪዓዊው እርድ የሚፈፀመው በሶስት መልኩ ነው:

የመጀመሪያው: አራጁ የትንፋሽ መተላለፊያውን፣ የምግብ መተላለፊያውንና በአንገቱ ጎን ያሉትን ሁለቱን የደም መተላለፊያ ቧንቧዎችን በመቁረጥ ነው። ይህ የተሟላውና ምርጡ አስተራረድ ነው። እነዚህ አራት ቧንቧዎች ከተቆረጡ ሁሉም ዑለማዎች ዘንድ እርዱ ፍቁድ ነው።

ሁለተኛው: የትንፋሽ መተላለፊያውን፣ የምግብ መተላለፊያውንና በአንገቱ ጎን ያለውን አንዱን የደም መተላለፊያ ቧንቧዎችን በመቁረጥ ነው። ይህም ከመጀመሪያው ዝቅ ያለ አስተራረድ ቢሆንም ፍቁድ፣ ትክክለኛና ደህና እርድ ነው።

ሶስተኛው: ሁለቱን የደም መተላለፊያ ቧንቧዎችን በመተው የትንፋሽ መተላለፊያውንና የምግብ መተላለፊያውን ቧንቧዎች ብቻ በመቁረጥ ማረድ ነው። ይህም ትክክለኛ እርድ ነው። ይህንንም በርካታ ዑለማዎች ፍቁድ ነው ብለውታል። ማስረጃቸውም ተከታዩ የነቢዩ -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና - ንግግር ነው: "ደምን ያፈሰሰና ሲታረድ የአላህ ስም የተወሳበትን በጥርስና በጥፍር እስካልሆነ ድረስ የታረደው ብሉ።" [14] በዚህ ርዕስ ዙሪያ የተመረጠውም ይህ ነው። [15] [14] (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል) [15] የኢብኑ ባዝን መጅሙዕ ፈታዋ (18/26) ተመልከት።

ባወቅነው ተጠቃሚ እንድንሆንና የሚጠቅመንንም እንዲያሳውቀን የምንማፀነው አላህን ብቻ ነው። እነሆ እርሱ ቸርና ለጋስ ነውና። የአላህ ሰለዋትና ሰላም በርከት ብሎ በነቢዩ ሙሐመድ፣ በተከታዮቻቸውና በባልደረቦቻቸውም ላይ ሁሉ ይስፈን።