أسئلة وأجوبة عن شهر رمضان للصغار، ولا يستغني عنها الكبار
የረመዳን ወርን የተመለከቱ ጥያቄዎችና መልሶች ለህፃናት እና ለአዋቂዎች
የረመዳን ወርን የተመለከቱ ጥያቄዎችና መልሶች ለህፃናት እና ለአዋቂዎች
የእስልምናን አስተምህሮቶች በተለያዩ ቋንቋዎች አገልግሎት ማህበር
በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በሆነው
መግቢያ
ምስጋና ሁሉ የረመዳንን ወር ከሌሎች ወራትና ቀናት በብዙ ደረጃዎች ላላቀውና ልዩ ላደረገው አላህ ነው። የአላህን ሰላትና ሰላም በሙሐመድ ኢብኑ ዐብደላህ፣ በቤተሰቦቻቸውና በባልደረቦቻቸው ላይ ሁሉ እንዲሰፍን እንለምናለን። ከዚህ በመቀጠል፦
ይህ ስለ ረመዳን ወር የሚያትት ጥያቄና መልስ የተዘጋጀው ለልጆች ሲሆን አዋቂዎችንም ተጠቃሚ ማድረግ የሚችል ነው። የተባረከውን የረመዳን ወር አስመልክቶ ግዴታ የሚሆኑ፣ ተወዳጅ የሆኑና በረመዳን ወር ሊፈፀሙ የሚገቡ ርዕሰ ጉዳዮችን ይዳስሣል። አስተማሪው የሚፈልገውንና ለልጁ እና ለእድሜው ተስማሚ የሆነውን ይመርጣል።
የተከበሩ ሰሓቦች አላህ ሥራቸውን ይውደድላቸውና ልጆቻቸውን በልጅነታቸው እንዲፆሙ ያደርጉ ነበር። ይህም ከዚህ (ለአላህ ከሚደረግ) ታዛዥነት ጋር እንዲላመዱ ለማስቻል ነበር።
አር-ሩበይዪዕ ቢንት ሙአውዊዝ ብን ዐፍራእ (አላህ ሥራዋን ይውደድላትና) ባስተላለፈችው ሐዲሥ እንዲህ አለች፡- የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በዓሹራ ዕለት ጠዋት በመዲና ዙሪያ ወደሚገኙ የአንሷሮች መንደሮች እንዲህ ሲሉ ላኩ፦ "ከእናንተ መካከል ፆመኛ ሆኖ ያነጋ ፆሙን ይሙላ፤ ፆመኛ ሳይሆን ያነጋ ደግሞ የቀረውን የቀኑ ክፍል በፆም ያሳልፍ።" ከዚያም በኋላ እኛ እንፆመው ነበር፤ እንዲሁም እንደ አላህ ፈቃድ ትንንሽ ልጆቻችንንም እናጾማቸው ነበር። ወደ መስጂድ እንሄዳለን፤ ከዒህን (ከሱፍ) የተሠራ መጫወቻ እናዘጋጅላቸዋለን፤ አንዱ (እርቦት) ምግቡ ፈልጎ ሲያለቅስ ፉጡር እስኪደርስ ድረስ መጫወቻውን እንሰጠው ነበር።" (((ቡኻሪ 1960 እና ሙስሊም 1136 ላይ ዘግበውታል፤ የቃል አጠቃቀሙ የሙስሊም ዘገባ ነው። )))
በዚህ ሐዲሥ ሰሐቦች ለልጆቻቸው ቀለም ከተቀባ ሱፍ መጫወቻ ያዘጋጁላቸው እንደነበር ተጠቅሷል። ከልጆቹ መካከል አንዱ ምግብ ፈልጎ የሚያለቅስ ከሆነ እነዚህን መጫወቻዎች ይሰጡትና በጫወታ ውስጥ ሆኖ ረሀቡን እንዲረሳ ያደርጉት ነበር፤ ይህንንም የኢፍጣር ሰዓት እስኪደርስ ይጠቀሙት ነበር፤ ይህ ሁሉ ልጆችን በአምልኮ ላይ ለማበረታታት እና ለማሰልጠን ሲባል ነው።
ነገር ግን ህፃኑ ፆሙን መጨረስ እስከማይችልበት ደረጃ ድረስ ከደረሰ እንዲፆም መገደድ እንደሌለበት ልብ ሊባል ይገባል። ይህም ልጁ አምልኮን ለመጥላት ወይም ለመዋሸት ወይም ለህመሙ መባባስ ሰበብ እንዳይሆነው ለመጠንቀቅ ነው። (በመሠረቱ) ልጆች ሸሪዓዊ ትዕዛዛት ግዴታ የሚሆንባቸው ዕድሜ ላይ የደረሱ እስካልሆኑ እንዲፆሙ በጣም መጫን ተገቢ አለመሆኑ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል።
የመጽሐፉ ጥቅም የተሟላ እንዲሆን አዋቂዎች ማወቅ ያለባቸውን ጉዳዮች ጠቅሰናል፤ ልጆችን በሚያስተምርበት ጊዜም (እነሱን ስለማይመለከት) ለይተው እንዲያወጡት ((ለአዋቂዎች)) በሚል በቅንፎች መካከል በማስቀመጥ ጠቁመናል።
ጠቃሚ እንዲያደርገውና እንዲቀበለንም አላህን ብቻ እንለምነዋለን።
ጥያቄዎች እና መልሶች
የረመዳን ወር ምንድን ነው?
መ፡ የረመዳን ወር የዓመቱ ምርጥ ወር ነው። በጨረቃ የዓመት አቆጣጠር ዘጠነኛው ወር ነው። ወሩን መፆም ከአምስቱ የእስልምና መሰረቶች መካከል አንዱ ነው።
ከኢብኑ ዑመር (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- «እስልምና በአምስት መሰረቶች ላይ ተገንብቷል: ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ አለመኖሩን እና ሙሐመድም የአላህ ባሪያና መልዕክተኛ መሆናቸውን መመስከር፣ ሶላትን ደንብና ስርዓቱን ጠብቆ መስገድ፣ ዘካን መስጠት፣ የረመዳንን ወር መፆም እና ሐጅ ማድረግ ናቸው።» (((ቡኻሪይ፡ በቁጥር 8 እና ሙስሊም፡ በቁጥር 16 ላይ ዘግበውታል)))
የረመዳንን ወር መፆም ግዴታ ነውን?
መ፡- አዎ! የረመዳንን ወር መፆም ከእስልምና መሰረቶች መካከል አንዱ በመሆኑ መፆሙ ግዴታ ነው።
ማስረጃውም የኃያሉ አላህ ንግግር ነው፦ "እናንተ ያመናችሁ ሆይ ፆም በነዚያ ከናንተ በፊት በነበሩት (ሕዝቦች) ላይ እንደ ተጻፈ በናንተም ላይ ተጻፈ (ተደነባ) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡" (አልበቀራህ፡ 183)
"በናንተም ላይ ተጻፈ" ማለትም፡ በናንተ ላይ ግዴታ ተደረገ።
ቀጣዩ የኃያሉ አላህ ንግግርም ሌላው ማስረጃ ነው፦ (ከእናንተም ወሩን ያገኘ ሰው ይጹመው።) (አልበቀራህ፡ 185)
ፆም ምንድን ነው?
መ፡ የበላይ የሆነውን አላህ ለማምለክ በመነየት (ቁርጠኛ ልባዊ ውሳኔ በመወሰን) ፀሐይ ከወጣችበት ጊዜ ጀምሮ እስክትጠልቅ ድረስ ከመብላት ከመጠጣትና ከሌሎች ፆምን ከሚያበላሹ ነገሮች ሁሉ መታቀብ ነው።
ማስረጃውም የኃያሉ አላህ ንግግር ነው፦ (ከጎህ የሆነው ነጩ ክርም ከጥቁሩ ክር (ከሌሊት ጨለማ) ለእናንተ እስከሚገልጽላችሁ ድረስ ብሉ፤ ጠጡም፡፡ ከዚያም ፆምን እስከ ሌሊቱ ድረስ ሙሉ።) (አልበቀራህ፡ 187)
ማለትም: እውነተኛው ንጋት በንጋቱ ንጣት ከሌሊቱ ጥቁረት በመለየት እስኪገለጽላችሁ ድረስ በሌሊቱ ክፍለ ጊዜ መብላትና መጠጣት ተፈቅዶላችኋል፤ ከዚያም ከፀሐይ መውጣት ጀምሮ ጀንበር እስክትጠልቅ ድረስ ፆምን ከሚያበላሹ ነገሮች በመከልከል ፆሙን ሙሉ ማለት ነው።
የረመዳን ወር ትሩፋቶች ምንድን ናቸው?
የረመዳን ወር ትሩፋቶች በጣም ብዙ ናቸው፤ ከእነርሱም መካከል፦
1- ይህ ወር የተከበረው ቁርኣን የተወረደበት ነው፤ የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ "(እንድትጾሙ የተጻፈባችሁ) ያ በርሱ ውስጥ ለሰዎች መሪ ከቅን መንገድና (እውነትን ከውሸት) ከሚለዩም ገላጮች (አንቀጾች) ሲሆን ቁርኣን የተወረደበት የረመዳን ወር ነው።" (አልበቀራህ፡ 185)
2- የጀነት በሮች የሚከፈቱበት ወር ነው።
3- የጀሀነም በሮች የሚዘጉበት ወር ነው።
4- ሸይጣኖች በሰንሰለት የሚታሠሩበትና የሚጠፈነጉበት ጊዜ በመሆኑ በሌላው ጊዜ ሙስሊሞችን ለመፈታተን የሚያገኙትን ያህል እድል አያገኙም።።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- «የረመዳን ወር በገባ ጊዜ የጀነት በሮች ይከፈታሉ፤ የጀሀነም በሮችም ይዘጋሉ፤ ሰይጣናትም ይታሰራሉ።» (((ቡኻሪይ፡ በቁጥር 3277 እና ሙስሊም፡ በቁጥር 1079 ላይ ዘግበውታል)))
5- በዚህ ወር ውስጥ በእምነትና የአላህን ምንዳ በመሻት በሰላት ቆመው ላሳለፉ አማኞች ከሺህ ወራት በላጭ የሆነችው ለይለቱል ቀድር (መወሰኛይቱ ሌሊት) አለች። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ "መወሰኛይቱ ሌሊት ከሺሕ ወር በላጭ ናት።" (አልቀድር፡ 3)
6- አንድ ሰው ወደ ኃያሉ አላህ ከሚያቃርቡት ተግባራት መካከል ትልቁና በላጭ የሆነውን ፆም በግዴታነት በዚህ ወር እንዲፆም አላህ መረጠው።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንደተላለፈው፣ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ሲሉ ሰማው፡- «አሸናፊና ኃያል የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል: "ፆም ሲቀር የሰው ልጅ የሚሠራው መልካም ስራ ሁሉ ለራሱ ነው፤ ፆም ግን (በእኔና በባሪያዬ መካከል ያለ ምስጢር ስለሆነ) የእኔ ነው፤ እኔ ነኝ ምንዳውን የምለግሰው፤ የሙሐመድ ነፍስ በእጁ በሆነችው አላህ እምላለሁ የፆመኛ አፍ ጠረን አላህ ዘንድ ከሚስክ (ምርጥ) ሽቶ በላይም ያውዳል።» (((ቡኻሪ በቁጥር 1904 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ዘግበውታል)))
“የፆመኛ አፍ ጠረን” ማለት፡- (በፆሙ ምክንያት ሆዱ ባዶ ሲሆን) የሚቀየረውን የአፉ ጠረን ነው።
7- በዚህ ወር ውስጥ ለአላህ ብሎ የፆመ እና የሰገደ ሰው ያለፈው ወንጀሉ ይማርለታል።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "(ግዴታነቱን) አምኖ እና ምንዳውን ከአላህ አስቦ የረመዳንን ወር የፆመ ሰው ያለፈ ወንጀሉ ይማርለታል።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 38 እና ሙስሊም በቁጥር 760 ላይ ዘግበውታል)))
በሌላም ሐዲሥ፦ "(በአላህ) አምኖ እና ምንዳውን ከአላህ አስቦ የረመዳንን ወር በሰላት ያሳለፈ ያለፈ ወንጀሉ ይማርለታል።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 37 እና ሙስሊም በቁጥር 759 ላይ ዘግበውታል)))
"ኢማነን/ አምኖ" ማለት፡- በአላህ አምኖና ኃያሉ አላህ የደነገገው ግዴታ መሆኑን ተቀብሎ።
"ኢሕቲሳበን" ማለትም፡ ከኃያሉ አላህ ምንዳን ፈልጎ እንጂ ለይዩልኝ ወይም ሌላ ከኢኽላስ (ለአላህ ብቻ ብሎ አጥርቶ ከመሥራት ጋር) የሚጻረር ነገር ፈልጎበት መሆን የለበትም።
8- በረመዳን የሚደረግ ዑምራ ያለው ምንዳ የሐጅ ምንዳ ያህል ነው።
ከኢብኑ ዐባስ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "በረመዳን የሚደረግ ዑምራ ከሐጅ ጋር እኩል ነው፤ ወይም ከእኔ ጋር ሐጅ እንደማድረግ ነው።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 1863 እና ሙስሊም በቁጥር 1256 ላይ ዘግበውታል)))
"ከሐጅ ጋር እኩል ነው" ማለት፡- ምንዳው ከሐጅ ምንዳ ጋር እኩል ነው።
9- (በረመዳን) ፆመኛን ያስፈጠረ ሰው የፆመኛውን ያክል ምንዳ ይኖረዋል።
ከዘይድ ኢብኑ ኻሊድ አል-ጁሃኒ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንደተላለፈው፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ፆመኛን ያስፈጠረ ሰው ከፆመኛው ምንም ምንዳ ሳይቀነስበት የፆመኛውን ያክል ምንዳ ይኖረዋል።" (((አት-ቲርሚዚይ፡ 807 እና ኢብኑ ማጃህ፡ 1746 ላይ ዘግበውታል)))
10- አላህ በዚህ ወር እያንዳንዱ ሌሊት ከጀሀነም እሳት ነጻ የሚያወጣቸው ባሮች አሉት።
ከጃቢር ብን ዐብደላህ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንደተላለፈው፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "አላህ በእያንዳንዱ (የረመዳን ቀን) የፉጡር ወቅት ነፃ የሚያወጣቸው ባሮች አሉት፤ ይህ ደግሞ ሁሌም በየምሽቱ ነው።" (((ኢብኑ ማጃህ በቁጥር 1643 ላይ ዘግበውታል)))
11- የረመዳንን ወር መፆም ከባባድ ወንጀሎችን ለራቀ ሰው ካለፈው ረመዳን እስከዚህኛው ረመዳን ድረስ የሠራቸው (ትናንሽ) ወንጀሎች ይቅር እንዲባሉለት ምክንያት ይሆናል።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ከትላልቅ ወንጀሎች ለራቀ ሰው አምስቱ (የግዴታ) ሶላቶች፤ ከአንዱ ጁምዓ እስከ ቀጣዩ ጁምዓ እንዲሁም ከአንዱ ረመዳን እስከ ሌላኛው ረመዷን በመካከላቸው ላለው (ትናንሽ) ወንጀሎች ማስማሪያ ናቸው።" (((ሙስሊም ዘግበውታል፡ 233)))
ትላልቅ (ከባባድ) ኃጢአቶች ከሆኑ ግን ተውበት (ንስሐ) ያስፈልጋቸዋል።
በአጠቃላይ የረመዷን ወር የአምልኮ፣ የጽድቅ፣ የልግስና፣ የእዝነት፣ የምህረት እና ከጀሀነም እሳት ነጻ መውጫ ወር መሆኑን የቁርኣንና ሐዲሥ ማስረጃዎች ያመለክታሉ።
የፆም ምንዳዎች ምን ምን ናቸው?
መ፡- ፆም ከሚያስገኛዎች ምንዳዎች መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፦
1- ከሌሎች መልካም ስራዎቹ ሁሉ በተለየ መልኩ አላህ ከእርሱ ዘንድ ልዩ የሆነን ምንዳ ይከፍለዋል።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) (አላህ) እንዲህ (ማለቱን) ነግረውናል፡- «ፆም ሲቀር የሰው ልጅ የሚሠራው መልካም ስራ ሁሉ ለራሱ ነው፤ ፆም (በእኔና በባሪያዬ መካከል ያለ ምስጢር ስለሆነ) የእኔ ነው፤ እኔ ነኝ ምንዳውን የምለግሰው።» (((ቡኻሪ በቁጥር 1904 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ዘግበውታል)))
2- ፆም ጋሻ ነው ማለትም፡- ከእሳት መከላከያና መጠበቂያ ነው።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ጾም ጋሻ ነው።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1904 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ዘግበውታል)))
3- የፆመኛ አፍ ጠረን - በፆም ምክንያት የሚከሰት መጥፎ የአፍ ሽታ - አላህ ዘንድ ከሚስክ (ከምርጥ ሽቶ) መዓዛ ይበልጣል።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- «የሙሐመድ ነፍስ በእጁ በሆነችው (አላህ) እምላለሁ የፆመኛ አፍ ጠረን በዕለተ ቂያማ (የፍርዱ ቀን) አላህ ዘንድ ከሚስክ (ከምርጥ ሽቶ) በላይ ያውዳል።» (((ቡኻሪ በቁጥር 1894 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ላይ ዘግበውታል)))
4- ለፆመኛ ሁለት የደስታ ጊዜዎች አሉት።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ለፆመኛ ሁለት የደስታ ጊዜዎች አሉት፤ ሲያፈጥር የሚያገኘው ደስታ እና ጌታውን ሲገናኝ የሚያገኘው ደስታ ናቸው።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1904 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ዘግበውታል)))
5- ጀነት ውስጥ ፆመኞች ብቻ የሚገቡበት በር አለ።
ከሰህል (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "በጀነት ውስጥ አር-ረያን የሚባል በር አለ፡ በቂያማ ቀን ፆመኞች ብቻ በዚህ በር ይገባሉ፤ ከነርሱ በቀር ማንም አይገባበትም፤ ፆመኞች የት አሉ? ይባላል፤ ይቆማሉ ከነሱ በቀር ማንም አይገባበትም፤ ከገቡ በኋላ ይዘጋል፤ ከዚያም ማንም አይገባባትም።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1896 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ዘግበውታል)))
6- ፆመኛ የሚያደርገው ዱዓ ምላሽ አያጣም (ተቀባይነት ያገኛል)።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ሶስቱ ዓይነት ሰዎች ዱዓቸው ምላሽ አያጣም፡ (ከነሱም መካከል) ፆመኛ ሰው እስኪያፈጥር ድረስ የሚያደርገው ዱዓእ አንዱ ነው።" (((ቲርሚዚይ በቁጥር 3598 ዘግበውታል)))
የፆም ጥበብና ጥቅሙ ምንድን ነው?
መ፡- ፆም ብዙ እና ታላላቅ ጥበቦች አሉት፡ ከነዚህም መካከል፡-
1- ከፆም ታላላቅ ጥበቦች መካከል አንዱና ዋነኛው አላህ (በተከበረ ቃሉ) የጠቀሰልን ነው፤ እርሱም ፆም ተቅዋ (ፈሪሀ አላህነትን) የማስገኘት መንገድ ነው። ተቅዋ (አላህን መፍራት) ማለት፦ አላህ ያዘዘውን መፈፀም እና የከለከለውን መተው ነው።
አላህ እንዲህ ብሏል፦ "እናንተ ያመናችሁ ሆይ ፆም በነዚያ ከናንተ በፊት በነበሩት (ሕዝቦች) ላይ እንደ ተጻፈ በናንተም ላይ ተጻፈ (ተደነባ) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡" (አልበቀራህ፡ 183)
2- ፆም የሰውን ልጅ የነገሩ ሁሉ መሰረት (ቁልፍ) የሆነውን ትዕግስት ያስተምራል። ትዕግስት ሦስት ዓይነት ነው፦ አላህ ያዘዘን ነገር በመፈፀም ላይ ትዕግስት ማድረግ። አላህ የከለከለውን ነገር በመራቅ ላይ መታገስ እና በቀደር (በአላህ ውሳኔዎችን) በትዕግስት መቀበል ነው።
3- ከረመዳን ፆም ጥቅሞች መካከል፡-ፆም መላ ማህበረሰቡ ኃያሉን አላህ በአንድነት ማምለኩን የሚያሳይበት ነው።ለዚህም የረመዳንን ወር ለመፆም ከምስራቅ እስከ ምዕራብ ያሉ ሙስሊሞች በሙሉ አንድ ሆነው ታገኛላችሁ።
4- መታዘዝን እና አምልኮን መላመድ፤ በተለይም ደግሞ ፆምን መላመድ።
5- ለአላህ ብሎ ነገሮችን መተውን መላመድ።
6- ፆመኛ የአላህን ፀጋዎች በደንብ እንዲረዳ ያደርገዋል፤ ከእነዚህም የምግብና የመጠጥ በረከቶች ይጠቀሳሉ።
7- ፆም ፆመኛ የሆነን ሰው ለደካሞች፣ ለድሆችና ለችግረኞች እንዲራራ ያደርጋል። ምክንያቱም እርሱም የረሃብን ስሜት ቀምሶታልና።
8- ፆም የሰይጣንን ውስወሳው እና ተጽዕኖ ያዳክማል።
9- ፆም በኢኽላስ እና የአላህን ቅርብ ተቆጣጣሪነት በመገንዘብ ላይ ያንፃል። የአላህን ቅርብ ተቆጣጣሪነት ማሠቡ እንጂ ፆመኛውን ከመብላትና ከመጠጣት የሚከለክለው ምንም ነገር የለም።
10- በሕክምና ጠበብቶች እንደተረጋገጠው ፆም ለሰውነት ጤና እና ጥንካሬ ይሰጣል።
ፆምን የሚያበላሹ ነገሮች ምን ምን ናቸው?
መ፡ 1- በረመዳን የቀኑ ክፍለ ጊዜ ሆነ ብሎ መብላት ወይም መጠጣት፤ ምክንያቱም የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏልና፡- "ከዚያም ፆምን እስከ ሌሊቱ ድረስ ሙሉ።" (አል'በቀራህ፡ 187)
ረስቶ የበላ ወይም የጠጣ ሰው ፆሙ ትክክለኛ ነው። ፆመኛ መሆኑን ካስታወሰ ወይም ሌላ ሰው ካስታወሰው ግን መብላትና መጠጣቱን ማቆም አለበት። ምክንያቱም ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋልና፡- "ፆመኛ መሆኑን ረስቶ የበላ ወይም የጠጣ ፆሙን ይሙላ (ይቀጥል)፤ ምክንያቱም ያበላውና ያጠጣው አላህ ነውና።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1933 እና ሙስሊም በቁጥር 1155 ዘግበውታል)))
2- አውቆ ማስመለስ፡ ማስመለስ ማለት፡ ሆድ ውስጥ ያለን ምግብ ወይም መጠጥ ሆን ብሎ በአፍ በኩል ማስመለስ ነው። ያለ ፍላጎቱ ትውከቱ አሸንፎት የወጣ ከሆነ ግን ፆሙ ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ የለም።
ምክንያቱም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው፦ «ትውከቱ አሸንፎት ያስመለሰ ሰው ቀዷ ማውጣት አይጠበቅበትም፤ ሆን ብሎ ያስታወከ ግን ቀዷእ ማውጣት አለበት።» (((ቲርሚዚይ በቁጥር 720 ላይ ዘግበውታል።)))
“ትውከቱ ያሸነፈው” ማለት፡- ያለ ፍላጎቱ ሆዱ ውስጥ ያለው ቀድሞ በመውጣት ካሸነፈው ማለት ነው።
3- ከእስልምና መውጣት እና ክህደት፤ ምክንያቱም ከአምልኮት ጋር ይቃረናልና (ሥራን ሁሉ ያበላሻል)። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ "ብታጋራ ሥራህ በእርግጥ ይታበሳል።" [አዝ-ዙመር፡ 65]
4‐ ዋግምት፤ ዋግምት ማለት ደምን ከሰውነት ማስወጣት ነው።
ምክንያቱም ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፦ «ዋግምት ያደረገውም የተደረገለትም ሰው አፍጥረዋል።» (((አቡዳውድ በቁጥር 2367 ላይ ዘግበውታል)))
ልክ እንደ ዋግምት: ደም መለገስም (ተመሳሳይ ብያኔ ይኖረዋል)።
ከቁስል፣ ከጥርስ መነቀል ወይም ከአፍንጫ ደም መፍሰስ ፆሙ ላይ ችግር አያስከትልም። ምክንያቱም እንደ ዋግምት አይደለም ወይም ተመሳሳይ ትርጉም (ይዘት) የላቸውምና ነው።
5- ((ለአዋቂዎች))፡ ፆም በግብረ ሥጋ ግንኙነት ወይም ብልትን በመነካካት የዘር ፈሳሽን በማስወጣት ይበላሻል።
6- ((ለአዋቂዎች))፡ የወር አበባ እና የድህረ ወሊድ ደም መፍሰስ፤ አንዲት ሴት የወር አበባ ወይም የድህረ ወሊድ ደም ባየች ጊዜ ፆሟን ታቋርጣለች፤ (በዚህ ምክንያት ያልፆመቻቸውን ቀናትንም) ቀዳ የማውጣት ግዴታ አለባት። ምክንያቱም ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ስለ ሴቶች እንዲህ ብለዋል፡- "...በወር አበባ ጊዜዋ አትሰግድም፤ አትፆምም አይደለምን?" (((ቡኻሪይ በቁጥር 304 ላይ ዘግበውታል)))
7- ምግብና መጠጣትን የሚተኩ ነገሮች፡ ለምሳሌ ምግብነት ያላቸው መርፌዎች (ጉሉኮስ)።
በፆም ወቅት የሚወደዱ ተግባራት ምን ምን ናቸው?
መ፡- ፆመኛ በፆሙ ወቅት ለሚከተሉት ጉዳዮች ትኩረት መስጠት ይወደድለታል ሱናም ይሆንለታል፦
1- ሰሑር፡- ምክንያቱም ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- «ሰሑር ተመገቡ፤ ምክንያቱም በሰሑር ውስጥ በረካ አለበትና።» (((ቡኻሪይ በቁጥር 1923 እና ሙስሊም በቁጥር 1095 ላይ ዘግበውታል)))
ሰሑር ብዙ ወይም ትንሽ ምግብ በመመገብ ሊገኝ ይችላል፤ በአንድ ጉንጭ ውኃ ብቻም ይገኛል። የሰሑር መመገቢያ ጊዜም ከእኩለ ሌሊት እስከ እውነተኛው ጎህ እስኪቀድ ባለው ጊዜ ውስጥ ነው።
2- ሰሑርን ማዘግየት፡- ዘይድ ቢን ሣቢት (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ ላይ እንዲህ ብለዋል፡- «"ከአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ጋር ሰሑር ተመገብንና ከዚያም ለመስገድ ተነሳን።" እኔም፦ "በመካከላቸው ምን ያክል ጊዜ ነበር?" ብዬ ጠየቅኩት። እርሱም፡- "ሐምሳ አንቀጾችን (የሚያስነብብ) ያክል።" አለኝ።» (((ቡኻሪይ በቁጥር 575 እና ሙስሊም በቁጥር 1097 ላይ ዘግበውታል)))
“ሐምሳ አንቀጾች” ማለት፦ ሰሑር በልተው ከጨረሱበት እና የሱብሒ ሰላት አዛን ባለበት መካከል የነበረው የጊዜ ርቀት ሐምሳ የቁርኣን አንቀጾችን ለማንበብ የሚፈጀው ያህል ጊዜ ነበር ማለት ነው። ይህ ሐዲሥ ሰሑርን እውነተኛው ጎህ ወደሚቀድበት ጊዜ እስኪደርስ ድረስ ማዘግየትን ያበረታታል።
3- ፈጡርን ማፍጠን፡- ፆመኛ ሰው ፀሐይ መጥለቋ ከተረጋገጠ በኋላ ፆሙን ለማፍጠር መፍጠኑ ይወደዳል።
ይህም የሰህል ቢን ሰዕድ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ሐዲሥ ላይ በመመርኮዝ ነው፤ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፦ "ሰዎች ፆምን በሰዓቱ ለማፍጠር እስከተቻኮሉ ድረስ በመልካም ላይ ከመሆን አይወገዱም።" (((ቡኻሪ፡ 1957 እና ሙስሊም፡ 1098 ዘግበውታል)))
4- በእሸት ተምር ማፍጠር፤ ካልተቻለ በተገኘው ተምር እሱም ካልተገኘ በውሃ ማፍጠር።
ይህም የአነስ ቢን ማሊክ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ሐዲሥን መሠረት በማድረግ ነው፦ «የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከመስገዳቸው በፊት በእሸት ቴምር ያንን ካላገኙ በተገኘው ቴምር ያንንም ካላገኙ ደግሞ ትንሽም ብትሆን ውሃ ጎንጨት ብለው ያፈጥሩ ነበር።» (((አቡ ዳውድ ቁጥር 2356 ላይ ዘግበውታል)))
"ትንሽም ብትሆን ውሃ ይጎነጩ" ማለት፡- ሦስት ጊዜ ይጎነጩ ነበር።
የሆነ ቦታ ላይ ሆኖ ማፍጠሪያ ጊዜ ቢደርስበትና ፆሙን የሚፈታበት ነገር ካላገኘ፤ በልቡ ፆምን ለመፍረስ መነየት (ማሰብ) ይችላል፤ ይህ አፍጥሯል ለመባል በቂው ነው።
5- በፈጡር ጊዜ እና በፆም ወቅት ዱዓእ ማድረግ።
ምክንያቱም የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፦ «ሦስት ዓይነት ሰዎች ዱዓቸው ተቀባይነት ያገኛል፦ ፍትሐዊ የሆነ መሪ፣ ፆመኛ በሚያፈጥርበት ጊዜ የሚያደርገው እንዲሁም የተበደለ ሰው የሚያደርገው ዱዓእ ናቸው።» (((ቲርሚዚይ በቁጥር 3598 ላይ ዘግበውታል።)))
6- ሰደቃ (ምፅዋት) መስጠት፣ ቁርኣን መቅራት፣ ፆመኞችን ማስፈጠር እና ሌሎች መልካም ስራዎችን ማብዛት ይበረታታል።
ኢብኑ ዐባስ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ እንዲህ ብለዋል፡- "የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከሰዎች ሁሉ የበለጠ ለጋስ ነበሩ፤ የበለጠ ለጋስና ቸር የሚሆኑት ደግሞ በረመዳን ጂብሪልም በሚያገኛቸው ጊዜ ነበር። ጂብሪል በረመዳን በየሌሊቱ ያገኛቸውና ቁርኣንን ያስተምራቸው ነበር። የአላህ መልዕክተኛም (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከአውሎ ነፋስ የበለጠ በመልካም ነገር ላይ ፈጣን ነበሩ።" (((ቡኻሪ በቁጥር 6 እና ሙስሊም በቁጥር 2308 ላይ ዘግበውታል)))
7- በሌሊት ሶላት ላይ መትጋት፡ በተለይ በረመዳን የመጨረሻዎቹ አስር ቀናት።
ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላትና) ባስተላለፈችው ሐዲሥ እንዲህ ብላለች፡- "አስሩ ቀናት ሲገቡ ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሽርጣቸውን ያጠብቁ፤ ሌሊቱን በአምልኮ ሕያው አድርገው ያሳልፉ፣ ቤተሰባቸውንም ይቀሰቅሱ ነበር።" (((ቡኻሪ በቁጥር 2024 እና ሙስሊም በቁጥር 1174 ላይ ዘግበውታል)))
"አስሩ ቀናት ሲገቡ" ማለት፡ አስሩ የረመዳን የመጨረሻዎቹ ቀናት ነው።
"ሽርጣቸውን ያጠብቁ" ማለት፡ ከወትሮው በበለጠ ለአምልኮ መዘጋጀታቸውን እና ከፍተኛ ጥረት በማድረግ መነሳሳታቸውን የሚጠቁም ዘይቤያዊ አነጋገር ነው።
"ሌሊቱን ሕያው ያደርጉ ነበር" ማለት፡ ሌሊቱን በሶላትና በሌሎች ዒባዳዎች ያሳልፋሉ ማለት ነው።
"ቤተሰባቸውን ይቀሰቅሱ ነበር" ማለት፡ በሌሊት ሰላት እንዲሰግዱ ያስነሷቸው ነበር ማለት ነው።
8- ዑምራ ማድረግ ይበረታታል፡-
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፦ "ረመዳን በመጣ ጊዜ ዑምራን አድርጉ፤ በረመዳን የሚደረግ ዑምራ ከሐጅ እኩል ነውና።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1782 እና ሙስሊም በቁጥር 1256 ላይ ዘግበውታል)))
9- ለሰደበው ሰው "እኔ ፆመኛ ነኝ" ማለት፤ ለሰዎችም መልካም ቃና ያለው ንግግር መናገር እና ከክፉ ቃልም መታቀብ፤
ምክንያቱም የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ ነው፦ «ከእናንተ አንዳችሁ ፆመኛ በሆነበት ቀን አይባልግ የመሀይም ሥራ አይሥራ፤ አንድ ሰው ቢሰድበው ወይም ቢጋደለው እንኳ እኔ ፆመኛ ነኝ! እኔ ፆመኛ ነኝ! ይበል።» (((ቡኻሪ በቁጥር 1904 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ላይ ዘግበውታል)))
"አይባልግ" ማለት፡ ጸያፍ ቃልን አይናገር ማለት ነው።
"የመሀይም ሥራ አይሥራ" መሀይምነት፡ የጥበብ እና የትክክለኛ ንግግር እና ተግባር ተቃራኒ ነው።
10- ፆመኛ ፆሙን በሚፈታ ጊዜ እንዲህ ማለቱ ይወደዳል፦ "ዘሀበ አዝዘመኡ፤ ወብተለቲል ዑሩቁ፤ ወሠበተል አጅሩ ኢን ሻአ አላህ" ትርጉሙ፡ (ጥም ተወገደ፤ የደም ሥሮችም ረጠቡ፤ ምንዳውም በአላህ ፈቃድ የተረጋገጠ ሆነ ማለት ነው።) (((አቡዳውድ በቁጥር 2357 ላይ ዘግበውታል)))
በፆም ወቅት የሚጠሉ ነገሮች ምን ምን ናቸው?
መ፡- ለፆመኛ የሚጠሉ አንዳንድ ነገሮች አሉ፤ እነዚህ ነገሮች ፆሙን የሚያበላሹ ወይም ምንዳውን የሚቀንሱ ሊሆኑ ይችላሉ። እነሱም፡-
1 - ውዱእ በሚያደርግ ጊዜ ሲጉመጠመጥም ሆነ ውኃ ወደ አፍንጫው ሲስብ (ሲሰረነቅ) ከመጠን በላይ መሳብ።
ይህም ውኃው አልፎ ወደ ሆድ ውስጥ እንዳይገባ ስለሚያሰጋ ነው። ምክንያቱም ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- «ፆመኛ ካልሆንክ በቀር ውኃን ወደ አፍንጫህ በደንብ ሳብ።» (((አቡዳውድ በቁጥር 2366 ላይ ዘግበውታል)))
2- አክታን መዋጥ፡ (አክታ) አንድ ሰው የሚተፋው ምራቅ ወይም ንፍጥ የሆነ ነገር ነው። የተጠላበትም ምክንያት ይህ ድርጊት ከአስጸያፊነቱና ከሚያስከትለው ጉዳት ባሻገር ወደ ሆድ ስለሚደርስ (በትንሹም ቢሆን) ብርታትን ይሰጣል።
3 - አስፈላጊ ሳይሆን ምግብ መቅመስ፤ ይህንን ማድረጉ አስፈላጊ ከሆነ ግን - ለምሳሌ ጨውን መቅመስ ያለበት ምግብ አብሳይ ወይም ተመሳሳዩ ከሆነ - ጉሮሮው ጋር እንዳይደርስ እስከተጠነቀቀ ድረስ መቅመሱ ችግር የለውም።
4- የቀኑን ክፍለ ጊዜ በመኝታ ማሳለፍ፣ ጊዜ ማባከን፣ እርባና የሌላቸውን ወሬዎችና ተግባሮችን ማብዛት፤ መሆን ያለበት ቀኑን የአምልኮ ተግባራትን በመፈፀም ማሳለፍ ነው።
5- ((ለአዋቂዎች))፡ ስሜቱ ቶሎ ለሚቀሰቀስበትና ፆታዊ ግንኙነት ወደመፈፀም እገፋፋለሁ ብሎ ለሚፈራ ሰው ሚስቱን መሳም፡ በመሰረቱ ፆመኛ የሆነ ሚስቱን መሳሙ አይወደድም፤ ምክንያቱም ፆሙ እንዲበላሽ የሚያደርገው የዘር ፈሳሹ እንዲወጣ ወይም ወደ ግብረ ሥጋ ግንኙነት እንዲያመራ የስሜት መነቃቃት ሊያስከትል ስለሚችል ነው። ፆሙ እንዲበላሽ የሚያደርግ ደረጃ እንደማይደርስ እርግጠኛ ከሆነ ግን መሳሙ ችግር የለውም።
6- ((ለአዋቂዎች)) ስለ ወሲባዊ ግንኙነት ማሰብ ወይም ፍላጎትን የሚቀሰቅስ ንግግር መነጋገር።
ያለ ሸሪዓዊ በቂ ምክንያት በረመዳን ፆምን የማፍረስ ብይኑ ምንድን ነው?
መ፡- አንድ ሙስሊም በረመዳን ቀን ያለ ሸሪዓዊ በቂ ምክንያት ፆሙን ከፈታ ወደ አላህ ተፀፅቶ መመለስና ምህረትን መጠየቅ አለበት። ምክንያቱም ይህ ከባድ ወንጀልና ትልቅ ጥፋት ነውና፤ ያልፆማቸውን ቀናት ከፀፀት እና አላህን ምህረት ከመጠየቅ ጋር ከረመዳን በኋላ ማካካስ አለበት።
በረመዳን የቀኑ ክፍለ ጊዜ ፆም መፍታት የተፈቀደላቸው ምን ዓይነት ሰዎች ናቸው? ምንስ ይጠበቅባቸዋል?
መ፡ የመጀመሪያው ሁኔታ፡- ከመፆም የሚከለክለው በሽታ ያለበት፣ መንገደኛ የሆነ፣ ለነፍሷም ይሁን ወይም ለምታጠባው ልጅ ጉዳትን የምትፈራ ነፍሰ ጡር ወይም የምታጠባ ሴት ወይም በሌሎች በቂ ሸሪዓዊ ምክንያቶች አለመፆም የሚፈቀድላቸው ፆማቸውን ማፍረስ ይችላሉ። ነገር ግን ከረመዳን በኋላ ያልፆሙትን ቀናት ቀዳ ማውጣት (ማካካሻውን የመፆም) ግዴታ አለባቸው። ምክንያቱም የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ "ከእናንተም ውሰጥ በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የሆነ ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን መፆም አለበት።" (አልበቀራህ፡ 184)
ማለትም፡- ከናንተ ውስጥ ፆምን አስቸጋሪ በሚያደርግ በሽታ የታመመ ወይም በጉዞ ላይ ያለ ሰው ፆሙን ሊያቋርጥ ይችላል፤ ከዚያም ያልፆመባቸውን ቀናት ቀዳ ያወጣል (ማካካሻውን ይፆማል)።
ሁለተኛው ሁኔታ፡- ህመሙ የማይድን በሽታ ከሆነና ይልቁኑ እየጠና የሚሄድና የሚዘወትር ከሆነ፣ እንዲሁም መፆም የማይችሉ አረጋውያን፤ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ቀዳ ማውጣት ስለማይችሉ ማካካሻውን መፆም ግዴታ አይሆንባቸውም። ይልቁኑ ድሆችን ማብላት ነው የሚጠበቅባቸው። ለእያንዳንዱ ላልፆሙበት ቀን ለአንድ ድሃ ግማሽ "ሷዕ" ምግብ ያበላሉ። አንድ "ሷዕ" በግምት 3 ኪ.ግ አካባቢ ነው።
ምክንያቱም የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ (በእነዚያም ፆምን በማይችሉት ላይ ቤዛ ድኻን ማብላት አለባቸው፡፡) (አልበቀራህ፡ 184) ይህን የቁርኣን አንቀጽ አስመልክቶ ኢብኑ ዐባስ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ ብለዋል፡- (የተሻረች (አንቀጽ) አይደለችም፡ መፆም የማይችሉ አዛውንት እና አሮጊትን የተመለከተ (አንቀጽ) ነው፤ ባልፆሙበት ቀን ምትክ ድሆችን በየቀኑ ይመግባሉ።) (((ቡኻሪ በቁጥር 4505 ላይ ዘግበውታል)))
አንድ ሰው ፆሙን መቼ ነው ቀዳ ማውጣት (ማካካስ) ያለበት? ቀጣዩ ረመዳን እስከሚገባ ድረስ ፆሙን ቢያዘገይስ?
በረመዳን ሸሪዓ በሚፈቅደው በቂ ምክንያት ፆሙን የፈታ ሰው የታላቁን አላህ ትእዛዝ በማክበር ማካካሻውን መፆም አለበት። (በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የሆነም ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን (በልኩ) መፆም አለበት።) (አልበቀራህ፡ 185)
በዓመቱ ውስጥ ማካካስ (ቀዳ ማውጣት) ግዴታ ይሆንበታል፤ እስከ ቀጣዩ (ሁለተኛው) ረመዳን በኋላ ማዘግየት የለበትም። ይህም እናታችንን ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላትና) እንዲህ ስላለች ነው፦ "ከረመዳን ቀዳ ማውጣት የሚጠበቅብኝ (መፆም ያለብኝ) ቀን ይኖርብኛና ነገር ግን በአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ተጠምጄ ስለምቆይ ከሸዕባን ወር በስተቀር እነሱን ማካካስ አልችልም ነበር።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1950 እና ሙስሊም በቁጥር 1146 ላይ ዘግበውታል)))
«ከሸዕባን ወር በስተቀር ማካካስ አልችልም ነበር» ማለቷ የሚቀጥለው ረመዳን ከመጀመሩ በፊት የግድ ማካካስ አስፈላጊ ለመሆኑ ማስረጃ ነው።
ነገር ግን እስከ ሁለተኛው ረመንዳ በኋላ ድረስ ቀዳ ማውጣቱን ካዘገየ፤ አላህን ምህረት (ይቅርታ) ከመጠየቅ፣ ወደ እርሱ በንሰሀ ከመመለስ እና ባደረገው ነገር ከመፀፀት ጋር ቀናቶቹን ማካካስ (ቀዳ ማውጣት) አለበት። ምክንያቱም ያመለጠውን ፆም ስላዘገየው ሊቀርለት አይችልም ስለዚህ ያልፆመባቸውን ቀናት ከሁለተኛው ረመዳን በኋላም ቢሆን ማካካስ (ቀዳ ማውጣት) አለበት።
በግዴታ ፆሞች ወቅት መጠበቅ ያለብን አደቦች (ስርዓቶች) ምን ምን ናቸው?
መ: የተወሰኑትን ለመጥቀስ እንሞክራለን፡ እነዚህ አደቦች (ስርዓቶች) በማንኛውም ጊዜ የሚያስፈልጉ ሲሆን ነገር ግን በረመዳን ወር በፆመኛው ላይ ይበልጥ የሚጠበቁበት ይሆናሉ፡-
1- ትዕዛዛትና ግዴታዎችን በአግባቡ ተጠባብቆ መፈፀም፤ ከእነዚህም መካከል ሰላትን በሰዓቱ እና በጀማዓ መስገድ ይገኝበታል።
አላህ እንዲህ ብሏል፦ (ሶላት በምእምናን ላይ በጊዜያት የተወሰነች ግዴታ ናትና።) (አን'ኒሳእ፡ 103)
2- ፆመኛ አላህና መልዕክተኛው (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከከለከሉት ነገር ሁሉ ማለትም ውሸት ከመናገር፣ ከሀሜት፣ ነገር ከማዋሰድ፣ ከማጭበርበር፣ ሙዚቃና ዘፈን ከማዳመጥ እና ከመሳሰሉት ሌሎች ወንጀሎችና ጥፋቶች መራቅ ይኖርበታል።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "የውሸት ምስክርነትንና በእርሱ መስራትን የማይተው ሰው፤ ምግቡንና መጠጡን መተዉ ለአላህ ምንም ጉዳዩ አይደለም።" ((ቡኻሪይ በቁጥር 1903 ላይ ዘግበውታል)))
“አዝዙር” ማለት፡ ውሸት፣ ከእውነት ማዘንበል (ማፈንገጥ) እና በውሸት መሥራት ማለት ነው።
“ለአላህ ምንም ጉዳዩ አይደለም” ማለት፡ የላቀው አላህ ለግለሰቡ ፆም ቦታ አይሰጠውም፤ አይቀበለውም ማለት እንጂ ፆሙን እንዲተው ታዘዘ ማለት አይደለም። ይልቁን በመልዕክቱ የተፈለገበት የውሸት ንግግርን ማስጠንቀቅ ነው።
ፆመኛ ሰው ሊፈፅማቸው የሚፈቀዱለት ነገሮች ምን ምን ናቸው?
መ፡- የኢስላም ሊቃውንት የዘረዘሯቸው ለፆመኛ የሚፈቀዱ በርካታ ነገሮች አሉ፡ ከነዚህም ውስጥ፡-
1 - ሰውነቱን መታጠብ እና ራሱን በውኃ ማቀዝቀዝ።
2- መፋቂያ መጠቀም።
3- በጣም ሳይስቡ ውኃ ወደ አፍንጫ ውስጥ መሳብ እና መጉመጥመጥ።
4- ለምርመራ ትንሽ ደም መውሰድ።
5- የዓይን እና የጆሮ ጠብታዎች መጠቀም።
6- ምግብነት የሌለው የሕክምና መርፌ መጠቀም
7- አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ምግብን ሳይውጥ መቅመስ፤ ከቀመሰ በኋላ ግን የግድ መትፋት አለበት።
8- ሽቶ መቀባት እና ማሽተት።
9- ዓይንን ኩል መቀባት።
በረመዳን የሌሊት ሰላት መስገድ ምን ፋይዳ አለው?
መ፡- የተራዊሕ ሰላት በመባል የሚታወቀው የረመዳን የሌሊት ሰላት ትልቅ ፋይዳ አለው።
ከአቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ፡ የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "በአላህ አምኖ እና ምንዳውን ከአላህ አስቦ የረመዳንን ወር በሰላት ያሳለፈ ያለፈ ወንጀሉ ይማርለታል።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 37 እና ሙስሊም በቁጥር 759 ላይ ዘግበውታል)))
“አምኖ” ማለት፡- በአላህ አምኖ እና ግዴታ ያደረገው እርሱ መሆኑን አምኖ ማለት ነው።
"ኢሕቲሳበን" ማለትም፡ ከኃያሉ አላህ ምንዳን ፈልጎ እንጂ ለይዩልኝ ወይም ሌላ ከኢኽላስ (ለአላህ ብቻ ብሎ አጥርቶ ከመሥራት) የሚጻረር ነገር ፈልጎበት መሆን የለበትም።
የሌሊት ሰላት የመስገድ ሙሉ ምንዳን ለማግኘት ኢማሙ እስከሚጨርስ ድረስ ተራዊህን አብሮ ለመስገድ ጥረት ማድረግ አለበት። ምክንያቱም የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ስላሉ፡- "ኢማሙ ሰላቱን እስኪጨርስ ድረስ አብሮ የሰገደ ሰው፤ የ (ሙሉ) ሌሊት ሰላት ምንዳ ይሰጠዋል።" (((ቲርሚዚይ በቁጥር 806 ላይ ዘግበውታል))
በረመዳን የመጨረሻዎቹ አስር ቀናት በተለይም በለይለቱል ቀድር (በመወሰኛይቱ ሌሊት) የሚወደዱ ተግባሮች ምን ምን ናቸው?
መ፡- ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በረመዳን የመጨረሻዎቹ አስር ቀናት ከሌሎች ጊዜያት የበለጠ በዒባዳ ላይ ትግል ያደርጉ ነበር። በውስጣቸውም ለይለተል ቀድርን (የመወሰኛይቱን ሌሊት) ይጠባበቁ ነበር። በነዚህ ቀናት ውስጥ ከሚወደዱ በርካታ ተግባሮች መካከል የተወሰኑትን እንጠቅሳለን፡-
1 - በነዚህ ቀናት ከፍተኛ ጥረት ማድረግ።
እናታችን ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላትና) እንዲህ ብለዋል፡- "አስሩ (የረመዷን የመጨረሻ) ለሊቶች ሲገቡ ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሽርጣቸውን ያጠብቁ፤ ሌሊቱን በአምልኮ ሕያው አድርገው ያሳልፉ፣ ቤተሰባቸውንም ይቀሰቅሱ ነበር።" (((ቡኻሪ በቁጥር 2024 እና ሙስሊም በቁጥር 1174 ላይ ዘግበውታል)))
"ሽርጣቸውን ያጠብቁ" የሚለው የእናታችን ዓኢሻ ንግግር ከወትሮው በበለጠ ለአምልኮ ለመዘጋጀት እና ከፍተኛ ጥረት ለማድረግ መነሳሳታቸውን የሚጠቁም ዘይቤያዊ አነጋገር ነው።
እናታችን ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላትና) በምታስተላልፈው ሌላ ሐዲሥ ደግሞ፡- "የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በመጨረሻዎቹ አስር ቀናት ውስጥ ከሌላው ጊዜ በበለጠ (በአምልኮ) ላይ ከፍተኛ ትግል ያደርጉ ነበር።" (((ሙስሊም በቁጥር 1175 ላይ ዘግበውታል)))
ለይለቱል ቀድር (የመወሰኛይቱ ሌሊት) የምትገኘው በረመዳን የመጨረሻዎቹ አስር ቀናት ውስጥ ነው። ስለሆነም ሙስሊሙ ለይለቱል ቀድርን ለማግኘት አስሩንም ሌሊቶችን በአግባቡ ሊጠቀምባቸው ይገባል። ኢብኑ ዐባስ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ለይለቱል ቀድርን በረመዳን የመጨረሻዎቹ አስር ሌሊቶች ውስጥ ፈልጓት።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 2021 ላይ ዘግበውታል)))
2- ለይለቱል ቀድርን (የመወሰኛይቱን ሌሊት) በሶላት ቆሞ ማሳለፍ።
አቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "(በአላህ) አምኖ እና ምንዳውንም ከአላህ አስቦ ለይለተል ቀድርን በሰላት ያሳለፈ ያለፈ ወንጀሉ ይማርለታል።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 1901 እና ሙስሊም በቁጥር 760 ላይ ዘግበውታል)))
3- በመስጂድ ውስጥ ኢዕቲካፍ ማድረግ።
እናታችን ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላትና) ባስተላለፈችው ሐዲሥ እንዲህ ብላለች፡- "ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በረመዳን የመጨረሻዎቹ አስር ቀናት ውስጥ ኢዕቲካፍ ያደርጉ ነበር።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 2033 እና ሙስሊም በቁጥር 1172 ላይ ዘግበውታል)))
ኢዕቲካፍ፡- በመስጂድ ውስጥ የአምልኮ ስርዓትን ለመፈፀም በማሰብ መገለል ነው፤ በሰዎች ከመጠመድ፣ በዱንያዊ ጉዳዮች ልብን ባዶ ከማድረግ እና ከመጠመድ (ከመወጠር) ተገልሎ ጥራትና ልዕልና በተገባው አላህ (እርሱን በማምለክ) ብቻ መጠመድ ነው።
ሱረቱል ቀድርን አንብብና ተርጉም።
በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በሆነው፡ (እኛ (ቁርኣኑን) በመወሰኛይቱ ሌሊት አወረድነው። (1) መወሰኛይቱም ሌሊተ ምን እንደ ኾነች ምን አሳወቀህ? (2) መወሰኛይቱ ሌሊት ከሺሕ ወር በላጭ ናት። (3) በርሷ ውስጥ መላእክትና መንፈሱ በጌታቸው ፈቃድ በነገሩ ሁሉ ይወርዳሉ። (4) እርስዋ እስከ ጎህ መውጣት ድረስ ሰላም ብቻ ናት።) [አልቀድር፡ 1-5]
ትንታኔዋ፡-
(እኛ (ቁርኣኑን) በመወሰኛይቱ ሌሊት አወረድነው።) [አልቀድር፡ 1] እኛ ቁርኣንን በረመዳን ወር በለይለቱል ቀድር ወደ ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ማውረድ እንደጀመርነው ሁሉ በአንድ ላይም (ሙሉውን) ወደ ታችኛው ሰማይ አወረድነው።
(መወሰኛይቱም ሌሊት ምን እንደሆነች ምን አሳወቀህ?) [አልቀድር፡ 2] (አንተ ነብይ ሆይ!) በዚህች ለሊት ምን አይነት መልካም ነገር እና በረከት (ፀጋ) እንዳለ ታውቃለህን?!
(መወሰኛይቱ ሌሊት ከሺሕ ወር በላጭ ናት።) [አልቀድር፡ 3] ይህች ሌሊት ታላቅና መልካም ምሽት ናት። በአላህ አምኖ እና ምንዳውንም ከአላህ አስቦ ለይለተል ቀድርን በሰላት ላሳለፈ ከሺህ ወራት በላጭ ናት። እርሷ የተባረከች ለሊት ናት፤ በዚህች ሌሊት ውስጥ የተሰራ መልካም ሥራ ከሺህ ወራት ሥራ በላጭ ነው።
(በርሷ ውስጥ መላእክትና መንፈሱ በጌታቸው ፈቃድ በነገሩ ሁሉ ላይ ይወርዳሉ።) [አልቀድር፡ 4] በኃያሉ ጌታቸው ፈቃድ መላኢካዎችም ጂብሪልም ዐለይሂ-ሰላም ጭምር ይወርዳሉ፤ አላህ በዚያ ዓመት የወሰናቸው ጉዳዮች ሁሉ ሲሳይም ሆነ ሞት፣ መወለድ ወይም ሌላ ነገር አላህ የወሰነው በዛች ሌሊት ይወርዳሉ።
(እርስዋ እስከ ጎህ መውጣት ድረስ ሰላም ብቻ ናት።) [አልቀድር፡ 5] ይህች የተባረከች ለሊት ከመጀመሪያዋ ጀምሮ ጎህ ቀዶ መጨረሻዋ እስኪደርስ ድረስ ሁሉ ነገሯ የተባረከ ነው።
ዘካተል ፊጥር ምንድን ነው? ሸሪዓዊ ብይኑስ ምንድን ነው?
መ፡- የረመዳን ፆም መጠናቀቅን ምክንያት በማድረግ እስልምና የደነገገው ዘካ (ምፅዋት) ነው።
ዘካተል ፊጥር በሁሉም ሙስሊም ላይ ትንሽም ሆነ ትልቅ፤ ወንድም ሆነ ሴት ላይ የተጣለ ግዴታ ነው። አንድ ሙስሊም ለራሱ እና ወጪያቸውን ሸፍኖ ለሚያስተዳድራቸው እንደ ሚስቱ እና ልጆቹ ላሉ የማውጣት ግዴት አለበት።
ኢብኑ ዑመር ((አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና)) እንዲህ ብለዋል፡- "የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በባሪያም ሆነ ጨዋ፤ በወንድም ሆነ በሴት፤ በልጅም ሆነ አዋቂ በሙስሊሞች ላይ ሁሉ ዘካተል ፊጥርን ከተምር ወይም ገብስ አንድ "ሷዕ" መስጠትን ግዴታ አድርገዋል።" (((ቡኻሪ በቁጥር 1503 እና ሙስሊም በቁጥር 984 ላይ ዘግበውታል)))
ዘካተል ፊጥር በአካባቢው በተለምዶ ለምግብነት በሚውሉ እንደ ሩዝና በመሳሰሉት ይሰጣል። ለመስጠት በጣም ጥሩው ጊዜ የዒድ ጠዋት ከዒድ ሰላት በፊት ሲሆን ከዚያ በፊት አንድ ወይም ሁለት ቀን ቀደም ብሎ መስጠትም ይፈቀዳል። ክብደቱ በግምት 3 ኪሎ ግራም አካባቢ ነው።
ከዘካተል ፊጥር ግዴታነት ጀርባ ያለው ጥበብ ምንድን ነው?
መ፡ ከጥበቦቹ መካከል፦
1- ፆመኛውን በፆሙ ወቅት ሊፈጠር ከሚችለው ከንቱ ወይም ፀያፍ ንግግር ማፅዳት።
2- በዒድ ቀን ድሆች እና ችግረኞች የሰው እጅ እንዳይጠይቁ ለማብቃቃት። ደስታንም በልባቸው ውስጥ ለመፍጠርና ዒድ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የደስታና የፌሽታ ቀን እንዲሆን ለማድረግ ነው። ኢብኑ ዐባስ ((አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና)) እንዲህ ብለዋል፡- "የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ዘካተል ፊጥር ማውጣትን ፆመኛን ከከንቱ እና ፀያፍ ንግግር ለማንፃት እንዲሁም ለድሆች ደግሞ ምግብ እንዲሆን በግዴታነት ደነገጉ።" (((አቡ ዳውድ በቁጥር 1609 ላይ ዘግበውታል)))
3- የረምዳን ወር ፆም ለማጠናቀቅ እና በሶላት ቆሞ ለማሳለፍ እንዲሁም በዚህ በተባረከ ወር የተቻለውን ሁሉ መልካም ስራዎችን ለመስራት በማስቻል አላህ በባሪያው ላይ ለዋለው ፀጋ የምስጋና መግለጫ ነው።
4- ለሚገባቸው ሰዎች በተወሰነለት ጊዜ ውስጥ በመስጠት ታላቅ ምንዳ ለማግኘት ይረዳል።
የዒድ ሱናዎች ምን ምን ናቸው?
መ፡ ዒድ (በዓል) በእስልምና አላህ ለዋለልን ችሮታ እና እዝነት ደስታን ከምንገልፅባቸው መንገዶች መካከል አንዱ ነው። አንድ ሙስሊም በዒድ ቀን ከሚያደርጋቸው ሱናዎች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፦
1- ወደ ዒድ ሰላት ከመውጣት በፊት ገላን መታጠብ።
ዐብደላህ ኢብኑ ዑመር (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በዒድ አልፊጥር ቀን ወደ ሶላት ቦታ ከመሄዳቸው በፊት ይታጠቡ እንደነበር በ"አል-ሙወጣእ" እና በሌሎች ድርሳናት (ኪታቦች) ላይ በትክክል ሰነድ ተዘግቧል። (((«ሙወጣእ» ማሊክ (1/177)))
2- ለዒድ አልፊጥር ሰላት ከመውጣቱ በፊት መመገብ፤ ተምሮችን ከመብላቱ በፊት ለሰላት መውጣት የለበትም። አነስ ኢብኑ ማሊክ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ ብለዋል፦ "የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በዒድ አልፊጥር ቀን የተወሰኑ ተምሮችን ሳይበሉ አይወጡም ነበር ... ጎዶሎ ቁጥር (ብዛት ያላቸውን ተምሮች) ይበሉ ነበር።" (((ቡኻሪ በቁጥር 953 ላይ ዘግበውታል)))
3- የዒድ ተክቢራ።
የዒድ አልፊጥር በዓል ላይ የተክቢራ ጊዜ የሚጀምረው በዒዱ ሌሊት ነው፤ ማለትም የረመዳን ወር የመጨረሻ ቀን ጀንበር ከጠለቀችበት ጊዜ አንስቶ ኢማሙ የዒድ ሰላት ለማሰገድ እስኪገባ ድረስ ነው።
አላህ እንዲህ ብሏል፦ "ቁጥሮችንም ልትሞሉ አላህንም ቅኑን መንገድ ስለመራችሁ ታከብሩትና ታመሰግኑት ዘንድ (ይህን ደነገግንላችሁ)።" (አል'በቀራህ፡ 185)
4- የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት መለዋወጥ፡- ከዒድ ስነ-ስርአቶች መካከል ቃሉ ምንም ይሁን ምን ሰዎች እርስ በእርሳቸው መለዋወጣቸው መልካም የደስታ መገለጫ ናቸው። አንዱ ለሌላው “ተቀበለላሁ ሚንና ወሚንኩም / አላህ ከእኛም ከናንተም ይቀበለን” ወይም “ዒድ ሙባረክን” እና ሌሎችም የሚፈቀዱ የደስታ መገለጫዎች ይገኙበታል።
ከጁበይር ቢን ኑፈይር (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንደተዘገበው፡- በዒድ ቀን የነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ባልደረቦች ሲገናኙ እርስ በርሳቸው፡- “ቱቁቢለ ሚንና ወሚንክ / አላህ ከእኛም ከናንተም ይቀበለን” ይባባሉ ነበር። (((አል-መሓሚሊይ ዘግበውታል፤ በ“ፈትሑ አል-ባሪ” (2/446) ላይ ኢብኑ ሐጀርም፡- የሐዲሡ ዘገባ ሰንሰለቱን (ሰነዱ) ሐሰን ነው ብለዋል።)))
5- ለሁለቱ ዒዶች ራስን ማስዋብ፡-
የምዕመናን መሪ ዑመር ቢን አል-ኸጣብ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) እንዲህ ብለዋል፦ "አንቱ የአላህ መልእክተኛ ሆይ! ዑጣሪድ በሐር የተሸመነ ልብስ ሲሸጥ ተመልክቼዋለሁና ለምን ለርሶ ገዝተንልዎት ልዑካን ሲመጡና እና ለዒድ ቀን አይለብሱትም?" (((ቡኻሪ በቁጥር 948 እና ሙስሊም በቁጥር 2068 ላይ ዘግበውታል))
ከናፊዕ በተላለፈ ሐዲሥ ደግሞ፦ ኢብኑ ዑመር (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በሁለቱ ዒዶች ላይ ምርጥ ልብሳቸውን ይለብሱ ነበር። (((አል'በይሃቂይ «አስ-ሱነኑ አል-ኩብራ» 6143 ላይ ዘግበውታል)))
6- ወደ ሶላት በአንድ መንገድ ሂዶ ሲመለሱ እና በሌላ መንገድ መመለስ፤
በጃቢር ብን ዐብደላህ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) በተላለፈ ሐዲሥ እንዲህ ብለዋል፡- "ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በዒድ ቀን (ለመሄጃና ለመመለሻ) የተለያየ መንገድ ይጠቀሙ ነበር።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 986 ላይ ዘግበውታል)))
የሸዋልን ወር ስድስት ቀናት መፆም ያለው ፋይዳ ምንድን ነው?
መ፡- የረመዳን ወር የግዴታ ፆም መጠናቀቅን ተከትሎ የሸዋልን ስድስት ቀናት መፆም የተወደደ ሱና ሲሆን ትልቅ ፋይዳና ብዙ ምንዳ አለው። ምክንያቱም ሸዋልን የፆመ ሰው ዓመቱን ሙሉ የፆመ ያክል ምንዳ ያገኛልና ነው። ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "ረመዳንን የፆመና ከዚያም ከሸዋል ስድስት ቀናት ያስከተለ ሰው ዓመቱን ሙሉ እንደፆመ ይቆጠርለታል።" (((ሙስሊም በቁጥር 1164 ላይ ዘግበውታል)))
ረመዳን ምን አስተማረን? ከረመዳን በኋላስ?
መ: ለዚህ ጥያቄ መልስ በመስጠት እንቋጫለን፤ ፆም ሙስሊሞች ከሚታነፁባቸው ታላላቅ የእስልምና ትምህርት ቤቶች መካከል አንዱ ነው። ከሃይማኖቱ ምሰሶዎችና ታላላቅ መሠረቶቿ አንዱ ነው። ቀጥሎ አንድ የአላህ ባሪያ ከረመዳን በኋላ ፀንቶ ይቀጥል ዘንድ በረመዳን ወር በፆም ትምህርት ቤት ከሚማራቸው ትምህርቶች እና ጥበቦች ጥቂቶቹ እንጠቅሳለን።
የመጀመሪያው ትምህርት፡
የረመዳን ወር ከታላላቅ የአምልኮ ዓይነቶችና ወደ አላህ መቃረቢያ መንገዶች መካከል አንዱ የሆነውን ትዕግስትን አስተምሮናል። አንድ የአላህ ባሪያ ምግብና መጠጥን በመከልከል ሲታገሥ በዚያውም መልካም ነገሮችን ሁሉ ሰብስቦ የያዘውን ትዕግስትን ይለማመዳል፤ የአላህን ትዕዛዛት በመፈፀም ላይ መታገስን፤ አላህን ከማመጽ የመቆጠብ ትዕግስትን እንዲሁም አሳማሚ በሆኑ የአላህ ቅድመ ውሳኔዎች ላይ ትዕግስት ማድረግን ይለማመዳል። የበላይ የሆነው አላህ የትዕግስትን የላቀ ደረጃ አስመልክቶ እንዲህ ብሏል፦ (ታጋሾቹ ምንዳቸውን የሚሰጡት ያለግምት ነው።) (አዝ-ዙመር፡ 10)
ሁለተኛው ትምህርት፡
የረመዳን ወር አላህና መልዕክተኛው (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) ያዘዙትን በመፈፀምና የከለከሉትን በመራቅ በኩል እጅ መስጠትን (ፍፁም ታዛዥ መሆንን) አስተምሮናል። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ "አላህና መልክተኛውም ነገርን በፈረዱ ጊዜ ለምእምናንና ለምእምናት ከነገራቸው ለእነርሱ ምርጫ ሊኖራቸው አይገባም! የአላህንና የመልክተኛውንም ትእዛዝ የጣሰ ሰው ግልጽ የሆነን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ።" (አልአሕዛብ፡ 36)
ሦስተኛ ትምህርት፡
የረመዳን ወር አላህን እንድንፈራ (ተቅዋ) እና አንደበታችንን፣ አካላቶቻችንን እና ስሜቶቻችንን (ፍላጎቶቻችንን) ለአላህ ብለን እንድንቆጣጠር አስተምሮናል። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፡ "እናንተ ያመናችሁ ሆይ ፆም በነዚያ ከናንተ በፊት በነበሩት (ሕዝቦች) ላይ እንደ ተጻፈ በናንተም ላይ ተጻፈ (ተደነባ) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና፡፡" (አልበቀራህ፡ 183)
አቡ ሁረይራ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) ባስተላለፉት ሐዲሥ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- «አሸናፊና ኃያል የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል: "ፆም የእኔ ነው፤ ስሜቱን፣ ምግቡን መጠጡን ለእኔ ብሎ ትቷልና እኔ ነኝ ምንዳውን የምለግሰው፤ ፆም ጋሻም ነው።» (((ቡኻሪይ በቁጥር 7492 እና ሙስሊም በቁጥር 1151 ላይ ዘግበውታል)))
የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "የውሸት ምስክርነትንና በእርሱ መስራትን የማይተው ሰው፤ ምግቡንና መጠጡን ከመተዉ አላህ ምንም ጉዳይ የለውም።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 1903 ላይ ዘግበውታል)))
አራተኛው ትምህርት፡
የረመዳን ወር አምልኮንና ጣፋጭነቱን አስተምሮናል። ይህም ከረመዳን በኋላ በሰላት፣ በፆም እና ቁርኣንን በማንበብ ላይ እንድቀጥልበት ዘንድ ነው።
ፆምን በተመለከተ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "(ግዴታነቱን) አምኖ እና ምንዳውን ከአላህ አስቦ የረመዳንን ወር የፆመ ሰው ያለፈ ወንጀሉ ይማርለታል።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 38 እና ሙስሊም በቁጥር 760 ላይ ዘግበውታል)))
በሰላት ቆሞ የማሳለፍን የላቀ ደረጃ አስመልክቶ ደግሞ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ብለዋል፡- "በአላህ አምኖ እና ምንዳውን ከአላህ አስቦ የረመዳንን ወር በሰላት ያሳለፈ ያለፈ ወንጀሉ ይማርለታል።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 37 እና ሙስሊም በቁጥር 759 ላይ ዘግበውታል)))
ቁርኣንን በተመለከተ ደግሞ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህ ነበሩ፡- "(የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና)) የበለጠ ለጋስና ቸር የሚሆኑት በረመዳን ጂብሪል በሚያገኛቸው ጊዜ ነበር። ጂብሪል በረመዳን በየሌሊቱ ያገኛቸውና ቁርኣንን ያስተምራቸው ነበር።" (((ቡኻሪይ በቁጥር 6 እና ሙስሊም በቁጥር 2308 ላይ ዘግበውታል)))
አንድ የአላህ ባሪያ እንደ ረመዳን ባይሆንም እንኳ እንደ ፆም፣ ሰላት እና ቁርኣንን ማንበብን የመሳሰሉ አምልኮዎች ላይ በርትቶ ይቀጥላል።
አምስተኛ ትምህርት፡
የረመዳን ወር የአላህን ቅርብ ተቆጣጣሪነትን (ሙራቀባ) እና የኢሕሳንን የላቀ ደረጃ አስተምሮናል። ኢሕሳን ማለት አላህን ልክ እንደምናየው ሆነን ልናመልከው ነው፤ እኛ ባናየው እርሱ ያየናልና። ይህም ፆመኛ የአላህን የቅርብ ተቆጣጣሪነትን በማስተዋል ላይ ነፍሱን ያሰለጥናታል። ማድረግ እየቻለ እንኳ አላህ እንደሚመለከተው ስለሚያውቅ ነፍሱ የምትወተውተውን (ክልክል) ነገር ይተዋል። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ "እርሱም (አላህ) የትም ብትሆኑ ከእናንተ ጋር ነው። አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው።" (አልሐዲድ፡ 4)
ስድስተኛው ትምህርት፡
የረመዳን ወር ሃይማኖታችን ገርና ቀላል እንደሆነና አላህ ነፍስን ከችሎታዋ በላይ እንደማያስገድዳት አስተምሮናል። መፆም የቻለ ይፆማል ያልቻለ ደግሞ እንደ ሰውየው ሁኔታ ወይ ፆሙን ያፈርስና ያልፆመበትን ቀን ቀዳ ያወጣል (በሚችል ጊዜ ያካክሳል) ወይም ደግሞ ከፋራ ያወጣል (ምስኪን ያበላል)። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ (ከእናንተም ወሩን ያገኘ ሰው ይጹመው። በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የሆነም ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን (በልኩ) መጾም አለበት። አላህ በእናንተ ገሩን (ነገር) ይሻል። በእናንተም ችግሩን አይሻም፡፡ ቁጥሮችንም ልትሞሉ አላህንም ቅኑን መንገድ ስለመራችሁ ታከብሩትና ታመሰግኑት ዘንድ (ይህን ደነገግንላችሁ)።) (አልበቀራ፡ 185)
ሰባተኛው ትምህርት፡
የረመዳን ወር ምጽዋት መስጠትን፤ ለድሆችና ለችግረኞች ቸር መሆንን፤ ለእነርሱም ማዘንን አስተምሮናል። ነብዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይስፈንና) በረመዳን በጣም ለጋስ ነበሩ። (((ቡኻሪይ በቁጥር 6 እና ሙስሊም በቁጥር 2308 ላይ ዘግበውታል)))
ምክንያቱም አንድ የአላህ ባሪያ የረሃብን ህመም ከቀመሰ፤ ይህ ስሜት ድሆችን እንዲረዳ ይጋብዘዋል። ይህም አንዱ የተቅዋ (አላህን የመፍራት) መገለጫ ነው።
ስምንተኛው ትምህርት፡
የረመዳን ወር የላቀውን አላህ ምህረት፣ እዝነት እና ፀጋ ሰፊነት አስተምሮናል። (ምክንያቱም) ወሩ ሁሉ የእዝነት፣ የይቅርታ (የምህረት) እና ከጀሀነም እሳት ነጻ የሚወጣበት ወር ነውና። እንዲሁም በውስጡም ከሺሕ ወራት በላጭ የሆነችው ለይለቱል ቀድር (የመወሰኛይቱ ሌሊት) አለች። (ከሺሕ ወራት በላይ) ማለት፡ ሰማንያ ዓመት ከአራት ወራት በላይ ማለት ነው። አላህ እንዲህ ብሏል፦ (መወሰኛይቱም ሌሊት ምን እንደ ኾነች ምን አሳወቀህ? (2) መወሰኛይቱ ሌሊት ከሺሕ ወር በላጭ ናት። (3) በርሷ ውስጥ መላእክትና መንፈሱ በጌታቸው ፈቃድ በነገሩ ሁሉ ይወርዳሉ። (4) እርስዋ እስከ ጎህ መውጣት ድረስ ሰላም ብቻ ናት።) [አልቀድር፡ 2-5]
የትምህርቱ መደምደሚያ፡-
ከረመዳን በኋላስ?! የረመዳኑም ጌታ የወራትና የቀናቶችም ሁሉ ጌታ አላህ ነው። ስለዚህም አንድ የአላህ ባሪያ ምንም ሁኔታዎችና ቀናቶች ቢለዋወጡ ሁልጊዜም አንድ መርህ መከተል ይኖርበታል ይህም ኃያልና የበላይ የሆነው አላህን ፍራቻ (ተቅዋ) ነው።
ማጠቃለያ
በመጨረሻም ጠቃሚ ማጣቀሻዎችን እና ምንጮችን መጠቆም እፈልጋለሁ፤ በዚህ ርዕስ ላይ ሰፋ ያለ ትምህርት ለማግኘትና ከፆም ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በጥልቀት ለመረዳት የፈለገ ሰው ሊመለከታቸው ይገባል።
በሸይኽ ዐብዱልዐዚዝ ቢን ባዝ የተዘጋጀው "ስለ ዘካ እና ፆም አጭር ማብራሪያ" መጽሐፍ።
በሸይኽ ሙሐመድ ቢን ሷሊሕ አልዑሠይሚን የተዘጋጀው "መጃሊሱ ሸህሪ ረመዳን" መጽሐፍ።
“መጃሊሱ ሸህሪ ረመዳን አልሙባረክ” በመቀጠልም፡- “ኢትሓፉ አህሊል ኢማን ቢዱሩሲ ሸህሪ ረመዳን” በሸይኽ ሳሊሕ ቢን ፈውዛን አል-ፈውዛን የተዘጋጁ መጽሐፍት።
“ዑቁዱል-ጁማን ፊ ዱሩሲ ሸህሪ ረመዳን” የተሰኘው በሸይኽ፡ ሰዐድ ቢን ቱርኪ አል-ኸሥላን የተዘጋጀ መጽሐፍ።
"ዱሩሱ ሸህሪ ረመዳን" የተሰኘው በሸይኽ፡ ሙሐመድ ቢን ሻሚይ ሸይባህ የተዘጋጀ መጽሐፍ።
አላህ ሆይ! አንተ መሓሪና ለጋስ ነህ ይቅር ማለትንም ትወዳለህና ይቅር በለን! የአላህ ሰላትና ሰላም በነብያችንና አለቃችን ሙሐመድ፣ በቤተሰቦቻቸው፣ በተከታዮቻቸውና ፈለጋቸውን በተከተሉ ላይ ሁሉ ይስፈን።