يومي الأول في الإسلام

يومي الأول في الإسلام

የእስልምና የመጀመሪያ ቀኔ

Language: lang_am
Prepared by:
Version: 1.0
Translations 20
Amharic Bosnian English Spanish +16
Attachments 7
PDF
Audio
Video
+3

የእስልምና የመጀመሪያ ቀኔ

በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በሆነው

መግቢያ

ምስጋና ነብዩ ሙሐመድን ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ለዓለማት እዝነት አድርጎ ለላከው አላህ የተገባ ነው። ከአላህም በቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ አለመኖሩን፣ ብቸኛና በምንም ተጋሪ የሌለው መሆኑንም እመሰክራለሁ። የመጀመሪያዎቹም የመጨረሻዎቹም (ፍጥረታት ሁሉ) አምላክ እርሱው ነው። የነብያትም የመልዕክተኞችም መደምደሚያ የሆኑት ነብያችን ሙሓመድም -የአላህ ሶለዋትና ሰላም በርከት ብሎ እስከ ፍርዱ ቀን ድረስ ይስፈንባቸውና- የአላህ ባሪያውና መልዕክተኛው መሆናቸውን እመሰክራለሁ። ከዚህም በማስከተል፦

ማንኛውም ሰው ደስታን ፈላጊ ነው፤ ታዲያ አንዳንዶቹ ይህ ደስታ ገንዘብ በመሰብሰብ የሚገኝ እንደሆነ ያስባሉ፤ አንዳንዶቹ ደግሞ ከዝና ጥላ ስር እየፈለጓት ይገኛሉ፤ አንዳንዶቹም እርሷን በከፍተኛ ማህበራዊ ክብር ላይ (እንዳለች አድርገው) ይመለከቷታል፤ ከዚህም ውጭ እነዚህን በመሳሰሉ በዱኒያ መጠቃቀሚያዎች ውስጥ የሚያስቡም አሉ፤ ተጨባጩ የሚያስረዳው እውነታ ግን እነዚህን ነገሮች ካገኙት በርካታዎቹ ያ የፈለጉትን ደስታ ያገኘ አለመሆናቸው ነው።

ይሀው ደስተኝነት እውን ሊሆንልን የሚችለው የመላው ሰው ፈጣሪ ወደ መረጠልን እውነተኛው ሃይማኖት ስንመራ፤ እርሱን በመተግበርና በአስተምህሮቱም ጎዳና መጓዝ ስንችል ብቻ ነው። በዚህች ባለንባት ዓለም ደስታንና ጥሩ ኑሮን ከሞት በኋላ ባለው ሕይወትም ዘለዓለማዊ ደስታን የምናገኘው በዚህ ብቻ ነው።። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"እርሱ በጎ ሠሪ ሆኖ ፊቱን ለአላህ የሰጠ ሰው ለርሱ በጌታው ዘንድ ምንዳው አለው። በነሱም ላይ ፍርሃት የለባቸውም፤ እነሱም አያዝኑም።"

[አል-በቀራ፡ 112]

እንዲህም ብሏል፦

"ከወንድ ወይም ከሴት እርሱ አማኝ ሆኖ በጎን የሰራ መልካም ኑሮን በእርግጥ እናኖረዋለን፡፡ ይሠሩትም ከነበሩት ነገር በመልካሙ ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን፡፡"

[አን-ነሕል: 97]

የተከበርከው ወንድሜ! ወደ እስልምና በመግባትህ እኮ እግርህ ወደ ምራቻ፣ ብርሃን እና ደስታ እንዲሁም ተድላ ወዳለበት ጎዳና ያመራው። ስለዚህም ወደ እስልምና የገባህበት ቀን እንደ ሌሎች የህይወትህ ቀናት እንዳልሆነ እርግጠኛ ልትሆን ይገባሃል። ይልቁኑ እንደአዲስ የተወለድክበት ቀን ነው!

ልክ ያኔ በተወለድክበት ቀን ከእናትህ ጨለማና ጠባብ ከሆነው ማኅፀን ወጥተህ ወደ ብርሃናማ እና ሰፊ ወደ ሆነው ዓለም እንደመጣሀው ሁሉ ዛሬም ከክህደት ጨለማ ወደ ኢማን (እምነት) ብርሃን ትወጣና ከጥመት ጥበትና ጭንቀት ወደ ሰፊው ቅን ጎዳና ትገባለህ። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ሙት የነበረና ሕያው ያደረግነው ለእርሱም በሰዎች መካከል በእርሱ የሚሄድበትን ብርሃን ያደረግንለት ሰው በጨለማዎች ውስጥ ከርሷ የማይወጣ ሆኖ እንዳልለ ሰው ብጤ ነውን?"

[አል አንዓም፡ 122]

በመሆኑም እንኳን ወደ እስልምና ግዛት በደህና መጣህ! ይህ መጽሐፍ (ቡክሌት) ገና እስልምናን በተቀበልክበት የመጀመሪያው ቀን ልታውቃቸው የሚገቡ አሳሳቢ ጉዳዮችን እና ትልልቅ መሰረቶችን ያካተተ ነው።

መግቢያ

እስልምና እውነተኛው ሃይማኖት ነው።

እስልምና አላህ ለሰው ልጆች ሁሉ የወደደላቸውና የመረጠላቸው እውነተኛው ሃይማኖት ነው። አላህ ከእርሱ ውጪ ሃይማኖትን የማይቀበልበት ብቸኛው ሃይማኖት ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ ዘንድ (የተወደደ) ሃይማኖት ኢስላም ብቻ ነው።"

[አሊ-ዒምራን፡ 19]

ልኡል ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ከኢስላም ሌላ ሃይማኖትን የሚፈልግ ሰው ፈጽሞ ከርሱ ተቀባይ የለውም። እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከከሳሪዎቹ ነው።"

[ኣሊ-ዒምራን፡ 85]

የእስልምናን ሃይማኖት አጥብቆ እና አሳምሮ የያዘ ሰው፥ የሰውን ልጅ ወደ ፈጠረው እና ወደዚህ ሕይወት ወዳመጣው አላህ ለመቃረብ በብርሃማው ቅን ጎዳና ላይ እየተጓዘ ያለ ሰው ነው።

የእስልምና ሃይማኖት የሰው ልጅን ዱንያዊ ህይወት እርጋታንና ደስታን ሊያበጅለት ከሞት በኋላም ባለው ሕይወቱ የላቀው አላህ ጀነት አስገብቶት ዘውታሪ ፀጋን በደስታና ስኬት እንዲኖር የመጣ ሃይማኖት ነው።

ማንኛውም ሰው በዱንያም በአኼራም ህይወቱ መልካሙን ነገር ለመጎናፀፍ እውነተኛውን ሃይማኖት ማለትም እስልምናን መፈለግ፤ ስለ እርሱ ማወቅ፣ አምኖ ወደ እርሱ መግባት፤ አስተምህሮቱንና ህግጋቱን አጥብቆ መያዝ አለበት።

አንድ ሰው ወደ እስልምና የሚገባው እንዴት ነው?

አንድ ሰው ወደ እስልምና የሚገባው፡- በትክክል አምኖበት፣ እርግጠኛም ሆኖ እና መልዕክቱንም አውቆ 'አሽሀዱ አን ላ ኢላሃ ኢለሏህ ወአነ ሙሐመደን ረሱሉሏህ' (ከአላህ በስተቀር ሌላ በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ እና ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ) በሚል የምስክርነት ቃል ነው። በመሆኑም የዚህችን ቃል ትርጉም አውቆ፣ በእውነትም ሆኖ የተናገረ እና ለምታስፈርደውም እውነታ ተገዥ ሆኖ የሚናገር ሰው ወደ እስልምና ይገባል። ከዚያም በመቀጠል የተቀሩትን የእስልምና ተግባራት መማር እና በአቅሙ ልክም መተግበር ይጠበቅበታል። መልካም ስራውም በበዛ ቁጥር እምነቱ እየጨመር የላቀው አላህ ዘንድ ያለው ምንዳም እየገዘፈ ይሄዳል።

የ “ላ ኢላሃ ኢለላህ ሙሐመዱን ረሱሉላህ” የሚለው የምስክርነት ቃል ትርጓሜ፦

በመሆኑም አምነህበት እና በእውነተኝነት ላይ ተመስርተህ 'አሽሀዱ አን ላ ኢላሃ ኢላ አላህ ወአነ ሙሐመደን ረሱል አላህ' (ከአላህ በስተቀር ሌላ በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ፣ ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ) የሚለውን የምስክርነት ቃል ስትሰጥ ወደ እስልምና ሃይማኖት ገብተሃል። ግን ትርጉሙን በትክክል ታውቃለህ?

. የ “ላ ኢላሃ ኢለላህ” የሚለው የምስክርነት ቃል ትርጓሜ፦ ከአንድ አምላክ በቀር አምልኮ እና ፍፁም መታዘዝ የሚገባው አምላክ እንደሌለ ማመን እና ማረጋገጥ (እውቅና መስጠት) ነው። ይሀው አምላክም ጥራት የተገባውና የላቀው የፍጥረተ ዓለሙ ፈጣሪ እና አስተናባሪው አላህ ነው።

. የ “ሙሐመዱን ረሱሉላህ” የምስክርነት ቃል ትርጓሜ፦ ሙሐመድ የአላህ ባሪያ እና ለሰው ልጆችም ሁሉ የተላኩ የመጨረሻ መልዕክተኛ መሆናቸውን ማመንና እርግጠኛ ሆኖ መቀበል ነው። ይህ የምስክርነት ቃል በሚያስፈርደው እውነታም በተግባር መገኘት ሲሆን እነርሱም፦ ያዘዙትን መታዘዝ፣ የተናገሩትን አምኖ መቀበል፣ የከለከሉትንና ያስጠነቀቁትን ነገር መራቅ፣ እርሳቸው በደነገጉት መልኩ ካልሆነ በቀርም አላህን አለማምለክ ነው።

በኢስላም (በመስለምህ) እንኳን ደስ አለህ!

ውዱ ወንድሜ! እስልምናን የተቀበልክበት ቀን የአንተ እጅግ ምርጡ ቀንህ ነው። በእውነቱ ነብያችን ሙሐመድ ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም እንዲህ ማለታቸው በተረጋገጠ ሓዲሥ የተዘገበ ነው፦

"እስልምና ከእርሱ በፊት የነበረውን (ወንጀል) ያፈርሳል።"

ሙስሊም ዘግበውታል

ይህም ማለት ወደ እስልምና ከመግባትህ በፊት የፈጸምከውን ክህደት፣ ክፋት፣ ስህተትና ኃጢያት (በደሎች) ሁሉ ወደ እስልምና በመግባትህ ተሰርዟል ማለት ነው። በመሆኑም ከአላህ በኩል ለተደረገልህ ምህረት እንኳን ደስ ያለህ። ልክ ገና እናትህ እንደ ወለደችህ ቀን ወደ ነበርክበት ንጽሕና በመመለስ፤ በመልካም የተሞላ አዲስ ሕይወትን እንድትጀምር፤ በብርሃን፣ በደስታ እና በፌሽታ በተሞላ ጎዳና ትጓዝ ዘንድ በህይወትህ ውስጥ አዲስ ባዶ ገጽ ከፍተሃል።

በእስልምና ፀጋ መደሰት፦

ወደ እስልምና ስትገባ የተሰማህ ታላቅ ደስታ እድሜ ልክህን አብሮህ ሊቆይ የተገባው ነው። ቅኑን ጎዳና መመራት ከታላላቅ ፀጋዎች (በረከቶች) መካከል እጅግ ታላቁ ነው። የበላይ የሆነው አላህ ባሪያዎቹ ላይ ከለገሳቸው ፀጋዎች ሁሉ ታላቁ ፀጋ ከዋለላቸው ውለታዎችም ሁሉ ታላቁ ውለታ ነው። ከእስትንፋስ፣ ከውሃ፣ ከምግብና ከመጠጥ ጸጋም ሁሉ የሚበልጥ ጸጋ ነው። ከገንዘብ፣ ከሹመትና ከክብርም እንዲሁም ከሌላው ነገርም ሁሉ የበለጠ ታላቁ ፀጋ ነው። ታዲያ እንዲህ ያለው ፀጋ ላይደሰቱበት እንዴት ይቻላል?! የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"«በአላህ ችሮታና በእዝነቱ (ይደሰቱ)፡፡ በዚህም ምክንያት ይደሰቱ፡፡ እርሱ ከሚሰበስቡት ሀብት በላጭ ነው» በላቸው።"

[ዩኑስ፡ 59]

በሚሊዮን ከሚቆጠሩ ሰዎች መካከል አንተን መርጦ ወደ እስልምና እንድትገባ ስላደረገህም አላህ በአንተ ላይ የዋለውን ታላቅ ጸጋ ልታስተውለው ይገባሃል። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፡-

"አላህም ሊመራው የሚሻውን ሰው ደረቱን (ልቡን) ለኢስላም ይከፍትለታል።"

(አል አንዓም፡ 125)

በመሆኑም ይህ ታላቅ በረከት (ፀጋ) እጅግ ብዙ ምስጋና ያስፈልገዋል። ስለዚህም የበላይና ታላቅ የሆነውን አላህ ትክክለኛውን ሃይማኖት ስለመራህ አብዝተህ ማመስገን እና ማወደስም ይገባሃል።

የግድ ማወቅ ያለብህ አስፈላጊ መሠረቶች፡-

ወደ እስልምና ሃይማኖት ከገባህ የግድ መማርና ማወቅ ያለብህ ጉዳዮች አሉ። ከእነርሱም መካከል እያንዳንዱ ሰው ከሞተ በኋላ የሚጠየቃቸው እና የዘላለም እጣ ፈንታውን ወደ ጀነት አልያም ወደ ሲኦል መግባቱን የሚወስኑትን የሦስቱ አንገብጋቢ ጥያቄዎችን መልስ ማወቅ ይገኝበታል። እነርሱም፡-

. ጌታህ ማን ነው?

. ሃይማኖትህ ምንድን ነው?

. ነብይህ ማን ነው?

የመጀመሪያው መሠረት፡ ጌታህ ማን ነው?

ጌታዬ አላህ ነው።

ሙስሊም ይህችን ፍጥረተ ዓለም እና በውስጧ ያለውን ሁሉ የፈጠረ እንዲሁም የሰው ልጅንም የፈጠረው ጌታው (አላህ) እንደሆነ ያምናሉ።

ስለዚህ ታላቅ ፍጥረተ ዓለም እና በውስጡ ስላሉት ግዙፍ ጋላክሲዎች፣ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ፕላኔቶችን እና ከዋክብትን ብናሰላስል፤ ይህች የምንኖርባትን ምድር፣ ሜዳዎቿንና ተራራዎቿን፤ መሬት፣ ወንዞች እና ባሕሮች፤ በጥልቀት ባሕር ውስጥ፣ በበረሃ እና በጫካ ውስጥ ያሉ ድንቅ ፍጥረታት፤ የሰው ልጅንም ይሁን የሌሎችን ፍጥረታት አስደናቂ አፈጣጠር ብናስተውል፤ አስተሳሰባችን ልንሸሸው ወደማንችለው ውጤት የሚያደርሰን ይሆናል፤ ይሀውም የግድ ታላቅ፣ ሁሉን አዋቂ፣ ሁሉን ቻይ እና ጥበበኛ የሆነ ይህንን ፍጥረተ ዓለም የፈጠረና ያስገኘ ፈጣሪ የመኖሩ እውነታ ነው። በመሆኑም እነዚህ ሁሉ ፍጥረታት ያለ ምንም ፈጣሪ አምላክ፣ ሁኔታቸውን የሚያስተናብር እና ለአእምሮ በሚደንቅ መልኩ የሠራቸው አካል ሳይኖር ሊገኙ የማይችሉ ናችው። ይህም ጉዳይ ታላቅና የበላይ የሆነው አላህ አእምሮ ላለው ሰው ሁሉ እንዲህ ሲል በግልፅ ያብራራው ነገር ነው፦

"ወይስ ያለ አንዳች (ፈጣሪ) ተፈጠሩን? ወይስ እነርሱ ፈጣሪዎች ናቸውን?"

[አጥ-ጡር፡ 35]

እነዚህ ፍጡራንም ራሳቸውን አልፈጠሩም፣ ያለ ፈጣሪም (አስገኚም) ድንገት አልተገኙም፤ ይህ ጤነኛ አዕምሮ ላላቸው ሰዎች አሳማኝ ያልሆነ (የማይታሰብ) ነገር ነው!

አላህ ብቻውን ነው አምልኮ የሚገባው፡-

ይህ ጌታ ነው በብኝነት ሊመለክ የሚገባው አምላክ፤ ምክንያቱም በዚህ ዩኒቨርስ (ፍጥረተ ዓለም) ውስጥ ያለ ነገር ሁሉ ፈጣሪ እና አስተናባሪ፤ በውስጧ ላለው ሁሉ ሲሳይን የሚሰጠው፤ ሰዎችን ሁሉ የፈጠረና ወደዚህች ምድርም ያመጣቸው፤ እንዲኖሩም ምክንያት የሆናቸው እርሱው ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ይለናል፦

"ይህ ጌታችሁ አላህ ነው። ከእርሱ በቀር አምላክ የለም፡፡ ነገርን ሁሉ ፈጣሪ ነው። ስለዚህ ተገዙት። እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ተጠባባቂ ነው።"

[አል-አንዓም 102]

ማንኛውም ሰው አላህን በብቸኝነት የማምለክ እና በአምልኮውም ምንንም ነገር ያለማጋራት ግዴታ አለበት። ከፍ ያለው አላህ እንዲህ ብሏል፡-

"እናንተ ሰዎች ሆይ! የፈጠራችሁን እነዚያንም ከናንተ በፊት የነበሩትን (የፈጠረውን) ጌታችሁን ተገዙ፤ (ቅጣትን) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና።"

[አል-በቀራ፡ 21]

ጥራት የተገባው አምላክ አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህንም ተገዙት፤ በርሱም ምንንም አታጋሩ።"

[አን-ኒሳእ: 36]

የነቢያቱም ጥሪ የበላይ የሆነውን አላህ በአምልኮ ብቸኛ አድርጉ የሚል ነው፡-

ምንም እንኳ ይህ ጉዳይ ግልጽ ቢሆንም፤ አሸናፊና የበላይ የሆነው አላህ ከችሮታው፣ ከለጋስነቱና ለእኛ ካለው እዝነት አንፃር ፈጥሮ ሕይወታችን ግራ መጋባት ውስጥ እንዲሆን አልተወንም፤ ይልቁን ወደ እኛ መልክተኞችን ልኮ ከእርሱ ጋ የሚያስተዋውቁንን እና ወደ እርሱም የሚመሩንን መጽሐፎችንም አብሮ አወረደ። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"እኛ አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን በእውነቱ (መምሪያ) ላክንህ። ማንኛይቱም ሕዝብ በውስጧ አስፈራሪ ያላለፈባት የለችም።"

[ፋጢር፡ 24]

የሰው ልጅ አባት የሆኑት አደምም (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ሆኑ ሁሉም ነቢያቶች ኑሕ፣ ኢብራሂም፣ ሙሳ፣ ዒሳ እና ሌሎችም በነቢያችን ሙሐመድ - የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳ ላይ ይስፈን - አማካኝነት ነብይነት እሲኪጠናቀቅ ድረስ የነበሩ ነብያት የተስማሙበት አንድ ትልቅ ጉዳይ አለ፤ ይሀውም ሰዎች የበላይ በሆነው አላህ እንዲያምኑ፣ በብቸኝነት እንዲያመልኩት፣ በአምልኮ እርሱን ብቻ እንዲነጥሉት፣ ከእርሱ ውጪ ያሉ ሌሎች አማልክትን ሰዎችን፣ ድንጋይን፣ ዛፍን፣ ከዋክብትን፣ ፕላኔቶችን ወዘተ ማምለክ እንዲተዉ ጥሪ ማድረግ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ «አላህን ተገዙ፤ ጣዖትንም ራቁ» በማለት መልክተኛን በእርግጥ ልከናል።"

[አን-ነሕል፡ 36]

ታላቅና የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ከአንተ በፊትም እነሆ ከእኔ ሌላ አምላክ የለምና ተገዙኝ በማለት ወደርሱ የምናወርድለት ቢሆን እንጅ ከመልክተኛ አንድንም አልላክንም።"

[አል-አንቢያእ፡ 25]

ከአላህ ስምና ባህሪያት መካከል፦

የበላይ የሆነው አምላክ አላህ ውብ የሆኑ ስሞችና የላቁ ባሕርያት አሉት። እነርሱን ይበልጥ እያወቅናቸው ስንሄድ ጥራት የተገባውና የበላይ ስለሆነው ጌታችን አላህ ይበልጥ እያወቅን እንሄዳለን። ለእርሱ ያለን ውዴታና ፍራቻ፣ ለጸጋው እና ልግስናው ያለን ክጃሎት ይበልጥ እየጨመረ ይሄዳል። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም። ለእርሱ መልካሞች የሆኑ ስሞች አልሉት።"

[ጣሀ፡ 8]

ባህሪያቱንም አመላካች የሆኑት ስሞቹ በርካታ ናቸው። የበላይ ከሆነው የአላህ ስሞች መካከልም፡-

§ አርረሕማን (እጅግ በጣም ሩኅሩህ) እና አርረሒም (በጣም አዛኝ) : የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አምላካችሁም አንድ አምላክ ብቻ ነው፤ ከርሱ በቀር ሌላ አምላክ የለም። (እርሱ) እጅግ በጣም ርኅሩህ አዛኝ ነው።"

[አል-በቀራ፡ 163]

እርሱ የሰፊ እዝነት ባለቤት፤ እዝነቱም ሁሉንም ነገር ያካተተና ሁሉንም ፍጥረት ያጠቃለለ ታላቅ ነው። እዝነቱ በዚህ ዓለም ላይ ያለውን ፍጥረት ሁሉ እንስሳትንም ይሁን የሰዎች ልጆችን ሙስሊም የሆኑትንም ይሁን ሙስሊም ያልሆኑትን ያጠቃለለ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ችሮታየም (እዝነቴም) ነገሩን ሁሉ ሰፋች።"

[አል-አዕራፍ፡ 156]

ሁሉንም ሲሳይ የሚለግሳቸው ጤና ምግብ ልጆችና የመሳሰሉትንም የሚሰጣቸውም እርሱው ነው። በመጨረሻይቱ ዓለም ያለው እዝነቱ ግን ከባሮቹ መካከል ነብያትን እና መልዕክተኞቹን ለተከተሉ ምእመናን ብቻ የሚሆን ነው። ለነርሱ ታዲያ ዘለአማዊ ወደ ሆነ ደስታ የሚያደርስ ሙሉ የሆነ እዝነት አለላቸው።

§ አል'ኻሊቅ (ትርጉሙም: የሁሉም ፈጣሪ)፦ የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው።"

[አዝ-ዙመር፡ 62]

እርሱ ያ ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም የፈጠረ ነው። ሁሉንም ነገር ከትንሿ አተም እስከ ትልቁ ጋላክሲ ያለውን የበለጠ ሰፊ የሆነውንም የፈጠረ እርሱው ነው። አፈጣጠሩም እንዲሁ በጥበብ፣ በችሎታና በችሮታው የተሟላ ነው፤ በመሆኑም በእርሱ ፍጥረት ውስጥ ምንም ዓይነት እንከንም ይሁን መዛነፍ አታገኝም።

§ አል'ገፉር (መሀሪ/ ይቅር ባይ)፦ ያ እውነተኛ ሆኖ ንስሐ (ተውበት) ላደረገ ሁሉ ኃጢአቱን በሙሉ ይቅር የሚል ነው፤ በቀድሞ ጊዜ የትኛውንም ዓይነት (መጥፎ) ሥራ ፈፅሞም ቢሆን ከቸርነቱ አንፃር ከፍጡራኖቹ በአላህ አምልኮ ላይ ከሚፈፀም ሽርክ (ማጋራት) በቀር ብዙውን ይቅር የሚል ነው። ሽርክ ግን በተውባ ካልሆነ በስተቀር ፈፅሞ የማይማር ወንጀል ነው። አላህ ለፍጥረታቱ በንስሐ፣ መሀርታውን በመማፀን፣ በኢማን፣ በበጎ ሥራ እና ለአላህ ፍጥረታት በጎ በማድረግ በተለያዩ መንገዶች የእርሱን መሀርታ የሚያገኙበትን እድሎች ክፍት አድርጓል። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"እኔም ለተጸጸተ፣ ላመነም፣ መልካምንም ለሠራ፣ ከዚያም ለተመራ ሰው በእርግጥ መሓሪ ነኝ።"

[አን-ነጅም፡ 82]

§ አር'ረዛቅ (ሲሳይ ለጋሽ)፦ ጥራት የተገባው አላህ የሁሉ ንግስና በእጁ የሆነው ንጉሥ እርሱው ነው፤ እንዲሁም ሀብታም ነው፤ ከችሮታውም መካከል አንዱ ስጦታ እርሱ ሰጪ መሆኑ ነው፤ ከፍጡራኑም መካከል ሲሳዩ ከአላህ ያልሆነ ማንም የለም። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ጂኒንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም። *

ከእነርሱም ምንም ሲሳይ አልፈልግም። ሊመግቡኝም አልሻም። *

አላህ እርሱ ሲሳይን ሰጪ የብርቱ ኀይል ባለቤት ነው።"

[አዝ-ዛሪያት: 56-58]

§ አስ'ሰላሙ (ሰላም የሆነ):- (አላህ) ከማንኛውም ዓይነት ነውር የፀዳና የእንከን የለሽ ባህሪያት ባለቤት ታላቅ (አምላክ) ነው። የምሉእነት፣ ግርማ እና ውበት ባለቤት እንዲሁም በቃልም ይሁን በተግባር ሰላምን የሚያስፋፉ (የሚያሰራጩ) ባሪያዎቹንም የሚወድ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"እርሱ አላህ ነው፤ ያ ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለ። ንጉሡ ከጉድለት የላቀው፣ የሰላም ባለቤቱ።"

[አል-ሐሽር፡ 23]

§ አል'ዐሊም (አዋቂ)፦ ጥራት የተገባው አላህ ሰሚ፣ ተመልካችና ዐዋቂ ነው። እውቀቱ ሁሉንም ነገር ያካበበ ነው። እርሱ ግልፅ የወጣውንም፣ ድብቅ የሆነውንም፣ በልቦች ውስጥ የተደበቀውንም ሁሉ ዓዋቂ ነው። ባለፈው ጊዜ የተከሰተውን፣ አሁን ላይ እየሆነ ያለውን እንዲሁም ወደፊት ምን እንደሚሆንም ያውቃል፤ የባሪያዎችን ሥራ የሚቆጣጠው ተመልካች እርሱው ነው። የታዛዦች ታዛዥነትም ሆነ የአመፀኞች ኃጢአት፤ የደካሞች ፍላጎትም ሆነ የደካሞች ተማፅኖ የማይደበቅበት ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህም ስለ ነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው።"

[አል-በቀራ፡ 231]

የላቀው አላህ የዓለማት ጌታ፤ ሁሉንም ነገር ውብ አድርጎ የፈጠረም ነው፤ በዚህ ምድር ላይ ያለው መልካም (ውብ) እና የተሟላ ነገር ሁሉ ጥራት የተገባው አላህ የእርሱ ፍፁምነት ውጤት ፋና ነው።

ሁለተኛው መሠረት፡ ሃይማኖትህ ምንድን ነው?

ሃይማኖቴ እስልምና ነው፦

ኢስላም ማለት፦ ለአላህ ትዕዛዝ ሁለመናን ሰጥቶ እርሱን በብቸኝነት ማምለክ፣ ለትዕዛዙ ፍፁም ታዛዥ መሆን (መጎተት)፣ ከሺርክም ሙሉ በሙሉ መጥራት ነው።

ሙስሊም ማለት፦ ወደ እስልምና ሃይማኖት የገባ፤ ጉዳዩን ሁሉ ለኃያሉ አላህ አሳልፎ የሰጠ፣ በአላህ ህልውናና ብቸኝነት ያመነ፣ ለትእዛዙም ተገዢ የሆነ፣ ከከለከለው ነገርም የራቀ ነው። የበላይ የሆነው አላህ በተከበረው ቁርኣን እንዲህ ብሏል፦

"እርሱ መልካም ሠሪ ሆኖ ፊቱን ለአላህ ከሰጠና የኢብራሂምንም መንገድ ቀጥተኛ ሲሆን ከተከተለ ሰው ይበልጥ ሃይማኖቱ ያማረ ማን ነው?"

[አን-ኒሳእ: 125]

እንዲህም ብሏል፦

"ወደ አላህ ከጠራና መልካምንም ከሠራ፣ «እኔ ከሙስሊሞች ነኝ» ካለም ሰው ይበልጥ ቃሉ ያማረ ማን ነው?"

[ፉሲለት፡ 33]

የእስልምና ሃይማኖትን ውብት ከሚያሳዩ ነገራቶች መካከል፡-

· እስልምና የፍትህ ሀይማኖት ነው፦ ከቅርብም ከሩቅም፣ ከጠላትም ከወዳጅም፣ ከአማኝም ከከሀዲም ጋር ፍትሃዊ እንድንሆንም የሚያዝ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ ማስተካከልን (ፍትህን) ያዛል።"

[አን-ነሕል: 90]

ኃያልና የበላይ የሆነው አላህ እርሱ ዘንድ ማንም የማይበደል ፍትሃዊ ዳኛ ነው። የበላይ የሆነው አላህ ስለ ቂያማ (ትንሳኤ) ቀን አስመልክቶ እንዲህ ብሏል፡-

"ዛሬ ነፍስ ሁሉ በሠራችው ሥራ ትምመነዳለች። ዛሬ በደል የለም።"

[ጋፊር: 17]

· እስልምና የእዝነት ሃይማኖት ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም።"

[አል-አንቢያእ: 107]

የአላህ መልዕክተኛም የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን እንዲህ ብለዋል፦

"አዛኞች እጅግ በጣም አዛኝ የሆነው አላህ ያዝንላቸዋል፤ በምድር ላሉት እዘኑ በሰማይ ያለው (አላህ) ያዝንላችኋል።"

አቡዳውድ ዘግበውታል።

· እስልምና የፍቅር፣ የህብረት እና የመተሳሰብ ሃይማኖት ነው። የአላህ መልዕክተኛ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን እንዲህ ብለዋል፦

"አንዳችሁም ለራሱ የሚወደውን ለወንድሙ እስካልወደደ ድረስ እምነቱ አልተሟላም።"

ቡኻሪይ ዘግበውታል።

· እስልምና ገር ሃይማኖት ነው። የእስልምና አስተምህሮ የተመሰረተው ነገራቶችን በማግራራትና ችግሮችን በማስወገድ ላይ ነው፤ ይህንንም ስለ እስልምና ሃይማኖት ጥናት ያደረገ ሁሉ የሚረዳው እውነት ነው።

"አላህ ለእናንተ ገሩን (ነገር) ይሻል። ለእናንተም ችግሩን አይሻም።" [አል-በቀራ: 185]

አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ በእናንተ ላይ ምንም ችግር ሊያደርግ አይሻም።"

[አል-ማኢዳ: 6]

አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ ነፍስን ከችሎታዋ በላይ አያስገድዳትም።"

[አል-በቀራ: 286]

· እስልምና የዕውቀት ሃይማኖትም ነው። ከቁርኣን የወረደው የመጀመሪያው አንቀጽ የሚከተለው ነው፡-

"አንብብ በዚያ (ሁሉን) በፈጠረው ጌታህ ስም።"

[አል-ዐለቅ: 1]

እስልምና እያንዳንዱ ሙስሊም ወንድም ሆነ ሴት እንዲማር እና ዕውቀቱንም እንዲጨምር አጥብቆ ያበረታታል። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ጌታዬ ሆይ! እውቀትንም ጨምርልኝ! በል።"

[ጧሀ: 114]

የእስልምናን አስተምህሮ የተማረ ሰው እጅግ ከፍተኛ ደረጃ አለው። ጥራት የተገባውና የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አላህ ከናንተ እነዚያን ያመኑትንና እነዚያንም ዕውቀትን የተሰጡትን በደረጃዎች ከፍ ያደርጋል።"

[አል-ሙጃዲላ፡ 11]

የእስልምና ሃይማኖት ዓለም አቀፋዊነት፡-

እስልምና ዓለም አቀፋዊ ሃይማኖት ነው። ከሌላው የምድር ክፍል ተለይቶ ለአንዱ ብቻ የተወሰነ፤ ከአንድ ህዝብ ተለይቶ ለአንዱ ብቻ የተሰጠ አይደለም፤ የዐረቦች ብቻም ሃይማኖት አይደለም። ይልቁን ለሁሉም ሰው ልጆች (ከአላህ የተለገሰ) ሃይማኖት ነው። የበላይ የሆነው አላህ ነቢዩ ሙሐመድን የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን በተከበረው ቁርኣን ውስጥ ሲያናግራቸው እንዲህ ብሏል፡-

"(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው፡- «እናንተ ሰዎች ሆይ! እኔ ወደናንተ ወደ ሁላችሁም የአላህ መልክተኛ ነኝ፡፡ (እርሱም) ያ የሰማያትና የምድር ንግሥና ለእርሱ ብቻ የኾነ ነው፡፡ እርሱ እንጂ ሌላ አምላክ የለም፡፡ ሕያው ያደርጋል፡፡ ይገድላልም፡፡ በአላህ በዚያም በአላህና በቃላቶቹ በሚያምነው የማይጽፍ የማያነብ ነቢይ በሆነው መልክተኛው እመኑ፡፡ ቅንንም መንገድ ትመሩ ዘንድ ተከተሉት።"

[አል-አዕራፍ፡ 158]

ኢስላም ለባለፈው ዘመን ተገድቦ የቀረ ሃይማኖትም አይደለም፤ ይልቁን ከነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም መላክ ጀምሮ እስከ ዕለተ ትንሳኤ ድረስ (የሚዘልቅ) እውነተኛ ሃይማኖት ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ከኢስላም ሌላ ሃይማኖትን የሚፈልግ ሰው ፈጽሞ ከርሱ ተቀባይ የለውም። እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከከሳሪዎቹ ነው።"

[አሊ-ዒምራን፡ 85]

የእስልምና ሃይማኖት ሁለንተናዊነት፦

- እስልምና የህይወት መንገድ ነው፦ ለሙስሊም ግለሰብ ይሁን ማህበረሰብ እንዲሁም ህዝብ በሁሉም ዘርፍ በፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ሶሺዮሎጂ እና ሌሎችም መስኮች የተሟላ መመርያ ያለው የህይወት ጎዳና ነው።

- እስልምና እምነት እና መመርያ ነው፡- ትክክለኛ እምነቶችን፣ ታላላቅ አምልኮዎችን፣ በጥበብ የተሞሉ መስተጋብሮችን፣ የተዋቡ ሥነ-ምግባራትን እና ስርዓት የተበጀላቸው አካሄዶችን ያካተተ ነው።

- የእስልምና አስተምህሮዎች እና ህግጋት አንድ ሰው ከጌታው ጋ፤ የሰው ልጅ ከራሱ ጋ፤ አንድ ሰው ከሌሎች ሰዎች ጋ እንዲሁም ከእንስሳት እና ግዑዝ ነገሮች ጋ ያለው ግንኙነት እንኳን ሳይቀር ያስተካክላል።

- የእስልምና አስተምህሮዎች ነፍስንም ሆነ አካልን ከማስተካከል ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን አጠቃለው (አካተው) የያዙ ናቸው።

በጥቅሉ፡- እስልምና የመጣው የሰዎችን መልካምነት፣ መስተካከል እና በቅርቢቱ ዓለምም ሆነ በመጨረሻው ዓለም ደስታን የሚያስገኝላቸውን መመርያ ይዞ ነው።

የእስልምና እምነት መሠረቶች (የእምነት ማዕዘናት)፡-

የእስልምና እምነት የሚወከለው ስድስት ጉዳዮችን በፅኑ በማመን እና እውነት ብሎ በመቀበል ሲሆን እነርሱም (የእምነት መሠረቶች) በመባል የሚታወቁት ናቸው፡-

1- የበላይ በሆነው አላህ ማመን፡- ማለትም በአላህ መኖር ማመን፤ እርሱ ብቻ የፍጥረተ ዓለሙና በውስጡ ያለው ሁሉ ፈጣሪ፣ ባለቤት (ንጉስ) እና አስተናባሪ መሆኑን፤ እርሱ ብቻ ያለ ምንም ተጋሪ አምልኮ የሚገባው መሆኑን እንዲሁም እርሱ ብቻ ውብ በሆኑ እና ልቅና ባላቸው ባህሪያት የሚገለፅ፤ ምሉእ እና ከማንኛውም ነውርም እንከንም የጸዳ እንደሆነ እና እርሱን የሚመስል ምንም ነገር እንደሌለ ማመን ነው።

2- በመላእክት ማመን፦ መላእክት የበላይ የሆነው አላህ ከፈጠራቸው ፍጥረታት መካከል የሆኑ ፍጡራን፤ የፈጠራቸውም እርሱን እንዲያመልኩ እንደሆነ፤ እነርሱም ለትዕዛዙ ሙሉ በሙሉ ተገዢ የሆኑ፤ ኃላፊነት የተጣለባቸውን ተግባራት ለመፈፀም የቆሙ ናቸው። በጥቅሉ እነርሱ እንዳሉ እናምናለን፤ በወሕይ (መለኮታዊ ራዕይ) የተገለፀልንን ስሞች፣ ባህሪያት እና ተግባራቸውንም በዝርዝር (ለምሳሌ ያክል) ጂብሪል አላህ ወደ ነቢያትና መልእክተኞች ወሕይ ለማድረስ የተመደቡ መሆናቸው፤ ሚካኢልም ዝናብንና ዕፅዋትን በተመለከተ እንደተመደቡ፤ ኢስራፊል ጡሩንባ (ሱር) እንዲነፉ መመደባቸውን፤ መለከል መውት የሰውን ነፍስ በመውሰድ ላይ መወከላቸውን እንዲሁም ማሊክ የጀሀነም እሳት በር ጠባቂ መሆናቸውን እናምናለን።

3- በመጻሕፍቱ ማመን፦ ማለትም አላህ በመልክተኞቹ ላይ ለፍጥረታቱ ባለው ርህራሄ ወደ ቀጥተኛው ጎዳና ሊመሩ ዘንድ እንዲሁም በዚህ ዓለምም ሆነ በመጨረሻው ዓለም ደስታን እንዲያገኙ ባወረዳቸው መጻሕፍት ማመን ነው። በጥቅሉ በመጻሕፍቱ እናምናለን፤ በወሕይ (መለኮታዊ ራዕይ) ስማቸውን ዝርዝር በሆነ መልኩ በተገለፀልን ለምሳሌ ለነብያችን ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በወረደላቸው ቁርኣን፤ ለዒሳ (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በወረደላቸው ኢንጂል (ወንጌል)፤ ለሙሳ (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በወረደላቸው ተውራት (ኦሪት)፤ ለዳውድ (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በተሰጣቸው ዘቡር (መዝሙረ ዳዊት) እና አላህ ወደ ኢብራሂም (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ባወረደላቸው ሱሑፎች እናምናለን።

4- በመልዕክተኞች ማመን፡- የበላይ የሆነው አላህ ቅኑን ጎዳና በወሕይ (መለኮታዊ ራዕይ) የገለጠላቸውና ሃይማኖቱንም ወደሰው ልጆች ያደርሱ ዘንድ የላካቸው ሰዎች ናቸው። የመጀመርያቸው ኑሕ (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ሲሆኑ የመጨረሻቸው ደግሞ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ናቸው። በሃይማኖትም ሆነ በሥነ-ምግባር ምሉእ ነበሩ። የተላኩበት ዋና አላማ ለሰዎች የበላይ የሆነውን አላህ በአምልኮ ብቸኛ እንዲያደርጉ (እንዲነጥሉ) እንዲሁም ሽርክን እና ከአላህ ውጪ የሚመለክ ማንኛውንም ነገር እንዲተዉ ጥሪ ሊያደርጉ ዘንድ ነው።

አላህ መልክተኞችን ከሰዎች መካከል እንደላከ እናምናለን። መልክተኞቹ የተናገሩትን ማመን፣ እነርሱን መከተልና ያዘዙትን መታዘዝም በባሮቹ ላይ ግዴታ አድርጓል። ከእነርሱ መካከል አላህ ስማቸውንና ከህዝቦቻቸው ጋ የነበራቸውን ታሪክ የተረከልንን እንደ ኢድሪስ፣ ኑሕ፣ ኢብራሂም፣ ሙሳ፣ ዒሳ፣ ሁድ፣ ሷሊሕ እና ሹዐይብ እንዳሉት ሁሉ፤ ከእነርሱ መካከል አላህ ስሞቻቸውን ያልነገረን እንዳሉም እናውቃለን (እናምናለን)። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ካንተ በፊትም መልክተኞችን በእርግጥ ልከናል። ከእነርሱ ባንተ ላይ የተረክንልህ አልለ። ከእነርሱም ባንተ ላይ ያልተረክነው አልለ። ለማንኛውም መልክተኛ በአላህ ፈቃድ ካልሆነ ተዓምርን ሊያመጣ አይገባውም። የአላህም ትእዛዝ በመጣ ጊዜ በእውነት ይፈረዳል። እዚያ ዘንድም አጥፊዎቹ ይከስራሉ።"

[ጋፊር፡ 78]

5- በመጨረሻው ቀን ማመን፦ ይሀውም አላህ ሰዎችን የሚቀሰቅስበት እና በቅርቢቱ ዓለም ላይ በሰሩት ስራም የሚተሳሰብበትና የሚመነዳበት የትንሣኤ ቀን ነው። የዚያኔ ሰዎችም ለሁለት ይከፈላሉ፤ ምእመናን በጀነት ውስጥ በርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ሆነው ይሰፍራሉ፤ ከሓዲያንም በውስጧ ዘውታሪዎች ሆነው በእሳት ውስጥ ይኖራሉ። አማኝ ሰው ሆኖ ነገር ግን ኃጢአትን የሠራ ከሆነ ወይ የበላይ የሆነው አላህ ኃጢዓቱን ይቅር ይለዋል አሊያም ለተወሰነ ጊዜ (በወንጀሉ ልክ) ይቀጣና ከዚያም ጀነት ይገባል።

6- ጥሩም ሆነ መጥፎ በቀደር (በአላህ ውሳኔ) ማመን፡- አላህ የሆነውን እና የሚሆነውን እንደሚያውቅ፤ አላህ የፍጡራንን እጣ ፈንታ እንደጻፈ፣ ፈልጎም እንዳስገኘው፤ በፍጥረተ ዓለሙ ውስጥ እርሱ ሳያውቀው፣ ሳይጽፈው፣ ሳይፈልገው እና ሳይፈጥረው ምንም ነገር እንደማይከሰት ሙስሊም ያምናል። በመሆኑም መልካም ነገር ከተከሰተ የበላይ ከሆነው አላህ እዝነት፤ ካልሆነ ግን የበላይ ከሆነው አላህ ፈተና ወይም ቅጣት ነው። ማንም ሰው ሊረዳው በማይችለው ታላቅነቱና ፍፁምነቱ የበላይ በሆነው አላህ ጥበብ እና ፍትህ የተከናወነው ነው። አንድ የአላህ ባሪያ በመልካምም ይሁን መጥፎ የአላህ ቀደር (ቅድመ ውሳኔ) ካመነ ልቡ ይረጋጋል፣ ነፍሱም ትረካለች፣ ጉዳዮቹንም ሁሉ የበላይ ለሆነው አላህ አሳልፎ ይሰጣል። ምክንያቱም ሁሉም ነገር በአላህ እጅ ብቻ እንደሆነ ያውቃልና፤ እርሱ የፈለገው ይሆናል ያልፈለገው ደግሞ አይሆንም።

የእስልምና ማዕዘናት፦

የእስልምና ማዕዘናት (ምሶሶዎች) የሚባሉት እስልምና የተገነባባቸው መሠረቶች ናቸው። አንድ ሙስሊም ሊያሟላቸው ግዴታ የሆኑ አምስት መሰረቶች አሉ:

1- ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ ሌላ አምላክ በፍፁም እንደሌለ እና ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን መመስከር፦ ይህች ምስክርነት በአንደበት የምትነገር ቃል ልብም አላህ ብቸኛና ተጋሪ የሌለው በእውነት የሚመለክ መሆኑን እና ሙሐመድ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን አላህ ያወረደውን መልዕክት የሚያደርሱ መልእክተኛ መሆናቸውን አምኖ የሚቀበላት ምስክርነት ነች።

2- ሶላት (ደንብና ስርዓት ጠብቆ) መስገድ:- አንድ ሙስሊም በቀንና በሌሊት አምስት ወቅት ሶላቶችን የመስገድ ግዴታ አለበት። የበላይ የሆነውን አላህ ለማላቅ ሲባል ሶላት ውስጥ መቆም፣ መጎንበስ (ሩኩዕ) እና በግንባር መደፋት (ሱጁድ) አለ። እያንዳንዱ የሶላት ወቅቶች የየራሳቸው መጠሪያ ስም አላቸው እነርሱም፦ የፈጅር፣ የዙሁር፣ የዐስር፣ የመግሪብ እና የዒሻእ ሶላት ናቸው፤ በተጨማሪም ሌሎች ግዴታ ያልሆኑ ሶላቶችም አሉ።

3- ዘካ መስጠት፡- ለዘካ የደረሰ የገንዘብ መጠን ያለው ሙስሊም ከገንዘቡ ትንሽ እና የተወሰነ መጠን ለሚገባቸው ድሆች፣ ችግረኞች እና ለመሳሰሉት ዘካ የሚገባቸው ሰዎች መስጠት ነው።

4- ረመዷንን መጾም፡- አንድ ሙስሊም በረመዷን ወር ጎህ ከቀደደበት ጊዜ ጀምሮ ጀንበር እስከምትጠልቅበት ጊዜ ድረስ ከምግብ፣ ከመጠጥ፣ ከግብረ-ስጋ ግንኙነት እና ሌሎች ከፆምን የሚያበላሹ ከሆኑ ነገሮች አላህን ለማምለክ አስቦ መታቀብ ነው።

5- የአላህን ቤት መጎብኘት (ሐጅ ማድረግ)፦ አንድ ሙስሊም ወደ ተከበረችው መካ የሐጅ ሥርዓትን ለመፈፀም የበላይ የሆነውን አላህ ለማምለክ አስቦ መጓዝ ነው። ለቻለ ሰው በህይወቱ አንድ ጊዜ እንኳን ቢሆን የመሄድ ግዴታ አለበት።

አምልኮ (ዒባዳ) በእስልምና፡-

አምልኮ (ዒባዳ) ማለት፡- የበላይ የሆነው አላህ የሚወዳቸውንና የሚቀበላቸውን ጉልህም ይሁኑ ድብቅ ቃላትንና ተግባራትን በመፈፀም ወደ አላህ መቃረብ ነው።

ከቃላት መካከል፡- ቁርኣን ማንበብ፣ ዱዓእ ማድረግ፣ የላቀው አላህን ማውሳት፣ ጠቃሚ እውቀትን ማስተማር፣ ለሌሎች ምክርን መለገስ እና የመሳሰሉት ይገኙበታል።

ከድርጊቶች መካከል፡- ንጽህና፣ ሶላት፣ ሐጅ፣ የሰዎችን ጉዳይ ለመፈፀም መሯሯጥ የመሳሰሉት ይገኙበታል።

ጉልህ የሆኑት ሲባል፦ ማለትም ክንውናቸው ግልፅ የሆኑ፣ የሚታዩና የሚሰሙ እንደ ሰላት፣ ሐጅ፣ ቁርኣን ማንበብ፣ ወደ አላህ መጣራት እና ዝምድና መቀጠል የመሳሰሉት ናቸው።

ድብቅ የሆኑት ሲባል፡- ማለትም ክንውናቸው በልብ ውስጥ የሆኑ ሥራዎች እንደ አላህን መውደድ፣ ተስፋን በአላህ ላይ ማድረግ፣ አላህን መፍራት፣ ለአላህ መተናነስ እና በአላህ ላይ መመካት የመሳሰሉት ናቸው።

የአምልኮ አስፈላጊነት በእስልምና፡-

አላህን ማምለክ አላህ ለእርሱ ሲል ሰዎችን የፈጠረበት ዓላማ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"አጋንንትንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም።"

[አዝ-ዛሪያት፡ 56]

አምልኮ የተደነገገው በሰዎች ነፍስና ሕይወታቸውም ላይ እውን እንዲሆኑ ለሚፈለጉ ታላላቅ ጥበቦችና በርካታ ጥቅሞች ነው። ከአምልኮ ፋይዳዎች መካከል ነፍስን ያስውባል፣ ያጠራል፤ እንዲሁም ወደ ከፍተኛ የሰው ልጅ ምሉእነት ደረጃ ከፍ ያድርጋል።

አምልኮ ለሰው ልጅ እጅግ በጣም የሚያስፈልገው ነገር ነው፤ ሰውነቱ ምግብና መጠጥ እንደሚያስፈልገው ሁሉ ልቡና ነፍሱም በአምልኮ ወደ አላህ መመለስ ያስፈልጋቸዋል። አላህን በማውሳትና በአምልኮቱ ካልሆነ በስተቀር ነፍስ ዕረፍትና እርካታ የላትም፤ የበላይ ወደሆነው አላህ በመቅረብ እና ከእርሱ ጋር ያለንን ቁርኝት በማሳመር ካልሆነ በስተቀር ቀልብ ደስተኛ፤ ልብም ክፍት (ሰፊ) አትሆንም። እውነተኛው የአምልኮ ሰዎችም ከሰዎች ሁሉ የበለጠ ደስተኛ፤ ሰፊ ልብ ያላቸውም እነርሱው ናቸው። ደስታን የሚፈልግ ለአላህ ብቻ የማገልገል ደረጃን አጥብቆ ይያዝ።

የአምልኮ ሁለንተናዊነት በእስልምና፡-

አምልኮ በእስልምና አላህ የሚወዳቸውን መልካም ሥራዎችን ሁሉ የሚያጠቃልል ነው። ይህንንም በማድረግ ወደ እርሱ እንቃረባለን። የሚከተሉትንም ያካትታል፦

- የአምልኮ ሥርዓቶች፡- ለምሳሌ ያክል ሶላት፣ ዘካ፣ ፆም፣ ሐጅ፣ ቁርኣን ማንበብ፣ ዱዓ፣ አላህን ማውሳት እና የመሳሰሉት ይገኙበታል።

- መልካም መስተጋብር፦ ለወላጆች መልካም መዋል፣ ዝምድናን መቀጠል፣ ከሚስት እና ልጆች ጋ በመልካም መኗኗር፣ በጥሩ ሁኔታ መገበያየት፣ ሥራን በጥራት መሥራት፣ ለጎረቤት መልካም መዋል፣ ለእንስሳት መልካም ማድረግና የመሳሰሉት ይገኙበታል።

- እንደዚሁም መልካም ስነምግባርን እውነት መናገርን፣ አደራ መወጣትን፣ ቃልን መሙላትን፣ ፈገግታ ማሳየትን፣ መልካም መናገርን የመሳሰሉትን ምግባሮችንም ያጠቃልላል።

ሙስሊሙ በሁኔታውም ሁሉ አላህን ያመልካል፤ በመስጊድም፣ በቤት ውስጥም፣ በስራ ቦታ እና በሁሉም ቦታ አላህን ያመልካል። ህይወቱ በሙሉ ለአላህ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"«ስግደቴ፣ መገዛቴም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም ለዓለማት ጌታ ለአላህ ነው» በል።"

[አል-አንዓም፡ 162]

ሦስተኛው መሠረት፡ ነብይህ ማን ነው?

የእኔ ነብይ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ናቸው፦

ነብያችን:- ሙሐመድ ቢን ዐብደላህ ቢን ዐብዱል ሙጠሊብ ቢን ሃሺም ሲሆኑ የዘር ሀረጋቸው የነብዩላህ ኢብራሂም ልጅ ወደሆኑት ነብዩላህ ኢስማኢል የአላህ ሰላም በእነርሱ ላይ ይስፈን ይመለሳል።

ነብዩ ሙሓመድ (ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም) በተከበረችው መካ ከተማ ሳሉ ዕድሜያቸው አርባ ዓመት ሲሞላ አላህ ነብይ አድርጎ ላካቸው፤ ቁርኣኑንም በእርሳቸው ላይ አወረደ፤ ሰዎችንም ወደ ተውሒድ (አላህን በብቸኝነት ወደ ማምለክ) እና ወደ እስልምና ሃይማኖት ተጣሩ፤ ሕዝባቸውም እጅግ በጣም በከበደ ሁኔታ አስቸገሯቸው፤ ባልደረቦቻቸውን አሰቃይተው ብዙዎችንም ገደሉባቸው፤ ከዚያም ከአሥራ ሦስት ዓመታት በኋላ ወደ የሥሪብ ከተማ ተሰደዱ (ከዚያም ስሟ አል-መዲነቱ አን-ነበዊይ በመባል ተሰየመች)፤ በመዲናም የእስልምናን መንግሥት አቋቋሙ፤ ኢስላማዊ ማህበረሰብም መሠረቱ፤ እዚያም እየመሩ፣ እያመላከቱ፣ (ዳዕዋ) ጥሪም እያደረጉ እና እያስተማሩ ለአሥር ዓመታት ቆዩ፤ የሸሪዓ ህግ ተሟልቶ እስኪደነገግ ድረስም በዚሁ ዘለቁ፤ በዚህም እስልምና ተሟላ ሃይማኖቱም ሙሉ ሆነ። የላቀው አላህ ቀጣዩ አንቀፅም ወረደ፦

"ዛሬ ሃይማኖታችሁን ለናንተ ሞላሁላችሁ፡፡ ጸጋዬንም በናንተ ላይ ፈጸምኩ። ለእናንተም ኢስላምን ከሃይማኖት በኩል ወደድኩ።"

[አል-ማኢዳ: 3]

ነብዩ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን ሰዎች በፍቅር እና በፈቃዳቸው ወደ አላህ ሃይማኖት ሲገቡ በማየት የዓይን ማረፊያ ካገኙ በኋላም ሕይወታቸው አለፈች። የላቀውና የበላይ የሆነው አላህ እንዳለው፦

"የአላህ እርዳታና (መካን) መክፈት በመጣ ጊዜ፤ (1)

ሰዎችንም ጭፍሮች እየሆኑ፤ በአላህ ሃይማኖት ውስጥ ሲገቡ ባየህ ጊዜ፤ (2)

ጌታህን ከማመስገን ጋር አጥራው። ምሕረትንም ለምነው። እርሱ ጸጸትን በጣም ተቀባይ ነውና።"

[አን-ነስር፡ 1-3]

የእዝነቱ ነቢይ፦

ነብያችን ሙሀመድ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን የእዝነት ነብይ ናቸው። በሁሉም የህይወት ታሪካቸው፤ በሁሉም የህይወታቸው እርከን እና ሁኔታቸው ሁሉ እዝነት ተለይቷቸው አያውቅም። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም።"

[አል-አንቢያእ: 107]

እዝነታቸው ከተገለፀባቸው ጉዳዮች መካከል የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና ሰዎችን ወደ ቅኑ ጎዳና እንዲመሩ ከፍተኛ ፍላጎት ነበራቸው፤ ከክህደት፣ ከድንቁርና እና ከፈተና ጨለማ ወደ እምነት ብርሃን፣ ዕውቀትና ቀና ጎዳና ለማውጣት የሚጥሩ መሆናቸው ነበር። ሕዝቦቻቸው አናምንም ባሏቸው ጊዜ (ህዝቡ) ባለማመኑ ምክንያት በሀዘንና ትካዜ ነፍሳቸውን ሊስቱም ተቃርበው ነበር። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"በዚህም ንግግር (በቁርኣን) ባያምኑ በፈለጎቻቸው ላይ በቁጭት ነፍስህን አጥፊ ልትሆን ይፈራልሃል።"

[አል-ከህፍ፡ 6]

ልክ እንደዚሁ የአዛኝነታቸው ፍቺ ለምእመናን ባላቸው ጉጉት (ተቆርቋሪነት) እና ለእነርሱ ባላቸው ርህራሄም ጎልቶ የታየ ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"ከጎሳችሁ የሆነ ችግራችሁ በእርሱ ላይ ጽኑ የሆነ፣ በእናንተ (እምነት) ላይ የሚጓጓ፣ በምእምናን (ላይ) ርኅሩኅ አዛኝ የሆነ መልክተኛ በእርግጥ መጣላችሁ።"

[አት-ተውባ፡128]

ለምእመናን የነበራቸው ጉጉት ከተገለፀባቸው አጋጣሚዎች መካከልም ሃይማኖቱን ቀለል ለማድረግ፣ ህዝባቸውን አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ላለመክተት፣ ክባድ ጫና ላለመፍጠር እና መፈፀም የማይችሉትን ላለማሸከም ጥረት ማድረጋቸው ነው። ነብዩ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን እንዲህ ብለዋል፦ "አግራሩ እንጅ አታከባብዱ፤ አበስሩ እንጅ አታባሩ።" ቡኻሪይና ሙስሊም ዘግበውታል።

የተከበሩት መልዕክተኛ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን ነፍሳቸው በእዝነት የተሞላች ነበረች፤ ለሴቶች እና ለህፃናትም ከሰዎች ሁሉ ይበልጥ እጅግ አዛኝ ነበሩ። ከባልደረቦቻቸው መካከል አንዱ የሆኑት አነስ ቢን ማሊክ አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸው እንዲህ ብለዋል፦ "ከአላህ መልእክተኛ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን የበለጠ ለልጆች እጅግ በጣም አዛኝ የሆነ ማንንም አይቼ አላውቅም።" ሙስሊም ዘግበውታል።

የነብዩ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን እዝነት በሰዎች ላይ ብቻ የተገደበ ሳይሆን እስከ እንስሳትም ጭምር ዘልቆ የሄደ ነበር፤ ለእንስሳቱ መልካሙን እንዲደረግላቸውም ጥሪ አድርገዋል፤ እንስሳን ከማስቸገርም ከልክለዋል። ለባልደረቦቻቸውም አንዲት ዝሙተኛ ሴት ውሻ ውኃ በመጠጣቷ ምክንያት አላህ ይቅር ብሏት ጀነት መግባቷን እንዲሁም ሌላኛይቱ ሴት ደግሞ ድመቷን አስራ እስክትሞት ድረስ ስላልመገበቻት በዚህ ምክንያት ጀሀነም መግባቷን በመንገር በምሳሌ አስተምረዋል።

መልዕክታቸው ለሰው ልጆች ሁሉ ነው፡-

ቀደምት ነብያትና መልዕክተኞች - የአላህ ሰላም በሁሉም ላይ ይስፈን - ለወገኖቻቸው ብቻ ተለይተው ነበር የሚላኩት፤ ነቢዩ ሙሐመድ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን ግን መልእክታቸው ለማንኛውም ጊዜና ቦታ ለመላው የሰው ልጅ ነው።

ከፍ ያለው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"(ሙሐመድ ሆይ!)፡- አንተንም ለሰዎች ሁሉ በመላ አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን ቢሆን እንጂ አላክንህም።"

[ሰባእ፡ 28]

ከፍ ያለው አላህ እንዲህም ብሏል፦

"(ሙሐመድ ሆይ!)፡- «እናንተ ሰዎች ሆይ! እኔ ወደናንተ ወደ ሁላችሁም የአላህ መልክተኛ ነኝ» በላቸው።"

[አል-አዕራፍ፡ 158]

ነቢዩም የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን እንዲህ ብለዋል፦

"ነብያቶች የሚላኩት ወደ ህዝቦቻቸው ብቻ ነበር፣ እኔ ግን ወደ ሰዎች ሁሉ ነው የተላክሁት።"

ቡኻሪይ ዘግበውታል።

ነብዩ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን ከተላኩ በኋላ በዚህ ዘመን ያለም ይሁን እስከ ሰዓቲቱ ፍፃሜ ድረስ የሚመጣ ማንኛውም ሰው እርሳቸውን የመከተል፣ ይዘውት የመጡትንም መልዕክት አምኖ የመቀበል እና ወደ ሃይማኖታቸውም የመግባት ግዴታ አለበት። አላህ በእርሳቸው አማካኝነት ሰማያዊ መልእክቶችን ደምድሟል። እርሳቸውን መታዘዝ ግዴታ አድርጓል፤ እርሳቸውን የታዘዘ በቅርቢቱ ዓለም ደስተኛ ይሆናል፤ በቀጣዩ ዓለምም ጀነት ይገባል። እርሳቸውን ያልታዘዘ (ያመፀ) በቅርቢቱ ዓለም እድለ ቢስ ይሆናል፤ በቀጣዩ ዓለምም የጀሀነምን እሳት ይገባል። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦

"መሪየን የተከተለ አይሳሳትም አይቸገርምም። (123)

ከግሣጼዬም የዞረ ሰው ለእርሱ ጠባብ ኑሮ አለው። በትንሣኤም ቀን ዕውር ሆኖ እንቀሰቅሰዋለን።"

[ጧሀ፡ 123-124]

መልእክተኛው የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን በቤታቸው እና ከቤተሰባቸው ጋ የነበራቸው መስተጋብር፡-

የማንኛውም ሰው ቤት መልካም ምግባሩን፣ ሙሉ የሆነ ስርዓቱን፣ ያማረ መስተጋብሩን የሚያሳይበት ቦታ ነው። አንድ ሰው ከሚስቱ፣ ከልጆቹ ወይም ከአገልጋዩ ጋር ሲሆን የማይደብቀው ትክክለኛ ማንነቱ ይወጣልና።

ሙስሊሙ ማህበረሰብ መልዕክተኛው፣ መሪው እና መምህሩ የሆኑት ነቢዩ - የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን - በቤታቸው ውስጥ የነበራቸውን ሁኔታ ቢያስተውል የተከበረ ሰው በቤቱ ውስጥ ከቤተሰቡ እና ልጆቹ ጋር ምን መሆን እንዳለበት የሚያሳዩ በጣም ምርጥ ተምሳሌቶችን ባገኘ ነበር።

የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ባለቤት ለሆኑት ዓኢሻ (መልካም ሥራዋን አላህ ይውደድላት) እንዲህ ተብለው ተጠየቁ፡- ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በቤት ውስጥ ምን ያደርጉ ነበር? አርሷም ስትመልስ፦

"በቤተሰባቸው ሙያ ውስጥ የሚያግዙ ነበሩ (ቤተሰባቸውን ያግዙ ነበር)፤ የሰላት ጊዜ ሲደርስም ወደ ሰላት ይሄዱ ነበር።"

ሙስሊም ዘግበውታል።

ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ለቤተሰቦቻቸውና ለሚስቶቻቸው ከሰዎች ሁሉ በላጭ ነበሩ። በመልካም ቤተሰባዊ መስተጋብር ውስጥ ድንቅ ምስሎችን ይፈጥራሉ፤ በለስላሳ ጎን፤ የሚስትን ስሜታዊ እና ስነ-ልቦናዊ ፍላጎት በማወቅ እና አጋጣሚዎችንም በመጠቀም ልቧ ውስጥ ደስታን ይፈጥሩላታል። እናታችን ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላት) እንዲህ ብለዋል፡-

“የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) አንድ ቀን ቤቴ በር ላይ ሆነው ሐበሾች መስጂድ ውስጥ ሲጫወቱ ተመለከትኳቸው። የአላህ መልእክተኛም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በመጎናጸፊያቸው ጋርደውኝ የሓበሾቹን ጫዎታ እመለከት ነበር።"

ቡኻሪይ እና ሙስሊም ዘግበውታል።

የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ሴት ልጆቻቸውን ይወዱና ያከብሩ ነበር፤ ልጃቸው ፋጢማ ወደ እርሳቸው በመጣች ጊዜ ቆመው ይቀበሏት፣ ይስሟትና ተቀምጠውበት በነበረው ቦታ ያስቀምጧትም ነበር። ልጆቻቸውንም ይጠይቁ (ይጎበኙ) እና ያሉበትንም ሁኔታ ያጣሩ ነበር።

ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ለህዝባቸው ካስተላለፉት አደራዎች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡-

"ስለ ሴቶች መልካሙን በማድረግ ላይ አደራ ተባባሉ።"

ቡኻሪይ እና ሙስሊም ዘግበውታል።

ከነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) መልካም ስነ ምግባሮች መካከል፦

ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በሥነ ምግባር ከሰዎች ሁሉ በላጭ፤ ስርዓታቸውም እጅግ ያማረ ነበሩ። አላህም እንዲህ ሲል በተከበረ ቃሉ ገልጿቸዋል፦

"አንተም በታላቅ ጠባይ ላይ ነህ።"

[አል-ቀለም፡ አንቀጽ 4]

ከእርሳቸው ውጪ ሌላ ማንም ሊደርስበት በማይችለው ሙሉነታቸው ይጠቃቀሙበት ነበር። ልክ እንደዚሁ ከጉድለት ሁሉ ነፃ ተደርገዋል። በመልካም መገለጫዎችም ሁሉ ምሉእነትን ተጎናፅፈዋል፤ ባህሪያቸው የተከበረው ቁርኣን ነበር፤ በእርሱ ይታነፁ ሌሎችንም በእርሱ ያንፁ ነበር። ከነቢዩ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ባህሪያት መካከል፦

- ከሰዎች ሁሉ እጅግ በጣም ቻይ፣ ፍትሃዊ፣ ይቅር ባይ፣ ለጋስ እና ቸር ነበሩ።

- ከሰዎች ሁሉ ይበልጥ ሐያእ (አፍረት) የሚሰማቸው ነበሩ።

- ማንም ጥሪ ካደረገላቸው ቀና ምላሽ የሚሰጡ ትሁት፤ ትንሽም ቢሆን ስጦታንም የሚቀበሉ፤ ውለታንም በበጎ የሚመልሱ ነበሩ።

- የታመመን ይጠይቁ፣ የሞተን ይቀብሩ፣ ከድሆች ጋ አብረው ይቀማመጡ፣ ችግረኞችንም የሚያበሉ፣ ብልጫና መልካም ባህሪ ያላቸውንም የሚያከብሩ እንዲሁም የተከበሩ ሰዎችንም ይወዳጁ ነበር።

- አንድ ሰው ትብብራቸውን ፈልጎ ቢመጣ ለጉዳዩ አብረውት ይቆሙ ነበር፤ ዐመለ መጥፎም ሆነ ልበ ደረቅ እንዲሁም መጥፎን በመጥፎ የሚመልሱ አልነበሩም፤ ይልቁኑ ይቅርታ እና ምህረትን ያደርጉ ነበር። የአላህ ክልከላዎች ሲጣሱ ግን ለራሳቸው ሳይሆን ለአላህ ብለው እጅግ ይቆጡ ነበር።

- ከባህሪያቸውም መካከል ያገኙትን ሰው በሰላምታ መጀመር ተጠቃሽ ነው፤ ከባልደረቦቻቸው መካከል ማንኛውንም ካገኙት ቀደመው ይጨብጡት ነበር።

- ከእርሳቸው ጋ አብሮ ለተቀመጠ ከፊታቸው፣ ከመስሚያቸው፣ ከንግግራቸው፣ ከልስላሴያቸውና ከርህራሄያቸው እንዲሁም ከምክራቸው ድርሻውን ይለግሱት ነበር።

- ከሰዎች ሁሉ በጣም (ጥሩ) ደግ፣ ከሰዎች ሁሉ ምርጥ እና ከሰዎች ሁሉ ለሰዎች እጅጉን ጠቃሚ ነበሩ።

- ይቀልዳሉ፤ ይሁን እንጅ ከእውነት በቀር ምንም አይናገሩም፤ በጣም ፈገግታ ያበዛሉ፤ ይስቃሉ ግን ያለማሽካካት፤ ከሚስቶቻቸውም ጋር ሁሉ (ሩጫ) ይወዳደሩ፤ ሚስቶቻቸውንም ይንከባከቡ ነበር።

- የቀረበላቸውንም ምግብ ይመገቡ ነበር፤ የትኛውንም ምግብ ፈፅሞ አነውረው አያውቁም። ተምርም ይሁን፣ ሥጋም ይሁን፣ የስንዴ ወይም የገብስ ዳቦም ይሁን፣ ጣፋጭ ነገርም ሆነ ማር ካገኙ ይመገቡ ነበር። ዳቦ እንኳ የሌለው ወተትም ቢያገኙ ይበቃቸው ነበር፤ ሐብሐብ ወይም የተምር እሸት ካገኙም ይመገቡ ነበር።

- የተፈቀደ እስከሆነ ድረስ ያገኙትን ልብስም ይለብሱ ነበር፤ አንዳንድ ጊዜ ኩታ አንዳንድ ጊዜ ከሱፍ የተሠራ ካባ ያደርጉ ነበር።

- ለመጓጓዣም ያገኙትን አማራጭ አንዳንድ ጊዜ ፈረስ፣ አንዳንዴ ግመል፣ አንዳንዴ በቅሎ፣ አንዳንድ ጊዜ አህያ ይጠቀማሉ፤ አለበለዚያም በእግራቸው ይጓዙ ነበር።

- ለአላህ እየሠሩ ወይም አስፈላጊ የሆኑ የግል ወይም የቤተሰብ ጉዳይ እየፈፀሙ ካልሆነ በቀር ጊዜያቸውን በከንቱ አያሳልፉም ነበር።

እነዚህን መሰል የላቁ ባህሪያት እና ውብ የሆነ መስተጋብርም ነበራቸው፤ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና።

መደምደሚያ

እስልምና ታላቅ ሃይማኖት ነው፤ ለአንድ ሙስሊም ግለሰብ - አስተምህርቶቱን ለሚከተል - በዚህ ዓለም ምቾት፣ ጥሩ ሕይወት እና የተስተካከለ ሁኔታ እንዲኖረው፤ በቀጣዩ ዓለምም ዘውታሪ የሆነ ፀጋ እና ዘለአማዊ ደስታ እንዲጎናፀፍ ያደርገዋል። ልክ እንደዚሁ አስተምህሮውን አጥብቆ ለሚይዝ ሙስሊም ማህበረሰብም ከፍታ፣ ስልጣኔ፣ ብልህነት፣ እድገት፣ ማህበራዊ ትስስር፣ ሰላም እና ደህንነትን ያረጋግጥላቸዋል።

እስልምናን የተቀበልክ ሆይ! ለዚህ ታላቅ ፀጋ እንኳን ደስ አለህ። ስለዚህም ዐቂዳውን (እምነቱን)፣ ሸሪዓውን (ህግጋቱን)፣ ትምህርቱን፣ ፍርዱን፣ ስነ ምግባሩን እና ስርዓቱን ተማር፤ በራስህም ላይ ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት አድርግ፤ በሁሉም የህይወትህ ዘርፍ ላይ በቻልከው ልክ አጥብቀህ ተከተለው። የዚህኔ እስልምና የሚያሳድረው መልካም ተጽዕኖ በጉልህ ይታያል፤ እንዴት መልካም ሰው መሆን እንደሚችል ይማራል፤ በራሱ ደስተኛ ይሆናል፤ በዙሪያው ያሉትን ወላጆቹን፣ ሚስቱን፣ ልጆቹን፣ ዘመዶቹን፣ ጎረቤቶቹን እና ጓደኞቹን እንዲሁም ከዚህ አላህ ወደ ራሱ ሃይማኖት በማስገባት ካከበረው ሙስሊም ጋ የሚኗኗሩ ሰዎችንም ሁሉ ደስተኛ ያደርጋል።

ይህ ቡክሌት የሃይማኖትህን ህግጋት ለመማር የመንገድህ መጀመሪያ ነው። ከዚያ በኋላ የበለጠ ጠቃሚ ዕውቀትንና መልካም ሥራዎችን ለመጨመር፣ ነፍስህንም ለማንጻት እና ልብህንም ለማስተካከል ጥረት ማድረግ ይገባሃል። ኢስላማዊ ዕውቀትህ በጨመረ እና ባወቅከው በሠራህ ቁጥር ቸር ኃያልና ታላቅ ወደሆነው ጌታህ ቅርብ ትሆናለህ። በመማር፣ በማንበብ እና አንቀጾቹን በማስተንተን ወደ ተከበረው ቁርኣን ተመለስ። የአላህ መልእክተኛ ሙሐመድን የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን ታሪክ እንዲሁም ሱንናቸውን አንብብ። በህይወትህ ውስጥ አርዓያ ልታደርጋቸው የምትችለው እርሳቸውን ነው፤ አላህ ያመጡትን ሁሉ እንድትቀበል ያዘዘህ እርሳቸውን ብቻ ነው። ከእርሳቸው ውጪ ያሉ ሌሎች ሰዎች ግን ደረጃቸው ምንም ይሁን ምን ንግግራቸው ከቁርኣንና ከሱና ጋ ከተስማማ ተቀባይነት ያገኛል የማይስማማ ከሆነ ደግሞ ውድቅ ይሆናል። በዲን ጉዳይ ከመጨቃጨቅ ተጠንቀቅ! ከሙስሊም ወንድሞችህ ጋ ጠብ፣ አለመግባባትንና ጭቅጭቅ ውስጥ ከመግባት ራቅ።

አላህ ስራችንን ወዶልን እስክንገናኘው ድረስ እኛንም እናንተንም በዚህ ዲን ላይ ስኬትና ፅናት እንዲሰጠን እንለምነዋለን። ምስጋና ሁሉ ለዓለማት ጌታ አላህ የተገባ ነው። ሰላትና ሰላም በነብያችን ሙሐመድ፣ በቤተሰቦቻቸው፣ በባልደረቦቻቸው እና እስከ ፍርዱ ቀን ድረስ በተከተላቸው ላይ ሁሉ ይስፈን።