دين الحق
እውነተኛው ሃይማኖት
እውነተኛው ሃይማኖት
በተከበሩ ሸይኽ
ዐብዱረሕማን ቢን ሐማድ አል ዑመር
በአላህ ስም እጅግ በጣም ርህሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው
መቅደም እና መግቢያ
ምስጋና ሁሉ የዓለማት ጌታ ለሆነው አላህ ነው፤ የአላህ ሶለትና ሰላም በመላው የአላህ መልክተኞች ላይ ይስፈን፤ በመቀጠልም፦
ይህችን፥ አስተዋይ ልቦና ላለው ወንድም ይሁን ሴት ሁሉ የማስቀድማት የስኬት ጥሪ ነች። የላቀው (የበላይ) እና ሁሉን ቻይ ጌታየም ከመንገዱ የጠመመን እድለኛ ሊያደርግበት፤ እኔንም ሆነ በማሰራጨቱ ላይ እገዛ ያደረገንም ሁሉ ታላቅ ምንዳን ሊመነዳን ዘንድ ተስፋ በማድረግ በአላህ እየታገዝኩ እንዲህ እላለሁ፦
አስተዋይ ልቦና ያለህ ሰው ሆይ! የፈጠረህን ጌታህን እስካላወቅክ፤ አምነህም በብቸኝነት እስካላመለክከው፤ እንዲሁም ጌታህ ወዳንተም ሆነ ወደ ሰው ልጆችም ሁሉ የላከውን ነብይ አውቀህና አምነህበት ተከታዩ እስካልሆንክ፤ ጌታህ ያዘዘበትንም ትክክለኛ ሃይማኖት አምነህ እስካልሰራህበት ድረስ በዚህ ሕይወት ውስጥም ይሁን ከሞት በኋላ በሚቀጥለው ሕይወት ስኬት ሆነ እድለኝነት እንደሌለህ እወቅ።
ይህ እጅህ ላይ የሚገኘው "ትክክለኛ ሃይማኖት" የሚል ርእስ ያለው ጽሁፍ አውቀህ ልትተገብራቸው ግድ የሚሉ የሆኑ ታላላቅ ጉዳዮችን ማብራሪያ በውስጡ ይዟል። በማስታወሻውም ላይ አንዳንድ ቃላቶችንና ሃሳቦችን ለመረዳት አስፈላጊ የሆኑ ጭማሪ ማብራሪያዎችንም ጠቅሻለሁ። ለዚህ ሁሉ ታድያ የላቀው አላህን ቃል ቁርኣንንና ነብያዊ ሐዲሥን መሰረት በማድረግ ነው። ይህም አላህ ከዛ ውጭ ሌላን ለማይቀበልበት ትክክለኛ ሃይማኖት ብቸኛ ምንጭ በመሆናቸው ነው።
ብዙዎችን ያጠመመውን ጭፍን ተከታይነትንም ርቅያለሁ። ይልቁኑ በትክክለኛው ሃይማኖት (እውነት) ላይ ነን ብለው የሚሞግቱ የተሳሳቱ ቡድኖችን (ጭፍራዎችን) ሁኔታዋን የማያውቁ አላዋቂዎች ራሳቸውን እንዲያርቁ ስል ጠቅሻለሁ። ለዚህም አላህ በቂዬ ነው። ምንኛ ያማረ መመኪያ ነው!
ይህንን የፃፈው: የላቀውን አላህን ምህረት ከጃዩ፦
ዐብዱረሕማን ብን ሐማድ ኣል ዑመር
የሃይማኖታዊ ትምህርት መምህር
የመጀመሪያው ክፍል፦ ታላቁን ፈጣሪ አላህን ማወቅ [1]
[1] አላህ፦ ለአጽናፈ ዓለም፣ ለሰዎች እና ለሁሉም ነገር አምላክ የሆነው ጌታ ብቻ ተለይቶ ያለ መጠሪያ ስም ነው። ይህ ስም ፍፁም ማንነቱን የጠራበት መጠሪያ ስሙ ነው። ትርጉሙም፦ "እውነተኛው አምላክ" ማለት ነው።
አስተዋይ ልቦና ያለህ ሰው ሆይ! ያ አንተን ያላንዳች ነገር (ካልነበርክበት ያስገኘህ) የፈጠረህና በፀጋውም እየተንከባከበህ ያለው ጌታህ የዓለማቱ ጌታ አላህ መሆኑን እወቅ። በርሱ ያመኑ አስተዋዮችም ቢሆኑ የላቀው[2] አላህን በዓይናቸው አይተውት አይደለም ያመኑበት፤ ይልቅ ህልውናውን፣ ፍጥረታትን ሁሉ የሚያስተናብር ፈጣሪ ለመሆኑ አስረጂ ምልክቶችን አይተው አወቁትና አመኑ። ከእነዚህም ማስረጃዎች መካከል፦
[2] የላቀው ስንል:- አላህ የላቀ እና ውዳሴም የሚገባው መሆኑን ከመጠቆም እንዲሁም ከፍ ያለና ከእንከን ሁሉ የጠራ መሆኑን ከመግለፅም አንፃር ነው።
የመጀመሪያው ማስረጃ፦ ፍጥረተ ዓለም፣ የሰው ልጅ እና ህይወት፥ እነኝህ ነገራቶች ጅማሮና ፍፃሜ ያላቸው ክስተቶች እና ከሌላ ፈላጊዎች ናቸው። ከሌላ አካል ፈላጊ የሆነ ሁሉ ደግሞ የግድ ፍጡር መሆን አለበት። ፍጡር ደግሞ የግድ ፈጣሪ ያስፈልገዋል። ታድያ ይህ ታላቁ ፈጣሪ አላህ ነው። የላቀው አላህ ነው ስለፍፁም ማንነቱ ህልውናውን ሁሉ የሚያስተናብር ፈጣሪ መሆኑን የነገረን። ይህ የፈጣሪነቱ መልዕክት ከላቀው አላህ ለመልዕክተኞቹ ባወረዳቸው መጽሐፍት በኩል ነው ወደኛ የደረሰው። የአላህ መልዕክተኞችም ቃሉን ለሰው ልጆች አድርሰዋል፤ በእርሱ ወደ ማመን እና እርሱን በብቸኝነት ወደ ማምለክ ጥሪ አድርገዋል፤ የላቀው አላህ በታላቁ ቁርኣን እንዲህ ብሏል፦
{ጌታችሁ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ አላህ ነው። ከዚያም (ለክብሩ በሚስማማ መልኩ) በዐርሹ ላይ ከፍ አለ። (አላህ) ሌሊትን በቀን ፈጥኖ የሚፈልገው ሲኾን ይሸፍናል። ፀሐይንና ጨረቃንም ከዋክብትንም በትእዛዙ የተገሩ ሲኾኑ (ፈጠራቸው)። ንቁ! መፍጠርና ማዘዝ የእርሱ ብቻ ነው። የዓለማት ጌታ አላህ (ክብሩ) ላቀ።}
[አል-አዕራፍ፥54]
የዚህ ታላቅ አንቀፅ ጥቅል መልእክት፦
የላቀው አላህ ለመላው የሰው ልጆች እነርሱን የፈጠራቸው፣ ሰማያትንና ምድርንም በስድስት ቀናት[3] የፈጠረ ጌታቸው መሆኑን እንዲሁም እርሱ ከዓርሹም በላይ ከፍ ያለ[4] መሆኑንም እያሳወቀን ነው። [3] ይህን በአፈጣጠር ላይ ያለ ሂደት ያደረገው ጥራት የተገባውና የበላይ የሆነው አላህ የፈለገው ጥበብ ስላለ እንጂ አለበለዚያ እሱ ከዓይን ብልጭታ በሚበልጥ ፍጥነት ሁሉንም ፍጥረታት በአንዳፍታ መፍጠር ይችላል። ምክንያቱም አንዳችን ነገር በፈለገ ጊዜ ሁን ሲለው ወድያውም እንደሚሆን ነግሮናልና። "ኢስተዋ ዓላ ሸይእ" ሲባል - የቁርኣን ቋንቋ በሆነው - የዐረቦች ቋንቋ ትርጉሙ፦ የበላይ ሆነ ከፍ አለ ማለት ነው። በመሆኑም አላህ ከዓርሹ ላይ ያለው "ኢስቲዋእ" ስንል ይህም ከእርሱ ውጭ ማንም በማያውቀውና ለልቅናው በሚገባው መልኩ በላዩ ላይ ከፍ ማለቱን ነው። "ኢስተዋ" የሚለው ቃል አንዳንድ አላህ ራሱን በገለፀበት እውነታ ብናፀድቅ አላህን ከፍጡራኖቹ ጋ ማመሳሰል ይሆናል በሚል ሰበብ አላህ ራሱን ከገለፀበት፣ መልዕክተኞቹም እርሱን ከገለፁበት እውነተኛ ባህሪ የሚያራቁቱ (የሚያሳጡ) ጠማማዎች እንደሚሉት "ኢስተውላእ" ወይንም ንግስናውን ተቆጣጠረ ማለት አይደለም። ይህ ከንቱ የሆነ ሙግት ነው። ምክንያቱም ማመሳሰል የሚባለው አንድን ነገር አመሳስሎ "ልክ እንደ" በሚያስብል መልኩ ከፍጡራኑ ጋ በማመሳሰል ሲገለፅ ነው። ለአላህ በሚገባው መልኩ ምንም ሳያመሳስሉ፣ ዝርዝር ሁኔታ ውስጥ ሳይገቡ፣ ውድቅም ሳያደርጉ፣ ምንም ሳያዞሩ ማፅደቅ ደጋግ ቀደምቶች የሄዱበት የመልዕክተኞች ፈለግ ነው። ብዙሃኑ ሰው ቢተወው እንኳ ሙእሚኖች ሊከተሉትና አጥብቀውም ሊይዙት ግዴታ የሆነ እውነት ነው።
ዓርሽ ከሰማያት በላይ ያለ ሲሆን ከፍጥረታት ሁሉ የላቀ (ግዙፍ) እና እጅግ ሰፊ የሆነ ፍጡር ነው። ታድያ አላህ ከዚሁ ከዓርሽ በላይ ከመሆኑም ጋ ከእውቀቱ፣ ከመስማትና መመልከቱ አኳያ ግን ምንም በማይደበቅበት መልኩ ከሁሉም ፍጥረታት ጋ ነው። አላህ ሌቱ ቀኑን በጨለማ ማከናነቡንና በፍጥነት መከታተሉንም አሳወቀን፤ ፀሀይ፣ ጨረቃንና ከዋክብትንም የፈጠረና እያንዳንዷ በትእዛዙ የተገራች ሆና በምህዋሯ የምትጓዝ መሆኗንም አሳወቀን። መፍጠርና ማዘዝም የእርሱው ብቻ መሆኑን፤ ዘውታሪ የሆነን በርካታ መልካም ነገርን የሚሰጠው በማንነትም በባህሪም የተሟላው ታላቁ እርሱው መሆኑን፣ ፍጡራንን ሁሉ የፈጠረው በፀጋ ተንከባካቢው የአለማቱ ጌታ እርሱው መሆኑንም አሳውቆናል።
ከፍ ያለው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ሌሊትና ቀንም ፀሐይና ጨረቃም ከምልክቶቹ ናቸው። ለፀሐይና ለጨረቃ አትስገዱ። ለእዚያም ለፈጠራቸው አላህ ስገዱ። እርሱን ብቻ የምትግገዙ እንደ ኾናችሁ (ለሌላ አትስገዱ)።}
[ፉሲለት፥ 37]
የዚህ ታላቅ አንቀፅ ጥቅል መልእክት፦
የላቀው አላህ ወደ እርሱ ከሚያመለክቱ (የሚጠቁሙ) ምልክቶቹ መካከል ሲነግረን፦ የሌሊትና ቀን የፀሐይና ጨረቃ መፈራረቅ ይገኝበታል። ለፀሀይም ሆነ ለጨረቃ መስገድ ክልክል አድርጎታል ምክንያቱም እንደሌላው ፍጡራን ብቻ ናቸው፤ ፍጡር ደግሞ ሊመለክ አይገባውምና ነው። መስገድ፦ አንድ የአምልኮ ዓይነት ነው። ታድያ ለዚህም ነው አላህ በዚህም አንቀፅ -በሌላውም አንቀፅ እንደሚያደርገው- የሰውልጆችን ሁሉ ለእርሱ ብቻ እንዲሰግዱ አዟቸዋል። ምክንያቱም ብቸኛ ፈጣሪ፣ አስተናባሪና ለአምልኮም ተገቢ የሆነው እርሱ ብቻ በመሆኑ ነው።
ሁለተኛው ማስረጃ፦
እርሱ ወንድንና ሴትን ፈጥሯል፤ የሴት እና የወንድ መኖር ደግሞ አምላክ ለመኖሩ ማስረጃ መሆን የሚችል ነው።
ሶስተኛው ማስረጃ፦
የልሳን (ቋንቋ) እና የመልክ መለያየት፦ ድምፃቸው ተመሳሳይ የሆነ ወይም መልካቸው ተመሳሳይ የሆኑ ሁሉት ሰዎች ማግኘት አይቻልም፤ የተወሰነ ልዩነት መኖሩ አይቀርም።
አራተኛው ማስረጃ፦
የዕድል ልዩነት፦ ሁሉም (ሰዎች) የአዕምሮ፣ የሀሳብና የእውቀት ባለቤት ከመሆናቸውም ጋ አንዱ ሀብታም ሌላኛው ድሃ፤ አንዱ መሪ ሌላኛው ተመሪ ይሆናሉ። (ሁሉም) ማግኘት ያልቻሉትን ሀብት፣ ክብር እና ጥሩ ሚስት ለማግኘት ከፍተኛ ጥረት ያደርጋል። ነገር ግን
ማንም ቢሆን አላህ (ሱብሓነሁ [5] የወሰነለትን ካልሆነ በቀር ሊያገኝ አይቻለውም። ይህም አላህ ከሻው ከትልቅ ጥበብ አኳያ የሚሆን ነው። ይህም ጥበብ ሁሉም የሚበጀውን እንዲያገኝ የሰው ልጆችን አንዱ ሌላውን የመፈተን፤ ከፊሉም በሌላኛው ከፊል የማገልገል ጥበብ ነው።
[5] ሱብሓነሁ ማለት፦አላህ ከእንከንም ሆነ ነውር ሙሉ በሙሉ የጠራ ፍፁም ነው ማለት ነው።
አላህ በዚህ ዓለም ዕድል ያልወሰነለትንም በአላህ አምኖ ከሞተ በአኼራው በላጭ የሆነ የፀጋ ድርሻን እንደሚያቆይለት አሳውቆናል። በዚህች ዓለምም ቢሆን ግን ድሀው አብዛኛውን ጊዜ በርካታ ሀብታሞች ዘንድ የማይገኝን የነፍስና የጤና ልዩ መጠቃቀም ያለው ከመሆኑም ጋር ነው። ይህም ከአላህ ጥበብና ፍትህ አኳያ ነው።
አምስተኛ ማስረጃ፦
እንቅልፍ እና አላህ (ሱብሓነሁ ወተዓላ) የተኛን ሰው የሚያሳየው የማስጠንቀቂያ ወይም የብስራት የሩቅ ምስጢር ትክክለኛ ህልምም ከማሰረጃዎች ነው።
ስድስተኛ ማስረጃ፦
ተጨባጭ እውነታዋን አላህ እንጂ ሌላ ማንም የማያውቃት የሆነችው ሩሕ ነው።
ሰባተኛ ማስረጃ፦
የሰው ልጅ፡ እና በሰውነቱ ውስጥ ያለው የስሜት ህዋሳት፣ የነርቭ ስርዓት፣ አንጎል፣ የምግብ መፍጫ ሥርዓት እና የመሳሰሉት ሁሉ ማስረጃ ናቸው።
ስምንተኛ ማስረጃ፦
አላህ በሞተ ምድር ላይ ዝናብን አውርዶ የተለያዩ ቅርጾች፣ ቀለሞች፣ ጥቅሞች እና ጣዕም ያላቸው ዕፅዋት እና ዛፎች ይበቅላሉ፤ ይህም የላቀው አላህ በቁርኣን ውስጥ ከጠቀሳቸው የአላህን መኖርና እና አላህ የሁሉም አስተናባሪ መሆኑን ከሚያመላክቱ በመቶዎች ከሚቆጠሩ ቋሚ ማስረጃዎች ጥቂቶቹ ናቸው።
ዘጠነኛ ማስረጃ፦
አላህ የሰው ልጆችን የፈጠረበት ተፈጥሯዊ ማንነት እንዲሁ ማስረጃ ነው። ተፈጥሮ የፈጠራትና የሚያስተናብራት የሆነ አምላክ እንዳላት ታምናለች። ይህንንም ያወገዘ ራሱን እያታለለና እያንገላታ ነው። ለምሳሌ ኮሚኒስት[6] (የሆነ ሰው) በዚህች ዓለም ሲኖር የእንግልት ህይወትን ነው የሚኖረው፤ ከሞት በኋላም መመለሻቸው ወደ እሳት ነው። ይህም ያ ካልነበረበት የፈጠረውንና በፀጋው የተንከባከውን ጌታውን በማስተባበሉ የተዘጋጀለት ምንዳው ነው። ምናልባት ወደ አላህ ተመልሶ በእርሱ፣ በሃይማኖቱና በመልዕክተኞቹ ካላመነ በስተቀር። [6] ኮሚኒስቶች አምላክ የለም እንደሚሉት ናቸው። ዐስረኛ ማስረጃ፦ በረከት ማለት የአንዳንድ ፍጥረታት መብዛት መበራከት ማለት ነው፤ ለምሳሌ እንደ በግና ፍየል ያሉ (እንስሣት)፤ የበረከት ተቃራኒ ደግሞ ውድቀት ነው፤ እንደ ውሻና ድመት ያሉ (እንስሳት መብዛት)። *** የላቀው አላህ ካሉት ባህርያት መካከል እርሱ፦
ጅማሮ አልባ መጀመሪያ ነው፤ ዘለዓለማዊ ህያው ነው፤ አይሞትም አያልቅ (መጨረሻ የለውም)፤ ራሱን የቻለና ከሌሎች የተብቃቃ ነው፤ ከሌሎች የማያስፈልገው ነው፤ ተጋሪ የሌለው ብቸኛ ነው፤ የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{በል «እርሱ አላህ አንድ ነው።}
{«አላህ (የሁሉ) መጠጊያ ነው።}
{«አልወለደም፤ አልተወለደምም።}
{«ለእርሱም አንድም ብጤ የለውም።»}
[አል-ኢኽላስ ፥1-4]
የአንቀፆቹ ማብራሪያ፦
(የመካ) ከሀዲያን የአላህን መልክተኛን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ስለ አላህ ባህሪ በጠየቁ ጊዜ አላህ ይህንን ምዕራፍ በእርሳቸው ላይ አወረደላቸው፤ በውስጡም መልዕክተኛው እንዲህ እንዲሏቸው አዘዛቸው፦
አላህ ተጋሪ የሌለው ብቸኛ ነው፤ አላህ ሕያው፣ ዘልአለማዊ እና አስተናባሪም ነው፤ እርሱ ብቻ በፍጥረተ ዓለሙ፣ በሰዎች እና በሁሉም ነገሮች ላይ ፍጹም ሉዓላዊ ስልጣን አለው። በመሆኑም ሰዎች ጉዳያቸው እንዲፈፀምላቸው ወደ እርሱ ብቻ ነው መመለስ ያለባቸው።
አልወለደምም አልተወለደምም። ወንድም ሆነ ሴት ልጅ ፤ አባት ወይንም እናት ሊኖረውም የሚገባው አይደለም። ይልቁኑ እነዚህን ሁሉ በዚህ እና በሌሎች የቁርኣን ምዕራፎች ውስጥ እጅግ ጠንካራ በሆነ መልኩ ከራሱ ላይ ውድቅ \ ነጻ አድርጓል። ምክንያቱም የዘር ሰንሰለትና መወለድ የፍጡራን ባሕርያት መካከል በመሆናቸው ነው። እናም ኢየሱስ (ዒሳ) የአላህ ልጅ ነው ለሚለው የክርስትያኖች ንግግርም ሆነ "ዑዘይር" የአላህ ልጅ ነው ለሚለው የአይሁዶች ንግግር እንዲሁም "መላእክት የአላህ ልጆች" ናቸው ለሚለው የሌላኞቹ አስፀያፊ ንግግር ሁሉ አላህ ምላሽ ሰጥቷል።
የሰው ልጆች ሁሉ አባት የሆኑትን አደምን ከአፈር እንደፈጠራቸው እና የሰው ልጆች ሁሉ እናት የሆነችውን ሐዋእንም ከአደም የጎድን አጥንቱ ፈጥሮ በጎኑ አድርጎላቸው ለአደም እንዳሳያቸው ሁሉ ዒሳንም - የአላህ ሰላም በእርሱ ላይ ይስፈንና - ያለ አባት ከእናት ብቻ በሁሉን አድራጊነት ችሎታው እንደፈጠረው ነግሮናል። ከዚያም የአዳምን ዘር ከወንድ እና ከሴት ፈሳሽ ፈጠረ። መጀመሪያውኑ የትኛውንም ነገር ያላንዳች መነሻ ነው የፈጠረው ከዚያ በኋላ ግን ለፍጥረታቱ ሁሉ ከእርሱ በቀር ማንም ሊለውጠው የማይችል ስርአትና ፈለግ አደረገላቸው። ጥራት ይገባውና ሁሉን ቻይ የሆነው አላህ ከዚህ ስርዓት አንድን ነገር ለመለወጥ ከፈለገ እንዳሻው ይለውጠዋል።
አላህ ልክ ዒሳን - የአላህ ሰላም ይስፈንበትና - ያለ አባት ከእናት እንደፈጠረውና ገና በጨቅላነቱም ጊዜ እያለ እንዲናገር እንዳደረገው፤ እንዲሁም የሙሴንም - የአላህ ሰላም ይስፈንበትና - በትር የምትሮጥ እባብ እንዳደረገውና ባህሩንም በሷ በመታ ጊዜ ባህሩ ተከፍሎ ለእርሱም ለህዝቦቹም መሻገሪያ ድልድይ እንዳደረገለት፤ ለመልእክተኞች መደምደሚያ ሙሐመድ -የአላህ ሶለዋትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ጨረቃን እንደሰነጠቀላቸው፤ እሳቸው ሲያልፉ ዛፎች ሰላምታ እንዲያቀርቡላቸው አድርጓል፤ እንስሶችም ሰዎች ሊሰሙት በሚችሉት ድምፅ መልዕክተኝነታቸውን -እርሶ የአላህ መልዕክተኛ መሆኖን እመሰክራለሁ- በማለት ምስክርነታቸውን እንዲሰጡ አድርጎላቸዋል፤ በቡራቅ ላይ ሆነው ከመስጅደል ሓረም ወደ መስጅደል አቅሷ ከዚያም ጂብሪል አብሯቸው ሆነው ወደ ሰማይ በላይ አርገዋል። ከዚያም አላህም አናገራቸው ሰላትንም ደነገገላቸውና ወደ መሬት መስጅደል ሓረም እንዲመለሱ አድርጓቸዋል። በመንገዳቸውም የየሰማዩ ነዋሪዎችን ተመልክተዋል። ይህ ሁሉ የሆነው ፀሃይ ከመውጣቷ በፊት በአንዲት ለሊት ነው። ይህ የሳቸው ወደ አቅሷ መስጅድና ወደ ሰማይ ያደረጉት ጉዞ በቁርኣንና በሓዲሥ እንዲሁም በታሪክ መዛግብት የታወቀ ነው።
***
የላቀው አላህ ራሱን ከገለፀበትና መልዕክተኞቹም እርሱን ከገለፁበት መገለጫዎች መካከል፦
1_መስማት፣ ማየት፣ ዕውቀት፣ ችሎታ እና ፈቃድ ሁሉ የአላህ ባህሪይ ናቸው። ሁሉንም ይሰማልም ያያልም፤ የአላህን መስማት እና እይታን ግርዶሽ አይጋረጥበትም።
ማህፀኖች ውስጥ ያለውንና በልቦናዎች ውስጥ የተደበቀውንም ያውቃል፤ የሆነውንና የሚሆነውንም ሁሉ ያውቃል፤ አንድን ነገር በፈለገ ጊዜ “ሁን” በማለት እንዲሆን ማድረግ የሚችል ሁሉን ቻይ ነው። 2- በፈለገም ጊዜ የሚፈልገውን ይናገራል፤ ሙሳ ዓለይሂ ሰላምንም አነጋግሯቸዋል እንዲሁም የመልእክተኞች መደምደሚያ የሆኑትን ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አናግሯቸዋል። ቁርኣንም እያንዳንዱ ፊደልም ሆነ መልእክቱ በነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ላይ የወረደው የአላህ ቃል ነው። በመሆኑም የአላህ ንግግር ከባህሪያቱ መካከል አንዱ ባህሪ እንጂ ጠማማ የሆኑት ሙዕተዚላዎች እንደሚሉት ፍጡር አይደለም። [7] [7] ሙዕተዚላ የሚባሉት፥ ውብ የአላህ ስሞችን ያዛቡ፣ ትርጉማቸውንም የላቀው አላህ እና መልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከሚፈልጉት ውጭ በሆነ መልኩ የሚተረጉሙ ጠማማ አንጃዎች ናቸው። 3- ፊት እና ሁለት እጆችን ያሉት መሆኑ ከዓርሽ በላይ ከፍ ማለቱንና ወደ ቅርቢቱ ሰማይ የሚወርድ መሆኑ [8] እንዲሁም ወዶ የሚደሰት እና ቁጣ ከአላህ ባህሪዎች መካከል ናቸው። እርሱ በአማኞች ባህሪያት የሚደሰት እንዲሁም በከሀዲያኖቹ እና ቁጣውን በሚያስከትሉ ክስተቶች የሚቆጣ ነው። የአላህ ደስታ እና ቁጣ እንደ ሌሎቹ ባሕሪያቶቹ ከፍጡራኖች ባህሪ ጋር አይመሳሰሉምም ሌላ ትርጓሜ ባለመስጠት ዝርዝር ሁኔታቸውም አናስቀምጥም። [8]ይህንንም ያልነው ከተከታዩ የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሐዲሥ አንፃር ነው፦ "የላቀው ልዑሉ ጌታችን ሁሌም ከሌሊቱ አንድ ሦስተኛው ሲቀር በየሌሊቱ ወደ ዝቅተኛው (ቅርቢቱ) ሰማይ ይወርድና እንዲህም ይላል፦ 'እመልስለት ዘንድ የሚለምነኝ ማን ነው? እሰጠውስ ዘንድ የሚጠይቀኝ ማን ነው? ይቅርታዬን እለግሰውስ ዘንድ ይቅር እንድለው የሚማፀነኝ ማን ነው?'" [ቡኻሪይ (7494)፣ ሙስሊም (758)፣ ቲርሚዚይ (3498)]
በቁርኣን እና ሐዲሥ እንደተረጋገጠው አማኞች በእለተ ትንሳኤ መስክ እና ጀነትም ውስጥ ሁሉን ቻይ የሆነውን አላህን በዓይናቸው እንደሚያዩ ተላልፏል። የላቀው አላህ ባህሪያት በታላቁ ቁርኣንና በተከበረው የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አስተምህሮ በዝርዝር ተገልይፅዋል።
***
አላህ የሰው ልጆችን እና አጋንንቶችን የፈጠረበት ጉዳይ፦ አንተ አስተዋይ ልቦና ያለህ ሰው ሆይ! ያ የፈጠረህ ጌታህ አላህ መሆኑን እስካወቅክ ድረስ በከንቱ እንዳልፈጠረህም እወቅ፤ ይልቁንም የፈጠረህ እርሱን እንድታመልከው ነው። ማስረጃውም ተከታዩ የአላህ ቃል ነው፦
{ጋኔንንና ሰውንም ሊገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም።} (56)
{ከነርሱም ምንም ሲሳይ አልፈልግም። ሊመግቡኝም አልሻም።} (57)
{አላህ እርሱ ሲሳይን ሰጪ የብርቱ ኀይል ባለቤት ነው።} (58)
[አዝ-ዛሪያት፥56-58] የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት፦
የላቀው አላህ በመጀመሪያው አንቀፅ ላይ “ጂንንም [9] የፈጠረው ሰውንም የፈጠረው እሱን በብቸኝነት እንዲያመልኩት መሆኑን አሳወቀን። በሁለተኛውና በሶስተኛው አንቀፅ ደግሞ እርሱ ከባሪያዎቹ የማይፈልግ ሙሉ በሙሉ የተብቃቃ መሆኑን፣ ከእነሱም ሲሳይን ወይም ምግብን እንደማይፈልግ አሳወቀን። ምክንያቱም እርሱ ብርቱው ሲሳይ ለጋሽ ነውና። ከእርሱም ዘንድ ካልሆነ በቀር ለሰዎችም ሆነ ለሌላው ፍጥረት ሁሉ ሲሳይ የማይገኝበት ብቸኛ ነው። ዝናብን የሚያወርደውም ሆነ ከምድርም ሲሳይን የሚያወጣው እርሱው ነውና። [9] ጂን ማለት እንደ ሰው ልጆች የሆኑ አላህን ሊያመልኩ የተፈጠሩ ባለ አእምሮ ፍጡራን ናቸው። እንደሰው ልጆች በምድር ላይ የሚኖሩ ቢሆኑም የሰው ልጆች ግን አይመለከቷቸውም።
በምድር ላይ ያሉት ሌሎች ፍጥረታት ደግሞ የላቀው አላህ ለሰው ሲል እንደፈጠራቸው ነግሮናል። እርሱን በመታዘዝ ላይ እንዲታገዙባቸው፤ እነርሱን በመጠቀም የአላህን ድንጋጌ እውን እንዲያደርጉ፤ በፍጥረተ ዓለሙ ያሉ እያንዳንዱ ፍጥረታትም ሆኑ፣ እያንዳንዱ እንቅስቃሴና ፀጥታ የላቀው አላህ በቁርኣን ውስጥ ለገለፀው ጥበብ ሲል ፈጥሮታል። እያንዳንዷንም የአላህን መመሪያ የሚያውቁ ሊቃውንቶች ባላቸው የእውቀት ልዩነት ልክ ይረዱታል። በመካከላቸው ያለው የዘመናት፣ የኑሮ ዘይቤ፣ ክስተቶች እና መከራዎች ሁሉ እንኳ የሚከናወነው በአላህ ፈቃድ አስተዋይ ባርያዎቹን ሊፈትንበት ነው። የአላህን ቀደር ወዶ የተቀበለና ለእርሱም እጅ እግሩን ሰጥቶ አላህን የሚያስደስት ነገር በመፈጸም ላይ ትግል ያደረገ የአላህን ውዴታ ያገኛል፤ በዚህችም ምድር ሆነ ከሞት በኋላ ባለው ዓለም ደስታን ይጎናፀፋል፤ የአላህን ቀደር ወዶ ያልተቀበለ፣ ለአላህ እጅ እግሩን ያልሰጠና ተገዥ ያልሆነው ግን ከአላህ ዘንድ የሆነ ቁጣ፣ በዱኒያም በኣኼራ ህይወቱም እድለቢስ ይሆናል። አላህን ውዴታውን እንዲለግሰንና ከቁጣውም እንዲጠብቀንም እንማፀነዋለን።
***
ከሞት በኋላ መቀስቀስ፣ በስራ መተሳሰብ፣ የስራ ምንዳ፣ የጀነትና የጀሀነም ጉዳይ
አንተ አስተዋይ የሆንክ ሰው ሆይ! አላህ እርሱን እንድታመልከው እንደፈጠረህ እስካወቅክ ድረስ በመልዕክተኞቹ ባወረዳቸው መጽሐፍት ሁሉ ውስጥ እርሱ ከሞት በኋላ ሕይወት ዘርቶ እንደሚያነሣህ፣ ከሞት በኋላ በዓለመ_ ምንዳ በሠራኸው ሥራ እንደሚመነዳህ ለመልክተኞቹ እንደገለጠ እወቅ። ይህም የሆነበት ምክንያት የሰው ልጅ በሞት አማካኝነት ከሥራ እና ጠፊ ከሆነው ዓለም - ማለትም ይህ ያለንበት ሕይወት ከሆነው - ወደ ምንዳ እና ዘውታሪ ወደ ሆነው ዓለም - እሱም ከሞት በኋላ ወዳለው - ዓለም የሚሸጋገርበት ድልድይ ነው።
አላህ ለሰው ልጅ እንዲኖር የወሰነለት ጊዜ ሲጠናቀቅ አላህ የሞት መልአክን የሰውየውን ነፍስ ከአካሉ ነጥሎ እንዲወስድ ያዘዋል። ሰውየውም ነፍሱ ከመውጣቷ በፊት የጣእረ ሞት ስቃይን ከቀመሰ በኋላ ይሞታል። ነፍስን በተመለከተ፣ በአላህ ያመነችና ለእርሱም ታዛዥ ከነበረች አላህ በመንበረ ጸጋ - ጀነት - ያኖራታል። ከሞት በኋላ ባለው ትንሣኤ እና በስራ መመንዳትን ያስተባበለች ከነበረች ግን የዓለም መጨረሻ ጊዜ ደርሶ ቂያማ እስክትቆም ድረስ አላህ በመንበረ ስቃይ - በእሳት ውስጥ - ያኖራታል። ከዚያም ከየፍጥረታት የቀሩት ሁሉ ይሞቱና አላህ ብቻውን ይቀራል። ከዚያም አላህ እንደገና ፍጥረታቱን ሁሉ - ሌላው ቀርቶ እንስሳውን እንኳን - መጀመሪያውኑ እንደፈጠረው አድርጎ መላውን አካሉን ከመለሰለት በኋላ እያንዳንዷን ነፍስ ወደ ሰውነቷ ይመልሳታል። ይህም እያንዳንዱን ወንድም ይሁን ሴት፣ ሀብታምም ይሁን ድሀ፣ መሪም ይሁን ተመሪ ማንም ሳይበደል ሁሉም በሰራው ስራ ልክ ሊተሳሰበው፣ እያንዳንዱ ተበዳይም ከፊሉ ከከፊሉ በደሉን ሊያስመልስ ዘንድ እንስሳ እንኳ ሳይቀር በደሏን ከበደላት አካል ይመለስላታል። ከዚያም እንስሶቹ ጀነትም ሆነ ጀሀነም ስለማይገቡ አፈር ሁኑ ይባላሉ። የሰው ልጆችን እና አጋንንቶችን እያንዳንዱን በሥራው ይመነዳዋል። እርሱን የታዘዙትን እና መልዕክተኞቹንም የተከተሉትን አማኞች ምንም ያክል ድሀ ቢሆኑ ጀነት ያስገባቸዋል። እርሱን የካዱትንና ያስተባበሉትን ደግሞ ምንም ያክል በዓለም እጅግ ሀብታም እና የተከበሩ ሰዎች ቢሆኑ እንኳ ወደ ጀሃነም እሳት ይገባሉ። {አላህ ዘንድ በላጫችሁ በጣም አላህን ፈሪያችሁ ነው። አላህ ግልጽን ዐዋቂ ውስጥንም ዐዋቂ ነው።} [አል-ሑጁራት፥13]
ጀነት: በውስጧ ማንም ሰው ሊገልፀው የማይችል የፀጋ ዓይነቶች ያሉባት የደስታ ሀገር ናት። በውስጧ መቶ ደረጃዎች ያሉ ሲሆን በእያንዳንዱ ደረጃም ነዋሪዎች አሉ። በአላህ ላይ ባላቸው የእምነት ጥንካሬ እና ታዛዥነት መጠን ልክ የተለያየ ደረጃ ያገኛሉ። በጀነት ውስጥ ዝቅተኛው ደረጃ ላይ ያሉ ሰዎች በዱኒያ እጅግ በጣም የተመቸው ንጉስ ከሚያገኘው ፀጋ ብዙ እጥፍ ድርብ የሆነን ፀጋ ይጎናፀፋሉ። [10] ይህንንም ያልነው ሹዕባህ ካስተላለፈው ተከታዩ የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሐዲሥ በመመርኮዝ ነው፦ "ሙሳ ጌታቸውን 'ከጀነት ነዋሪዎች መካከል ዝቅተኛው ደረጃ ላይ ያለው ማን ነው?' በማለት ጠየቁ። አላህም እንዲህ አላቸው፦ 'ወደ ጀነት የሚገቡት ሁሉ ወደ ጀነት ከገቡ በኋላ የመጨረሻው ወደ ጀነት ለሚገባው ሰው 'ወደ ጀነት ግባ ይባላል' እርሱም እንዲህ ይላል፦ 'ጌታዬ ሆይ! ሰዎች ሁሉ የየራሳቸውን መኖርያ የሚይዙትንም ሁሉም ይዘው እንዴት (ብየ መግባት እችላለሁ)?' ሲል እንዲህ ይባላል። 'ከዱኒያ ነገሥታት መካከል እንደ አንድ ንጉሥ ፀጋ ቢሰጥህ ደስ ይልሃልን?' እርሱም 'ጌታዬ! በጣም ደስ ይለኛል እንጅ።' በማለት ሲመልስ፤ 'ያውና እርሱ አለልህ እና ጭማሪ እንደሱም አለልህ፣ ጭማሪ እንደሱም አለልህ፣...' እያለ አምስተኛው ላይ ሲደርስ 'ጌታዬ በጣም ተደስቻለሁ።' ይላል። አላህም እንዲህ ይለዋል፦ 'ይህ አለልህ፤ ከዚያም የሱን አስር እጥፍ አለልህ፤ ደስ ያለህንና ልብህ የከጀለው ሁሉ ተሰጥቶሀል።' እርሱም እንዲህ ይላል 'ጌታዬ ሆይ! በጣም ተደስቻለሁ።' ይላል።' ከዚያም (ሙሳ) እንዲህ አሉ '(ከነሱ) (ከጀነት ሰዎች) መካከል ከፍ ያለ ደረጃ ላይ ያለውስ?' (አላህም እንዲህ) አለው 'እነኝህማ መከበሪያቸውን እኔው ያቋቋምኩላቸው እና በላዩ ላይ ያተምኩላቸው ናቸው። ዓይንም ያላየውን፣ ጆሮም ያልሰማውን፣ በሰው ልጅ ልቦና ውል ብሎ የማያውቀውን ነው ያሰናዳሁላቸው።" (ሙስሊም፥189) የጀሀነም እሳት ደግሞ፦ አላህ ከእርሱ ይጠብቀንና- ትውስታው ልብን የሚያስደነግጥ እና ዓይኖችን የሚያስለቅስ የተለያዩ የስቃይና የመከራ ዓይነቶች ያሉበት ከሞት በኋላ በመጪው ዓለም ያለ የስቃይ ሀገር ነው።
በኣኺራ ሞት ቢኖር ኖሮ የጀሀነም ሰዎች ስለተመለከቷት ብቻ ይሞቱ ነበር፤ ነገር ግን ሞት አንድ ጊዜ ብቻ ነው። እሱም የሰው ልጅ ከዚህ የዱኒያ ሕይወት ወደ ቀጣዩ ዓለም የሚሸጋገርበት ነው። በታላቁ ቁርኣን ውስጥ ስለ ሞት፣ ከሞት በኋላ ስላለው ትንሣኤ፣ ስለ ተጠያቂነት (በስራ ስለመተሳሰብ)፣ ስለ ምንዳ (በስራ ስለመመንዳት)፣ ስለ ጀነት እና ስለ ጀሀነም የተሟላ መግለጫ ተጠቅሷል፤ በዚህ ባወሳነው ላይም ጥቆማ አለ።
ከሞት በኋላ ስላለው ትንሣኤ፣ ስለ ተጠያቂነት (በስራ ስለመተሳሰብ) እና ስለ ምንዳ (በስራ ስለመመንዳት) የሚያስረዱ ማስረጃዎች እጅግ በርካታ ናቸው። በታላቁ ቁርኣን አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ከእርሷ (ከምድር) ፈጠርናችሁ። ወደ እርሷም ውስጥ እንመልሳችኋለን። ከእርሷም በሌላ ጊዜ እናወጣችኋለን።}
[ጧሀ፥ 55]
ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡ {ለእኛም ምሳሌን አደረገልን፤ መፈጠሩንም ረሳ፤ «አጥንቶችን እነርሱ የበሰበሱ ሲኾኑ ሕያው የሚያደርጋቸው ማነው?» አለ።} [ያሲን፥ 78 - 79]
አላህ እንዲህ ይላል:
{እነዚያ የካዱትን በፍጹም የማይቀሰሱ መኾናቸውን አሰቡ። «አይደለም በጌታዬ እምላለሁ። በእርግጥ ትቀሰቀሳላችሁ። ከዚያም በሠራችሁት ሁሉ ትነገራላችሁ። ይህም በአላህ ላይ ቀላል ነው።» በላቸው።}
[አተጋቡን፥ 7] የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት፦ 1_ በመጀመሪያው አንቀፅ ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ እንዲህ አለ፦ የሰው ልጆችን ከምድር ፈጠረ፤ ይህም የሆነው አባታቸውን አደም - የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን - ከአፈር በፈጠረ ጊዜ መሆኑን አሳወቀን፤ ከዚያም ከሞቱ በኋላ በቀብራቸው ወደ አፈር እንደሚመልሳቸውም አሳወቀን፤ ለእነሱ እንደ ክብር ማለት ነው። ከዚያም መልሶ ደግሞ እንደገና ከሷው እንደሚያስወጣቸው አሳወቀን፤ ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ ያሉትን ሁሉ ከየመቃብራቸው ህያው አድርጎ በድጋሚ ይቀሰቅሳቸዋል፣ በየስራቸው ከተሳሰባቸው በኋላ እንደየስራቸው ይመነዳቸዋል። 2- በሁለተኛው አንቀፅ - አላህ፥ ከሞት በኋላ መቀስቀስን ለሚያስተባብል፣ አጥንታችንም ብናኝ ከሆነ በኋላ ህይወት መዝራቱ ደንቆት ለሚያስተባብል ከሀዲ ምላሽ በመስጠት ህያው እንደሚያደርጋት አሳወቀን። ምክንያቱም መጀመሪያውኑ ያላንዳች ነገር የፈጠራት እሱው ነውና። 3- በሦስተኛው አንቀጽ ደግሞ፡ አላህ፥ ከሞት በኋላ በትንሣኤ ለሚክዱ፣ ለብልሹ ጥያቄያቸው ምላሽ በመስጠት መልእክተኛውን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ጠንካራ መሀላን ምሎ አላህ ከመቃብራቸው እንደሚቀሰቅሳቸው፣ ሲሰሩት የነበሩትም ስራ ምን እንደነበር እንደሚነግራቸውና በስራቸውም እንደሚመነዳቸው፤ ይህም አላህ ዘንድ ቀላል እንደሆነ እንዲያሳውቅ አዘዘው።
አላህ በትንሣኤና በእሳት ለሚያስተባብሉ ከሐዲዎችም በገሃነም እሳት እንደሚቀጣቸው በሌላ አንቀፅ ላይ ተናግሯል። እንዲህም ይባላሉ፦
{«ይህ ያ በእርሱ ታስተባብሉ የነበራችሁት መለያው ቀን ነው» (ይባላሉ)።}
[አስ-ሰጅዳህ፥20]
የሰውል ልጅ ድርጊትና ቃል መቆጣጠር:
በእርግጥ እርሱ - ኃያሉ እና ልዑል ጌታችን - እያንዳንዱ ሰው ለወደፊት የሚናገረውን እና የሚያደርገውን ሁሉ ጥሩም ሆነ መጥፎ፣ በስውርም ይሁን በግልፅ የሚፈፅመውን የሚያውቅ መሆኑን አሳወቀ፤ ይህንንም ሰማያትንና ምድርን እንዲሁም የሰው ልጆችንም ሆነ ሌሎችን ከመፍጠሩም በፊት እርሱ ዘንድ በተጠበቀው ሰሌዳ ውስጥ በፅሁፍ እንዳሰፈረውም አሳወቀ። ይህ ከመሆኑም ጋ ለእያንዳንዱ ሰው ሁለት መላእክትን መደበለት፤ አንዱ በቀኝ በኩል ሆኖ መልካም ሥራዎችን ይጽፋል፤ ሌላኛው ደግሞ በግራ በኩል ሆኖ መጥፎ ሥራዎችን ይጽፋል፤ ሁለቱም ሲፅፉ ምንም ነገር አያመልጣቸውም። የላቀው ልዑሉ ጌታችን - እያንዳንዱ ሰው የተናገረው ቃሉ እና የፈፀመው ተግባሩ የተፃፈበትን መዝገቡን በፍርድ ቀን እንደሚሰጠውም ተናግሯል። ስለዚህም ምንንም ነገር ሳያስተባብል ያነባታል፤ ለሚያስተባብል ደግሞ የላቀው አላህ መስሚያውን፣ መመልከቻውን፣ ሁለት እጆቹን፣ ሁለቱ እግሮቹን እንዲሁም ቆዳውንም የሠራውን ሁሉ እንዲናገሩ ያደርጋቸዋል።
ይህም በታላቁ ቁርኣን ውስጥ በዝርዝር ተብራርቷል። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ከቃል ምንም አይናገርም በአጠገቡ ተጠባባቂና ዝግጁ የኾኑ (መላእክት) ያሉበት ቢኾን እንጅ።}
[ቃፍ፥18]
አላህ እንዲህ ይላል: {በእናንተ ላይ ተጠባባቂዎች ያሉባችሁ፤ ስትሆኑ፤ (10) የተከበሩ ጸሐፊዎች የሆኑ፤ (ተጠባባቂዎች)። (11) የምትሠሩትን ሁሉ የሚያውቁ። (12)} [አል-ኢንፊጧር፥10 - 12]
የአንቀፆቹ ማብራሪያ፦
-የላቀው እና ከፍ ያለው- አላህ ለእያንዳንዱ ሰው ሁለት መላእክትን መደበለት፤ አንዱ በቀኝ በኩል ሆኖ መልካምነትን የሚፅፍ ረቂብ (ተቆጣጣሪ) ሲሆን ሌላኛው ደግሞ በግራ በኩል ሆኖ መጥፎነትን የሚፅፍ ዓቲድ (ተጠባብቂ) ናቸው። አላህ በመጨረሻዎቹ አንቀፆች ለሰው ልጆች ስራቸውን ሁሉ የሚመዘግቡ የተከበሩ መላእክቶችን እንደመደበላቸው አሳወቀ። ለመላእክቶቹም የሰው ልጆችን እያንዳንዱ ድርጊት በማወቅም ሆነ በመፀፉ ረገድ ችሎታን እንዳደረገላቸውም አሳወቀ። እርሱም እነርሱን ከመፍጠሩም በፊት አውቆትና በለውሐል መሕፉዝም ፅፎት እንደነበረው ሁሉ ማለት ነው።
ሸሀዳህ፡
ከአላህ በቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ እመሰክራለሁ፤ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ፤ ጀነትም እውነት፣ ጀሀነምም እውነት መሆኑን፣ ምንም ጥርጥር የሌለበት እለተ_ ትንሳኤ እየመጣ መሆኑን እመሰክራለሁ፤ አላህ በመቃብር ውስጥ ያሉትን ለሒሳብ እና ለቅጣት እንደሚያስነሳ እና አላህ በመጽሐፉ ወይም በመልእክተኛው አንደበት (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የተናገረው ሁሉ ትክክል መሆኑንም እመሰክራለሁ። አስተዋይ የሆንክ ሰው ሆይ! በዚህ የምስክርነት እንድታምን፣ እንድታውጅ እና በትርጉሙም እንድትሠራበትም እጋብዝሀለሁ። የመዳን መንገድ ይሀው ነውና።
ሁለተኛው ክፍል፦ መልዕክተኛውን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ማወቅ፦
አስተዋይ የሆንክ ሰው ሆይ! የፈጠረህ ጌታህ እንደሆነና በሠረኸው ሥራህም ልክ ምንዳህን ሊመነዳህ ከሞት እንደሚያነሳህ ካወቅህ አንተም ሆንክ ሌላው እርሱን እንድትታዘዙትና እንድትከተሉት የታዘዛችሁበትን መልዕክተኛ እንደላከም እወቅ። እርሱንም እንድትታዘዙትና እንድትከተሉትም አዘዘ፤ ይህንን መልእክተኛ በመከተል እና በመመሪያው በመመራት ካልሆነ በቀርም ለእሱ ትክክለኛውን አምልኮ የሚታወቅበት ምንም መንገድ እንደሌለም አሳወቀ።
እናም ይህ ሰዎች ሁሉ ሊያምኑበት እና ሊከተሉትም የሚገባቸው የሆነው ክቡር መልእክተኛ፥ የመልእክተኞች መደምደሚያ፣ ወደ ሰው ልጆች ሁሉ የተላኩ የአላህ መልእክተኛ፤ የማይፅፉና የተፃፈንም የማያነቡ ናቸው። ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ነብዩሏህ ሙሳ እና ዒሳ - የአላህ ሰላም በሁለቱም ላይ ይስፈንና - በተውራትና በኢንጂል አይሁዶችና ክርስትያኖች መጽፎቻቸውን መጫወቻ አድርገው ከመበረዛቸው በፊት ከአርባ በላይ በሆኑ ቦታዎች ላይ ያበሰሯቸው ነብይ ናቸው። [11]
[11] "አልቢሻረቱ ቢሙሓመዲን"(የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በተውራት እና በኢንጂል ውስጥ እንደተጠቀሰው - አልጀዋቡ ሶሒሕ ሊመን በደለ ዲነል መሲሕ “1” በ ሸይኹል ኢስላም አሕመድ ኢብኑ ተይሚያህ እንዲሁም መጽሐፉን (ሂዳያት አል-ሒያራ) በእውቁ ሸይኽ ሙሐመድ ኢብኑል ቀይም እና (አስ-ሲራ አን-ነበዊያህ) ኪታብ የኢብኑ ሂሻም እና የኢብኑ ከሲር የታሪክ መጽሐፍ ውስጥ ነብያዊ ተአምራትን እና ሌሎችንም ይመልከቱ።
እናም ይህ አላህ መልእክተኞቹን የደመደመባቸው እና ለሰዎች ሁሉ የላካቸው የተከበሩ ነብይ ሙሐመድ ቢን ዐብደላህ ቢን ዐብዱል ሙጠሊብ አል-ሃሺሚይ አል ቁረሺይ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ናቸው። በምድር ላይ እጅግ በከበረ ነገድ ውስጥ በጣም የተከበረ እና እውነተኛ ሰው፤ የአላህ ነብይ ኢብራሂም ልጅ ከሆኑት ከአላህ ነብይ ኢስማዒል ዝርያ ናቸው። የመልእክተኞች መደምደሚያ የሆኑት ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በ570 ዓ /ልደት በመካ ተወለዱ።
በተወለዱ ምሽት እና ከእናታቸው ማህፀን በወጡበት ቅጽበት ሰዎችን ያስገረመ ታላቅ ብርሃን ፈንጥቆ አጽናፈ ዓለምን አብርቷል፤ ይህም በታሪክ መጽሐፍት ውስጥ ተመዝግቧል። በመካ ካዕባ ውስጥ የሚያመልኩት የቁረይሽ ጣዖታትም ተደፍተው ወድቀዋል፤ የፋርስ ንጉሥ የኪስራ አእማደ በርም ተንቀጠቀጠ፤ አስራ ምናምን በረንዳዎችም ረገፉ፤ ፐርሺያኖች የሚያመልኩት የጣኦት እሳትም ጠፋ፤ ከዚያ በፊት ግን ለሁለት ሺህ ዓመታት ያክል ጠፍቶ አያውቅም ነበር።
ይህ ሁሉ ከአምላክ ውጭ የሚመለኩትን ጣዖታት የሚያጠፉት የመልክተኞች መደምደሚያ የሆኑት ነብይ ለመወለዳቸው ለምድር ሰዎች ከኃያሉ አምላክ የተላከ ማስታወቂያ ነው። እርሱም ፐርሺያኖችንም ይሁን ሮማውያንን አላህን ብቻ እንዲያመልኩ፤ ወደ ትክክለኛው ኃይማኖትም እንዲገቡም ይጠራቸዋል። እምቢ ካሉ ደግሞ እርሱና እርሱን የተከተሉት ይፋለሟቸዋል። ከዚያም አላህ በነርሱ ላይ ይረዳቸውና በምድርም ላይ አምላካዊ ብርሃኑ የሆነው ሃይማኖቱን ያሰራጫል። አላህ መልእክተኛውን ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከላከ በኋላ በእውነቱ የሆነውም ይህ ነው።
እናም አላህ የመልክተኞቹን መደምደሚያ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከእሳቸው በፊት ከነበሩት መልእክተኞች ወንድሞቻቸው መካከል በተለያዩ መለያዎች ሰጥቷቸዋል፤ ከእነዚህም መካከል፦
አንደኛ፡ እርሳቸው የመልእክተኞች መደምደሚያ ናቸው፤ ከእርሳቸው በኋላ መልክተኛም ሆነ ነቢይ የለም።
ሁለተኛ፡ ተልእኳቸው ለሁሉም ሰዎች አጠቃላይ መሆኑ፤ ሰዎች ሁሉ የሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሕዝብ ናቸው። እርሳቸውን የሚታዘዝ እና የሚከተል ጀነት የሚገባ ሲሆን ያልታዘዛቸው ደግሞ ወደ ጀሃነም ይገባል። አይሁዶችና ክርስቲያኖችም እንኳ ቢሆኑ እርሳቸውን የመከተል ግዴታ አለባቸው። እርሳቸውን የማይከተልና በእርሳቸውም የማያምን ሙሳን፣ ዒሳን እና ነቢያትን ሁሉ ክዷልና ነው።
የአላህ ነብይ ሙሳም ይሁኑ ዒሳ እንዲሁም ሌሎቹም ነብያት ሁሉ ነብዩ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከማይከተል ሰው ሁሉ የጠሩ ናቸው። ምክንያቱም አላህ ሲልካቸው እነርሱም እንዲያምኑባቸውና ህዝባቸውንም የእርሳቸው ተከታይ እንዲሆኑ ዳዕዋ (ጥሪ) እንዲያደርጉ አዟቸዋልና። እንዲሁም ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የተላኩበት ዲን (እምነት) አላህ ሌሎቹንም መልእክተኞች የላከበት ዲን (እምነት)ነውና። የሀይማኖቱ መሟላትና መግራትም በነኚህ በተከበሩት የመልእክተኞቹ መደምደሚያ በሆኑት መልእከተኛው አደረገ። በመሆኑም ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከተላኩ በኋላ ከእስልምና ሀይማኖት በቀር ሌላን ሀይማኖት ሊይዝ አይፈቀድም። ምክንያቱም አላህ ሌሎቹንም ሀይማኖቶችን ሁሉ የሻረበት የተሟላ እና በአምላካዊ ጥበቃ ተጠብቆም የሚዘልቀው ሀይማኖት በመሆኑ ነው።
አይሁድና ክርስትናን አስመልክቶ አላህ እንዳወረዳቸው ባሉበት የዘለቁ ሳይሆኑ የተዛቡ ኃይማኖቶች ናቸው። ነብዩ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የተከተለ ሙስሊም ሁሉ ሙሳንና ዒሳን እንዲሁም ሌሎቹንም ነብያቶች በአጠቃላይ እንደተከተለ ነው። ከእስልምና ውጭ የሆነ ሁሉ ደግሞ የሙሴና የኢየሱስ ተከታይ ነኝ ብሎ ቢሞግት እንኳ በሙሳም ሆነ በዒሳ እንዲሁም በሌሎቹም ነብያቶች ሁሉ እንደካደ ነው የሚቆጠረው። ለዚህም ነው የአይሁድ ልሂቃኖችና ከክርስትያኑም አስተዋይና ብልህ ፃድቃኖች በነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አምነው ወደ እስልምና መግባት ላይ ተጣድፈው የታዩት። ***
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ተአምራት[12]።
በቁርአን ውስጥ ያላት ስያሜ “አያት” (ምልክት) በሚል የተገለፀች ስትሆን ትክክለኛው መገለጫዋም ያው ነው። ተአምር (ሙዕጂዛ) በሚል የምንገልፀው ከተለምዶ ውጭ የሆኑትን ነጥሎ ለማመልከት ነው። የነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ታሪክ አጥኝዎች ለነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የተከሰቱላቸው እውነተኛ የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸውን የሚያመላክቱ ተዓምሮች በቁጥር ከሽህ በላይ መሆናቸውን ገልፀዋል። ከእነዚህም መካከል፦ 1‐ አላህ በትከሻቸው መሀል ያበቀለው የነብይነት ማህተም፤ ይኸውም ኪንታሮቶችን ከመሰሉ ነገሮች የተሰራ ነው።[13] [13] አሠኣሊል የኪንታሮት ብዙ ቁጥር አመላካች ለማለት ሲሆን እንደ ሽምብራ የሚያካክሉ ትናንሽ በሰውነት ቆዳ ላይ የሚወጡ ነጠብጣቦች ናቸው። እናም ይህ ማህተምም ቅርፁ እንደ ጨረቃ ክብ እና እንደ ርግብ እንቁላል መጠን ነበር፤
2‐ በበጋው ወለል ባለ ሀሩር ፀሀይ ላይ ሲንቀሳቀሱ ደመና ይከልላቸው (ያጠልላቸው) መሆኑ።
3‐ የጠጠሮች በእጃቸው ላይ ሆነው “ተስቢሕ” ማድረጋቸው(አላህን ሲያልቁ መደመጣቸው)ና ዛፍ ለሳቸው ሰላምታን ማቅረቡ።
4‐ በመጨረሻው ዘመን ስለሚከሰቱ የሩቅ ሚስጥሮች ተናግረው አንድ በአንድ በተናገሩት መልኩ በተጨባጭ እየተከሰቱ መሆናቸው። እነኝህ የመልዕክተኞች መደምደሚያ የሆኑት ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ካለፉ በኋላ እስከ እለተ ፍፃሜ እየተከሰቱ የሚዘልቁትና አላህ ያሳወቃቸው የሆኑት የተናገሯቸው የሩቅ ምስጢሮች በሐዲሥ መዛግብትና ስለ እለተ ፍፃሜ ምልክቶች በሚያወሩ ኪታቦች ሰፍረው ይገኛሉ። ለምሳሌ፦ የኢብኑ ከሢር “አን‐ኒሀያህ”፣ “አል‐አኽባሩል ሙሻዓህ ፊ አሽራጢ‐ስ‐ሳዓህ” እና “አብዋቡል ፊተን ወልመላሒም” በመሰሉ የሓዲሥ መዛግብትን መጥቀስ ይቻላል። እነዚህ ተአምራትም ከሌሎቹ ቀደምት ነብያቶች ተአምራትም ጋ የሚመሳሰሉ ናቸው። ይሁን እንጅ አእምሯዊ በሆነ እስከ ዱንያ ፍፃሜ ድረስ በገፀ ምድር የሚቆይ ተአምር ሰጥቷቸዋል። ይኸውም የአላህ ቃል በሆነው የተከበረው ቁርኣን ነው። ያ አላህ ጥበቃ እንደሚያደርግለት ቃል የተገባለት፣ የማዛባት እጆች ሊዘረጉበት አይቻላቸውም። ማንም የሆነች ፊደልን እንኳ ለመለወጥ ቢያስብ ሴራው ይኮላሻል። ያውና በሚልዮኖች የሚቆጠሩ የቁርኣን ቅጅዎች በህዝበ ሙስሊሙ ተሰራጭተው የሚገኙ ሲሆን አንዱ ከሌላው በሆሄ እንኳ አይለያዩም። የተውራትና የኢንጂል ቅጅ ግን አንዱ ከሌላው የሚለያይ በርካታ ስርጭት ነው የሚገኘው። ምክንያቱም አይሁድና ክርስትያኖች መፅሀፋቸውን እንዲጠብቁ ኃላፊነቱ በነርሱው ላይ የተጣለ በመሆኑ እያዛቡ ተጫውተውባቸዋልና ነው። ቁርኣንን ግን ጥበቃውን አላህ ከራሱ ውጭ ለማንም አሳልፎ አልሰጠውም። ይልቁንም በተከታዩ አንቀፅ እንዳሳወቀን ቁርአንን የሚጠብቀው የላቀው አላህ ነው፦ {እኛ ቁርኣንን እኛው አወረድነው። እኛም እርሱን ጠባቂዎቹ ነን።} [አል-ሒጅር፥9] ቁርኣን የአላህ ቃል ለመሆኑ እና ነብዩ ሙሐመድም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኛ ለመሆናቸው አእምሯዊ ማረጋገጫዎች እና አምላካዊ ቃል ከሆነው ቁርኣን ማስረጃዎች፦ ቁርኣን የአላህ ቃል ለመሆኑ እና ነብዩ ሙሐመድም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኛ ለመሆናቸው አመክንዮአዊ እና አእምሯዊ ከሆኑ ማስረጃዎች መካከል እንደ ቀደምቱ ነብያትን አስተባባዮች የቁረይሽ ሙሽሪኮችም ነብዩ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ባስተባበሉት ጊዜ፥ አላህ ያስቀመጠላቸው ውርርድ ነው። አላህ አምሳያውን ማምጣት ይችሉ እንደሁ እንዲያመጡ ተወራረዳቸው። በራሳቸው ቋንቋ ብሎም በቋንቋቸውም እጅግ የመጠቁ ተናጋሪዎች ከመሆናቸውም ጋ፣ በመካከላቸውም እጅግ ታላላቅ አንደበተ_ርቱኦች፣ አጅግ የረቀቁ ተናጋሪዎቻቸው፣ ጮሌ ገጣሚዎች ያሉ ከመሆናቸውም ጋ በውርርዱ መሰረት አምሳያውን ማምጣት ተሳናቸው። ከዚያም ከአምሳያው በሆነ አስር የተቀጠፉ ምእራፎችን ማምጣት ከቻሉ እንዲያመጡ ተፎካከራቸው አሁንም ተሳናቸው፤ ከዚያም አንዲትን ምእራፍ እንኳ ማምጣት ይችሉ እንደሁ ተፎካከራቸው አሁንም የሚሳናቸው መሆኑን ባረጋገጡ ጊዜ እነርሱም የሚሳናቸው እንደሆኑ እና መላው የሰው ልጅና አጋንንትም ቢሆን ከፊሉ ለከፊሉ ተረዳድተው እንኳ አምሳያውን ማምጣት እንደሚሳናቸው በይፋ አወጀ። የላቀው አላህ እንዲህም አለ፦
{«ሰዎችም ጋኔኖችም የዚህን ቁርኣን ብጤ (መሰል) በማምጣት ላይ ቢሰበሰቡ ከፊላቸው ለከፊሉ ረዳት ቢሆንም እንኳ ብጤውን (መሰሉን) አያመጡም» በላቸው።}
[አል-ኢስራእ: 88]
ቁርኣን የነብዩ ሙሐመድ ወይንም የሌላ ሰው ንግግር ቢሆን ኖሮ ሌላውም የቋንቋው ተናጋሪ አፈቀላጤ አምሳያውን ማምጣት ይችል ነበር።
ቅሉ ግን ቁርአን የአሏህ ቃል ነው፤ የአሏህ ንግግር ደግሞ ከፍጡራኖቹ ንግግር አኳያ ያለው በላጭነት አሏህ በሰው ልጆች ላይ ካለው በላጭነት አንፃር የሚታይ ነው። ልክ ለአላህ ብጤ (አምሳያ) እንደሌለው ሁሉ የአላህ ቃልም እንዲሁ ብጤ (አምሳያ) የለውም። በዚህም መሰረት ቁርላን የላቀው አላህ ቃል መሆኑና ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸው ግልፅ ይሆናል። ምክንያቱም የአላህን ቃል ይዞ መምጣት የሚችለው ከርሱ የተላከ መልዕክተኛ ብቻ ነውና። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ሙሐመድ ከወንዶቻችሁ የአንድም ሰው አባት አይደለም። ግን የአላህ መልክተኛና የነቢያቶች መደምደሚያ ነው። አላህም ስለ ነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው።}
[አልአሕዛብ፥40]
አላህ እንዲህ ይላል:
{አንተንም ለሰዎች ሁሉ በመላ አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን ቢሆን እንጂ አላክንህም። ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም።}
[ሰባእ 28]
አላህ እንዲህ ይላል:
{(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም።}
[አል-አንቢያእ: 107]
የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት፦ 1‐ የላቀው አላህ በመጀመሪያው አንቀፅ መልዕክተኛውን ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ወደ ሰው ልጆች ሁሉ የላካቸው እንደሆነ፤ ከእርሳቸው በኋላ ነብይ የሌለና የመልዕክተኞች መደምደሚያም መሆናቸውን፤ ከየትኛውም ሰው ይበልጥ ተገቢ መሆናቸውን፥ አላህ ስለሚያውቅ ለተልእኮው እጩ አድርጎና ለነብይነትም መደምደሚያነት እንደመረጣቸው አሳወቀን።
2‐ የላቀው አላህ በሁለተኛው አንቀፅ ደግሞ፦ አላህ መልዕክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ለነጩም ሆነ ለጥቁሩ፣ ዓረብ ለሆነውም ይሁን ዓረብ ላልሆነው እንደላካቸው፤ አብዛኛው ሰው ግን እውነታን ስለማያውቅ በሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አምነው ተከታዩ ሳይሆኑ እንደቀሩ ነገረን። 3‐ በሶስተኛው አንቀፅ ደግሞ አላህ መልዕክተኛውን ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በቀጥታ እያናገረ ለዓለማት በሙሉ እዝነት አድርጎ እንደላካቸው ግልፅ አደረገ፤ እሳቸው አላህ ለሰዎች የዋለላቸው የእዝነት ፀጋ በመሆናቸው በሳቸው አምኖ የተከተላቸው የአላህን እዝነት በመቀበሉ ጀነት አለለት። በሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ያላመነ እና ተከታያቸውም ያልሆነ ግን የአላህን እዝነት አሻፈረኝ ብሏልና እሳት ለመግባትና ለአሳማሚ ቅጣት የተገባ መሆኑን አሳወቀን። በአላህና በመልዕክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የማመን ጥሪ! ስለዚህም አስተዋይ የሆንክ ሰው ሆይ! አላህን በጌትነት፣ በመልዕክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በመልዕክተኝነት አምነህ በመቀበል እንድትከተላቸው፣ አላህ መልዕክተኛውን የላከበት በሆነው ድንጋጌያቸው ምንጩን የተከበረውን ቁርኣንና ከነብያቶች መደምደሚያ በተረጋገጡ ሐዲሦች ላይ የተመሰረተውን በእስልምና እንድታምን ጥሪያችንን እናቀርባለን። ምክንያቱም ይህ ሀይማኖት አላህ ባዘዘው ካልሆነ በቀር የሚያዝ አይደለም፤ አላህ ከከለከለው ካልሆነ በቀር አያስጠነቅቅምና ነው። በመሆኑም ልቦናህን የጌታህን ፊት ብቻ ከጅለህበት “አላህ ብቸኛው አምላኬም ጌታዬ ነው” በል፤ እንዲህም በል “ነብዩ ሙሐመድም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸውን አምኛለሁ” ከዚያም ተከተላቸው ከዛ ውጭ የምትድንበት የለህምና። አላህ እኔንም ሆነ እናንተን ለእድለኝነትና ለመዳን ተውፊቁን ይስጠን (ለስኬት ያብቃን)። ኣሚን!!!
***
ሶስተኛው ክፍል፦ እውነተኛውን ሃይማኖት፥ እስልምናን ማወቅ፤
አንተ አስተዋይ የሆንክ ሰው ሆይ! አንተን የፈጠረህ ሲሳይም የሚለግስህ ጌታህ አላህ ተጋሪ የሌለው ብቸኛው እውነተኛ አምላክ መሆኑን ከተረዳህ እርሱን ብቻ ልታመልከው ግድ ይልሃል። እንዲሁም ነብዩ ሙሐመድም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከአላህ ላንተም ለመላው የሰው ዘርም የተላኩ መልዕክተኛ መሆናቸውንም ካወቅክ በላቀው አላህና በመልዕክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ያለህ እምነትም እስልምናን ተረድተህ በእስልምና እስካልኖርክበት ድረስ እምነትህ ከንቱ ነው። ምክንያቱም አላህ ወዶ የሚቀበለውና መልዕክተኞቹንም ያዘዘበት መደምደሚያቸው የሆነውን ሙሐመድንም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ወደ ሰው ልጆች ሁሉ በመላክ እንዲሰሩበትም ያዘዘበት ሀይማኖት ነውና።
*** ኢስላምን ለማወቅ የነብያት መደምደሚያ እና ወደ ሰው ዘር ሁሉ የተላኩት የአላህ መልዕክተኛ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦
«(እስልምና ማለት) ላ ኢላሃ ኢለላህ ሙሐመደን ረሱሉላህ በማለት ከአላህ በቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ አለመኖሩን እና ሙሐመድ የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸውን መመስከር፤ ሰላትንም ደንብና ስርዓቷን አሟልተህ መስገድ፤ ዘካንም መስጠት፤ የረመዷንንም ወር መፆም እና አቅምህ ከቻለ ደግሞ ሐጅ ማድረግህ ነው።»
[14] ሙስሊም (8)፤ አቡዳውድ (4695) ዘግበውታል።
እስልምና አላህ የሰው ልጆችን ሁሉ ያዘዘበት ዓለም አቀፋዊ፤ የአላህ መልዕክተኞችም አምነው ሙስሊምነታቸውን ያወጁበት፤ የላቀው አላህ ከእርሱ ውጭ ሌላን እንደማይቀበል ገልፆ ትክክለኝነቱን ያወጀበት ሃይማኖት ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {አላህ ዘንድ የተወደደው ሀይማኖት እስልምና ነው።} [ኣሊ-ዒምራን፥19]
ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡
{ከኢስላም ሌላ ሃይማኖትን የሚፈልግ ሰው፥ ፈጽሞ ከርሱ ተቀባይ የለውም። እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከከሳሪዎቹ ነው።}
[ኣሊ-ዒምራን፥85]
የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት:
1‐የላቀው አላህ እርሱ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ሃይማኖት እስልምና ብቻ መሆኑን አሳወቀ።
2‐የላቀው አላህ በሁለተኛው አንቀፅ ከእስልምና ውጭ የሆነን ሃይማኖት እንደማይቀበል፤ ከሞት በኋላ ብቸኛዎቹ ስኬታማዎች ሙስሊሞች ብቻ መሆናቸውን፤ ከእስልምና ውጭ ሆነው የሚሞቱ ሰዎች በኣኺራ (በመጨረሻው ዓለም) ኪሳራ ላይ መሆናቸውንና ቅጣትም እንዳላቸው አሳወቀ።
ለዚህም ነው ነብያቶች ሁሉ እጅ እግራቸውን ለአላህ የሰጡት፤ ሙስሊሞች መሆናቸውን ያወጁት። ለአላህ ተማርኮ እስልምናን ካልተቀበለ አካል ሁሉ የፀዱ መሆናቸውንም አውጀዋል። ከአይሁድም ይሁን ከክርስትያን መዳንን እና ስኬትን የፈለገ ሁሉ ወደ እስልምና መግባት ይኖርበታል። የኢስላምን መልዕክት ያስተማሩትን ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ተከታይ ሊሆን ይገባል፤ ትክክለኛ የሙሳም ሆነ የዒሳ ተከታይ መሆን የሚችለውም ያኔ ነው። ምክንያቱም ሙሳ፣ ዒሳም ይሁን ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በሁሉም ላይ ይስፈንባቸውና) እንዲሁም ሁሉም ነብያቶች ሙስሊሞች ናቸው፤ አላህ ሁሉንም የላከበት ዓላማ እና እነርሱም ጥሪ ያደረጉት ወደ ኢስላም ነውና። በመሆኑም ከነብያቶች መደምደሚያ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከተላኩ በኋላ እስከ መጨረሻው እለተ የሚመጣው ሰው ሁሉ ራሱን ለአላህ ተገዥ የሆነ ሙስሊም ብሎ ለመጥራትም ይሁን አላህ ይህን ሙግቱን ሊቀበለው የሚችለው በነብዩ ሙሐመድ የአላህ መልዕክተኝነት አምኖ ተከታይ ሲሆን፤ አላህ ባወረደለት ቁርኣንም አምኖ ሲገኝ ነው። የላቀው አላህ በታላቁ ቁርኣን እንዲህ ብሏል፦
{«አላህን የምትወዱ እንደሆናችሁ ተከተሉኝ፤ አላህ ይወዳችኋልና። ኀጢኣቶቻችሁንም ለናንተ ይምራልና። አላህም መሓሪ አዛኝ ነው።»በላቸው}
[ኣሊ-ዒምራን፥31]
የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት:
አላህ መልዕክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አላህን እወዳለሁ ብሎ ለሚሞግት ሁሉ “በትክክል አላህን የምትወዱ ከሆናችሁ እኔን ተከተሉኝና አላህም ይወዳችኋል፤ ምክንያቱም አላህ ሊወዳችሁና ወንጀላችሁንም ሊምራችሁ የሚችለው የላከውን መልዕክተኛ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አምናችሁ ከተከተላችሁት ብቻ ነውና” ብለው እንዲሉ እያዘዛቸው ነው።
ይህ አላህ መልዕክተኛውን ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ወደ ሰው ዘር ሁሉ የላከበት እስልምና፦ የተሟላ፣ ሁለንተናዊና ገር የሆነው ነው፤ ይህ እስልምና አላህ ሙሉ ያደረገውና ለባርያዎቹ የወደደላቸውና ከእርሱም ውጭ ሌላን የማይቀበልበት የሆነ ሃይማኖት ነው፤ ይህ ሃይማኖት ነብያቶች ያበሰሩበትና ያመኑበት የሆነው የታወቀው እስልምና ነው። የላቀው አላህ በታላቁ ቁርኣን እንዲህ ብሏል፦
{ዛሬ ሃይማኖታችሁን ለናንተ ሞላሁላችሁ፤ ጸጋዬንም በናንተ ላይ ፈጸምኩ፤ ለእናንተም ኢስላምን ከሃይማኖት በኩል ወደድኩ።}
[አል ማኢዳህ 3]
የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት:
የላቀው አላህ በዚህ በመልዕክተኞች መደምደሚያ በሆኑት ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አላህ ረድቷቸው እስልምና ተስፋፍቶ የቁርኣን መውረድም የተሟላ በሆነበት በእድሜያቸው የመጨረሻ ወቅቶች ላይ በመሰናበቻው ሐጅ ከሙስሊም ወገኖቻቸው መካከል በመካ ዓረፋ ላይ ሆነው ጉዳያቸውን ለአላህ እየነገሩና እየተማፀኑት ሳሉ ባወረደው በተከበረው አንቀፅ እንዲህ በማለት አወጀ።
የላቀው አላህ ለሙስሊሞች ዲናቸውን እንዳሟላላቸው፤ ነብዩ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በመላክና ታላቁ ቁርኣንን በማውረድ ፀጋውን ሙሉ እንዳደረገ ተናግሯል። እንዲሁም ኢስላምንም ከሃይማኖት በኩል መቼም የማይቆጣበት እንደውም የወደደላቸው እንደሆነና ከርሱ ውጭ ሌላን የማይቀበልበት ብቸኛው ሃይማኖት መሆኑን አውጇል።
የላቀው አላህ ነብዩ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ወደ ሰው ዘር ሁሉ የላከበት የሆነው የእስልምና ሃይማኖት የተሟላ፣ ሁለንተናዊ፣ ለሁሉም ጊዜና ቦታና ህዝብ ተስማሚ የሆነው ነው። ይህ ኢስላም የዕውቀት፣ የፍትህና የመልካምነት ሀይማኖት፤ የተለያየ የህይወት መስክን የሚያስተካክል የተሟላ ግልፅ የህይወት ፈለግ፤ ትክክለኛ የሆነ አስተዳደራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ አካሄድ ያለው ሀይማኖትም ሀገርም ነው። እያንዳንዱ ለሰው ልጅ በኑሮው የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ ያካተተ እና ከሞት በኋላ ያላቸውን ደስተኝነትም ያጠቃለለ ነው።
***
የኢስላም ማእዘናት
አላህ መልዕክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የላከበት የሆነው እስልምና ከአምስት ማእዘናት የተገነባ ነው። ማንም ሰው በእነርሱ አምኖ በአግባቡ እስካልተወጣቸው ድረስ ትክክለኛ ሙስሊም አይሆንም። እነሱም፦ 1‐ “ላ ኢላሃ ኢለላህ ሙሓመዱን ረሱሉላህ” ብሎ በአላህ ብቸኛ ተመላኪነትና በነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኝነት መመስከር 2‐ ሰላትን በተገቢው መልኩ አሟልቶ መስገድ። 3‐ ዘካ መስጠት። 4‐ የረመዷንን ወር መፆም። 5‐ አቅሙ የሚችል ከሆነ በተከበረው የአላህ ቤት ሐጅ ማድረግ [15] [15] የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦ «እስልምና ከአምስት መሰረቶች ተገነባ፥ “ላ ኢላሃ ኢለላህ ሙሓመዱን ረሱሉላህ” ብሎ እአላህ ብቸኛ ተመላኪነትንና የነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኝነት መመስከር፣ ሰላትን በተገቢው መልኩ አሟልቶ መስገድ፣ ዘካን መስጠት፣ የተከበረውን የአላህን ቤት ሐጅ ማድረግ እና የረመዷንን ወር መፆም ናቸው። (ቡኻሪይ በሶሒሑ፥ (8: 4515)፣ በታሪኹል ከቢር፥(4/213) ፣ (8/ 319،322)፣ ሙስሊም፥(16)) ቁርኣናዊ ማስረጃዎቻቸውን ስለ ማእዘናቱ በዝርዝር ስናወራ እንጠቅሳቸዋለን።» የመጀመሪያው ማእዘን፦ 1‐ “ላ ኢላሃ ኢለላህ ሙሐመዱን ረሱሉላህ” ብሎ በአላህ ብቸኛ ተመላኪነትና በነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኝነት መመስከር፤
ይህ የምስክርነት ቃል ማንኛውም ሙስሊም አውቆ ሊተገብረው ግድ የሚል ትርጉም አለው። ትርጉሙን ሳያውቅና የሚያስገድደው ተግባር ላይ ሳይገኝ በምላሱ ብቻ ለሚለው ግን አይጠቅምም።
የ (ላ ኢላሃ ኢለላህ) ትርጉም፦ ከብቸኛው አላህ ውጭ በሰማይም በምድርም በእውነት የሚመለከክ የለም፤ ብቸኛውና ትክክለኛ አምላክ እርሱ ብቻ ሲሆን ከርሱ ውጭ የሚመለክ ሁሉ ከንቱ ነው። "ኢላህ" ማለት አምልኮ የሚደረግለት (የሚመለክ) ማለት ነው። የሚመለከው ነብይ ወይም ወልይ (የፈጣሪ ወዳጅ) ቢሆንም ወይም በሱ አማካኝነት ወደ አላህ ለመቃረብ በሚል ሰበብም እንኳ ቢሆን ከአላህ ውጭ የሚያመልክ ማንም ሰው በአላህ የካደ ሙሽሪክ (አጋሪ) ነው። ምክንያቱም እነዚያ ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የተፋለሟቸው ሙሽሪኮች፤ ነብያቶችንና ወልዮችን (የፈጣሪ ወዳጆችን) ያመለኩ የነበረው እኮ በዚህ ሰበብ ነበር። ይሁን እንጅ ይህ ሙግታቸው ተመላሽ የሆነ ውዳቂ ሰበብ ነበር፤ አምልኮን ከአላህ ውጪ ላለ አካል እያጋሩ ወደ ላቀው አላህ መቃረብና ተወሱል ማድረግ ሊሆን አይችልምና። ይልቅ ወደ አላህ መቃረብ የሚቻለው በስምና ባህርያቶቹ፣ እንደ ሰላት፣ እንደ ምፅዋት፣ አላህን ማውሳት፣ ፆም፣ ጂሃድ፣ ሐጅ፣ ለወላጆች መልካም መዋልን በመሰሉ አላህ ያዘዘባቸው በጎ ስራዎች፤ አንድ በህይወት ያለ ሙእሚን (አማኝ) ለወንድሙ በሚያደርገው ዱዓ ነው። አምልኮ ሲባል ብዙ ዓይነት ነው። ከእነዚህም መካከል፦
1‐ ዱዓእ፦
ዱዓእ ማለት ዝናብ ማውረድን፣ ህመምተኛን መፈወስን፣ ፍጡራን ሊገላግሉን ከማይችሉ ጭንቅ መገላገልን፣ ጀነትን መከጀል፣ ከጀሀነም መዳን፣ ልጆችን፣ ሲሳይንና ደስተኝነትን መከጀል የመሳሰሉ ከአላህ ውጭ ማንም የማይችላቸው ጉዳዮችን በልመና መማፀን ነው።
ይህ ሁሉ ከአላህ እንጅ ከሌላ ከማንም አይከጀልም (ከማንም አይጠየቅም)። እነኝህን መሰል ነገሮች ከፍጡራን ከህያውም ይሁን ከሞተ የከጀለ በርግጥም አምልኮታል። የላቀው አላህ ባርያዎቹ እርሱን ብቻ እንዲማፀኑት ሲያዝ፤ ዱዓእ አምልኮ መሆኑንና ከአላህ ውጭ ላለ አካል አሳልፎ የሰጠ የእሳት ጓድ መሆኑን ሲያሳስብ እንዲህ ብሏል፦
{ጌታችሁም አለ «ለምኑኝ፤ እቀበላችኋለሁ፤ እነዚያ እኔን ከመግገዛት የሚኮሩት ተዋራጆች ኾነው ገሀነምን በእርግጥ ይገባሉ።} [ጋፊር፡ 60] የላቀው አላህ ከሱ ውጭ የሚለመኑት ሁሉ ነብያትና ወልዮች እንኳ ቢሆኑ ለማንም ጥቅምን ሊያመጡም ሆነ ጉዳት ሊያደርሱ አቅም እንደሌላቸው ሲያሳውቅ እንዲህ ብሏል፦ {«እነዚያን ከእርሱ ሌላ (አማልክት) የምትሏቸውን ጥሩ። ከእናንተም ላይ ጉዳትን ማስወገድን (ወደ ሌላ) ማዞርንም አይችሉም» በላቸው፤} [ኢስራእ አንቀፅ ቁጥር 56 እና ከዛ በኋላ ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡ {እነሆ መስጊዶችም የአላህ ብቻ ናቸው። (በውስጣቸው) ከአላህ ጋር አንድንም አትገዙ (ማለትም)።} [አል_ጂን፡ 18] 2‐ እርድ (መስዋእት) ማድረግ፣ ስለትና ወደ አላህ መቃረቢያ ቁርባን ማድረግ: መንኛውም ሰው (ለልቅናው ብሎ) ደምን በማፍሰስ (እርድን በመፈፀም)፣ ወይንም መቃረቢያ ቁርባን በማድረግ ወይም ደግሞ ስለት በማድረግ ወደ አላህ ካልሆነ በቀር ወደማንም ሊቃረብበት አይገባም። ለመቃብርና ለጅን እርድን እንደሚፈፅሙትና መሰሎቻቸው ከአላህ ውጭ ላለ አካል እርድን የሚያቀርብ (የሚሰዋ) በእርግጥም ከአላህ ውጭም አጋርቷል የአላህ እርግማንም ተረጋገጠበት። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {«ስግደቴ፣ መገዛቴም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም ለዓለማት ጌታ ለአላህ ነው» በል።}
[አል_አንዓም 162_163]
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦ «ከአላህ ውጭ ላለ አካል እርድን መስዋእት ያደረገ አላህ ረግሞታል።» [16] [16] ሙስሊም (1978) ዘግቦታል፤ እንዲሁም ነሳኢይ (4422)
ማንም ሰው ፦ “እንዲህ እንዲህ አይነት ነገር ከሆነልኝ የዚህን ያህል ልመፀውት ወይም እንዲህ እንዲህ አይነት ነገር ላደርግ ለእገሌ ስለት አለብኝ” ካለ ይህ ትልቁ ሽርክ ነው የሚሆንበት። ምክንያቱም ለፍጡራን መሳል ስለሆነ ነው። ስለት ደግሞ አምልኮ በመሆኑ ለአላህ ካልሆነ በቀር ለሌላ ለማንም የሚቻል አይደለም። የተደነገገው የስለት አይነት እንዲህ ማለት ነው፦ “እንዲህ እንዲህ አይነት ነገር ከሆነልኝ የዚህን ያህል ልመፀውት፤ ወይም እንዲህ እንዲህ አይነት አምልኮ ላደርግ ለአላህ ስለት አለብኝ”
3‐ ኢስቲቓሣህ፣ ኢስቲዓናህ እና ጥበቃን መሻት [17] [17] ኢስቲዓናህ ሲባል በጥቅሉ እገዛን መከጀልና መማፀን ማለት ሲሆን፤ ኢስቲጋሣህ ደግሞ በጭንቅና በከባድ መከራ ጊዜ የሚደረግ የድረሱልኝ ክጃሎትና ተማፅኖ ነው። ጥበቃን መሻት ሲባል ደግሞ ከለላን መፈለግና ክፋትንና የሚጠላ ነገር በሚመክት አካል መቆራኘት ነው። ኢስቲጋሣም (ይድረሱልኝ ጥሪ) ይሁን ኢስቲዓናህ (እገዛን መሻት)እንዲሁም ጥበቃ መሻት በአላህ ካልሆነ በቀር በማንም አይቻልም። የላቀው አላህ በተከበረው ቁርአን እንዲህ ብሏል፦ {አንተን ብቻ እንግገዛለን፤ አንተንም ብቻ እርዳታን እንለምናለን።} [አል_ፋቲሓ፡ 5] ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡
{በል «በተፈልቃቂው ጎህ ጌታ እጠበቃለሁ።} {«ከፈጠረው ፍጡር ሁሉ ክፋት።} [አል_ፈለቅ፡ 1-2]
መልእክተኛው የአላህ እዝነትና ሰላም በሳቸው ላይ ይሁንና እንዲህ ብለዋል:
«እኔ ለጭንቅ ጊዜ ድረስልኝ ተብዬ አልጠየቅም፤ የጭንቅ ጊዜ ድረስልኝ የሚባለው አላህ ነው።» [18]
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦ "ማንኛውንም ነገር ስትለምን ከአላህ ዘንድ ለምን፤ እርዳታ ከፈለግክም በአላህ ታገዝ።" [19] [18] አሕመድ (5/317/22758)፤ ጦበራኒ (10/246) ሶሒሕ ብለውታል
[19] ቲርሚዚይ (2516)፤ ጦበራኒ (2820) (12989) ቲርሚዚይም ሓዲሡን ሓሰን ሶሒሕ ብለውታል።
ህያው በሆነ ሰው በብርቱ ጭንቅ ጊዜም ይሁን በጥቅሉ በሚችለው ነገር ላይ ብቻ የእርዳታ ጥሪ ሊያደርጉለት የተፈቀደ ነው። ጥበቃ መከጀል ግን በአላህ ካልሆነ በቀር በማንም አይቻልም። የሞተ ወይንም መርዳት ከሚችልበት ሁኔታ የራቀን ግን ነብይም ይሁን ወልይ አልያም መላኢካ እንኳ ቢሆን በከባድ ጭንቅም ይሁን በሌላ የድረስልኝ ጥሪ ሊያደርጉለት በፍፁም አይቻልም፤ ምክንያቱም ማድረግ የሚችልበት አቅም የለውምና።
የሩቅ ምስጢር ከላቀው አላህ በቀር የሚያውቅ የለም። እኔ አውቃለሁ ብሎ የሚሞግት ካለ ደግሞ ከሀዲ ነው፤ ሊያስተባብሉት ይገባዋል። ምናልባት ጠንቁሎ አንዳች ነገር ባጋጣሚ ሆኖ ቢገኝ ራሱ ከአጋጣሚ የዘለለ ሊሆን አይችልም። የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦
"ጠንቋይን ወይም አዋቂ ነኝ ባይን ጎብኝቶ የተናገረውን ያፀደቀ ሰው ወደ ሙሐመድ በወረደው ነገር ክዷል።" [20]
[20] አቡ ዳውድ (3904)፤ ቲርሚዚይ (135)፤ ኢብኑ ማጃህ (639) ዘግበውታል። አልባኒይም በ "ሶሒሑ ተርጊብ ወተርሂብ" (3047) ሶሒሕ ብለውታል።
መመካት፣ ተስፋ ማድረግ[21] እና እውቀት አዘል ፍርሀት: የሰው ልጅ መመካት፣ ተስፋ ማድረግ እና መፍራት ያለበት አላህን ብቻ ነው።
[21]ተወኩል ሲባል በሚመኩበት አካል ላይ ሙሉ እምነትን አሳድሮ በርሱ ላይ መደገፍ ነው። ተስፋ መጣል ሲባል ደግሞ የሚፈለግ ነገር ወደፊት እንደሚከሰት በማሰብ የልቦና መንጠልጠሉ ነው።
እጅግ ከሚያሳዝኑ አውነታዎች መካከል ብዙ ሰዎች ራሳቸውን ወደ እስልምና የሚያስጠጉ ሆነው በአላህ የሚያጋሩ መኖራቸው ነው። በህይወት ያሉ የሚያከብሯቸውን ሰዎች እና የቀብር ጓዶችን በዱዓ የሚመፀኗቸው አሉ፤ በቀብራቸው ዙሪያ ጠዋፍ ያደርጋሉ፤ ጉዳያቸውን እነሱ እንዲፈፅሙላቸው ይከጅላሉ፤ እነዚህ ድርጊቶች ግን አምልኮን ከአላህ ውጭ ላለ አካል አሳልፎ መስጠት በመሆናቸው ድርጊት ፈፃሚው ሙስሊም ነኝ ብሎ ቢሞግት፣ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ ሙሓመዱን ረሱሉሏህ” ቢልም፣ ቢሰግድ፣ ቢፆም፣ ሐጅ ቢያደርግ እንኳ ሙስሊም እንዳይሆን የሚያደርጉት ድርጊቶች ናቸው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ብታጋራ ሥራህ በእርግጥ ይታበሳል። በእርግጥም ከከሓዲዎቹ ትኾናለህ ማለት ወደ አንተም ወደእነዚያም ካንተ በፊት ወደነበሩት በእርግጥ ተወርዷል።} [አዝ_ዙመር፡ 65] ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡ {« እነሆ በኣላሀ የሚያጋራ ሰው አላህ በርሱ ገነትን በእርግጥ እርም አደረገ። “መኖርያቸውን እሳት ናት... በዳዮች ምንም ረዳቶች የላቸውም”::»}
[አል ማእዳህ:72] የላቀው አላህ መልእክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ህዝባቸውን እንዲህ እንዲሉ አዟል፦
{«እኔ አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው ማለት ወደኔ የሚወረድልኝ ቢጤያችሁ ሰው ብቻ ነኝ። የጌታውንም መገናኘት የሚፈልግ ሰው፤ መልካም ሥራን ይሥራ። በጌታውም መገዛት አንድንም አያጋራ» በላቸው።}
[አል-ከህፍ: 110]
እነዚህን አላዋቂዎች ያጃጃሏቸው ትንሽ ቅርንጫፋዊ እውቀትን ይዘው የዲኑ መሰረት የሆነውን ተውሒድን የማያውቁ ጠማሞችና ክፉ አዋቂዎች ናቸው። በመሆኑም በሸፋዓህ እና በተወሱል ስም እውነታውን ባለማወቃቸው ሰዎችን ወደ ሽርክ የሚጣሩ ሆኑ። ለዚህም ድሮም ዘንድሮም እንደ ማስረጃ የሚያቀርቡት በተዛባ መልኩ የተረዷቸውን ቁርአናዊና ሐዲሣዊ ጥቅሶችን እና በነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ላይ የተቀጠፉ ሐዲሦችን፣ ሸይጧን የሚተርክላቸው ተረት ተረቶችና ቅዠቶች እና መሰል እንደ ቀደምቶቹ ሙሽሪኮች ሸይጧንንና ስሜታቸውን በመከተል፣ ወላጆቻቸውንና አያቶቻቸውን በጭፍን በመከተል ከአላህ ውጭ ያላቸውን አምልኮ የሚያጠነክሩባቸው ኪታቦቻቸውን የሞሉባቸው ጥመቶች ናቸው።
{… ወደርሱም መቃረቢያን (መልካም ሥራን) ፈልጉ፡፡… } በሚለው የቁርኣን አንቀፅ የታዘዝነው መቃረቢያም: አላህን በብቸኝነት መገዛት፣ ሶላት፣ ምፅዋት፣ ፆም፣ ሐጅ ማድረግ፣ ጂሀድ፣ በመልካም ማዘዝና ከመጥፎ መከልከል፣ ዝምድናን መቀጠል እና መሰል በጎ ስራዎችን በመስራት ወደ አላህ እንድንቃረብ ነው። ሙታንን መለመንና በከባድ ጭንቅ ጊዜ ድረሱልኝ ብሎ መማፀን ግን እነሱን ከአላህ ውጭ አምላክ አድርጎ መያዝ ነው።
እንዲሁም ሸፋዓ እንዲያደርጉ አላህ የሚፈቅድላቸው ሙስሊሞች፣ ነብያቶችና ወልዮች የሚያማልዱ መሆናቻው እውነት መሆኗንም እንመሰክራለን ነገር ግን የምትፈለገው ከሙታኖች አይደለም። ምክንያቱም የአላህ ሐቅ በመሆኗ ከላቀው አላህ ፈቃድ በኃላ ብቻ ነው የምትገኘው ተውሒዱን ያሳመረ አማኝ እንዲህ በማለት ሊፈልጋት ይገባል: “አላህ ሆይ! እገሌን ደጋግ ባሮችህንም ለኔ ሸፋዓ አድርግልኝ” በማለት ሸፋዓውን ከአላህ ይለምናል እንጅ “እገሌ ሸፋዓየ ሁንልኝ” ብሎ ሊጠይቀው አይቻልም። ምክንያቱም ሟች በመሆኑ ነው፤ ከሟች ደሞ መቼም ምንም ነገር አይከጀልም። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {«ምልጃ መላውም የአላህ ብቻ ነው፡፡ የሰማያትና የምድር ሥልጣን የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ከዚያም ወደእርሱ ትመለሳላችሁ» በላቸው፡፡} [አዝ_ዙመር፡ 44]
እስልምናን የሚቃረኑ ከሆኑ በእስልምናም ከተከለከሉ እና የአላህ መልዕክተኛም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በቡኻሪይና በሙስሊም እንዲሁም በሱነን ኪታቦችም ሶሒሕ በሆኑ ሐዲሦች ካስጠነቀቁን ቢድዓዎች መካከል የቀብር ቦታ ላይ መስገጃ ማድረግ፣ መብራት ማብራት፣ በላዩ ላይ መገንባት፣ ጀሶ መቀባትና መፃፍ፣ በላዩ ላይ መከለል፣ በመቃብር ውስጥ መስገድ ይገኙበታል፤ እነዚህ ሁሉ የተከበሩት የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የከለከሏቸው ነገራት ናቸው። ምክንያቱም የቀብሩን ባለቤት ወደ ማምለክ ከሚያዳርሱ ታላላቅ ምክንያቶች መካከል ነውና።
በዚህም መሰረት በብዙ ሀገራት የሚገኙ አላዋቂዎች በአንዳንድ ቀብሮች በነ አል‐በደዊይ፣ በነ ሰይዳህ ዘይነብ መቃብር ላይ በግብፅ፤ እንዲሁም በነ ዓብደልቃድር ጀይላኒይ በዒራቅ፤ እንዲሁም ወደ ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ቤተሰቦች እየተባለ በሚያሳብቡት በዒራቅና በነጅፍ ባሉ መቃብሮች፤ እንዲሁም በሌሎች ብዙ ሀገሮችም እንደሚደረገው: ጠዋፍ ማድረግ፣ ቀብር ውስጥ ያለው አካል ጉዳይን እንዲያሳካ መማፀን፣ የቀብሩ ባለቤት ሊጠቅምና ሊጎዳ ይችላል በሎ ማመንና የመሳሰሉት ድርጊቶች ሁሉ በአላህ ማጋራት (ሽርክ) መሆኑን እንረዳለን።
እነዚህ ሰዎችም ምንም እንኳ ቢሰግዱ፣ ቢፆሙ፣ በተከበረው የአላህ ቤት ሐጅ ቢያደርጉ እንኳ በዚሁ ድርጊታቸው አማካኝነት በአላህ ያጋሩና መንገድ የሳቱ መሆናቸው ግልፅ ይሆናል። በአንደበታቸው “ላ ኢላሃ ኢለሏህ ሙሐመዱን ረሱሉሏህ” ቢሉ እንኳ አንድ ሰው ላ ኢላሃ ኢለሏህ ሙሓመዱን ረሱሉሏህ የሚለውን ቀደም ብለን ባሳለፍነው ማብራርያ መሰረት አውቆ እስካልተገበረው ድረስ በቃሉ በማለቱ ብቻ በአላህ ብቸኝነት ያረጋገጠ አያደርገውም። ይህ ሰው ከእስልምና ውጭ በሆነ ሃይማኖት የነበረ ከሆነ ግን ቃሉን ባለበት ጊዜ ወደ እስልምና የገባ ሲሆን ከቃሉ ጋር የሚጋጭ እንደነዚህ አላዋቂዎች በሽርክ ላይ መዝለቅ፣ ወይም ከተብራራለት በኃላ ከእስልምና መመርያዎች አንዳች ነገርን ማውገዝ ወይም ደግሞ ከእስልምና ጋር በሚጣረስ ሌላ ሀይማኖት ማመን መሰል ነገር እስካልተገኘበት ድረስ ሙስሊም እንደሆነ ነው።
ነብያቶችና ወልዮችም ቢሆኑ እነሱን ከሚማፀኗቸውና ድረሱልን እያሉ ከሚጣሯቸው ሁሉ የተጥራሩ ናቸው። ምክንያቱም የላቀው አላህ መልዕክተኞቹን የላከው ሰዎች እሱን ብቻ እንዲያመልኩትና ከሱ ውጭ ነብይም ይሁን ወልይ ማንንም ከማምለክ እንዲታቀቡ ነውና።
የአላህ ወዳጆች (ወልዮች) ይበልጥ ተውሒድ ላይ ያሉና ይበልጥ ለአላህ ታዛዦች፣ የመልዕክተኛውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ይበልጥ ተከታይ እነሱ ናቸው። ከነሱ መካከል በዒልሙ እና በትግሉ ታዋቂ የሆነ አለ፤ ከነሱ መካከል የማይታወቅም አለ። ከነሱ መካከል ታዋቂ የሆኑትም ሰዎች ፍፁም አድርገው እንዲያይዋቸው አይፈልጉም። በትክክል ወልይ ከሆኑ ራሳቸውን እንደወልይ አያዩም፤ ይልቅ ብዙ ያጎደሉት ነገር እንዳለ ነው የሚሰማቸው። በአላህ መልዕክተኛ ፈለግ ካልሆነ በቀር የተለየ አለባበስም ሆነ የተለየ አኳኃን የላቸውም። ማንኛውም በአላህ ብቸኝነት ያረጋገጠና የአላህ መልዕክተኛን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በሚገባ የሚከተል ሁሉ ባለው ጥሩነትና ታዛዥነት ልክ ወልይነት አለው። በዚህም መሰረት የአላህ ወዳጆች (ወልዮች) ነን ብለው የሚሞግቱ፤ ሰዎች ፍፁም አድርገው እንዲያይዋቸውም የሚጥሩና ከፍ ከፍ እንዲያደርጓቸውም የተለየ አለባበስ የሚለብሱ አንዳንድ ሰዎች የአላህ ወዳጆች (ወልዮች) መሆናቸው ቀርቶ ቀጣፊዎች መሆናቸው ግልፅ ይሆናል።
የአላህ መልዕክተኛን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሆነ የአላህ ወዳጅ (ወልይን) መውደድ እነሱን በማምለክ አይደለም የሚገለፀው። ምክንያቱም እነሱን ማምለክ ከእነርሱ ጋ ጠላትነትን መመስረት ነዋ። ይልቅ እነሱን መውደድ የሚገለፀው በእነሱ (መልካም ጎዳና) በመመራትና ፈለጋቸውን በመከተል ነው። ትክክለኛ ሙስሊም ነብያቶችንና ወልዮችን ይወዳቸዋል እንጅ አያመልካቸውም። እኛም የአላህ መልዕክተኛን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከራሳችን፣ ከቤተሰባችን፣ ከልጆቻችንም ይሁን ከመላው የሰው ልጅ ሁሉም በላይ መውደድ ግዴታ መሆኑንም እናምናለን። *** የምትድነዋ ቡድን ሙስሊሞች በአሁኑ ጊዜ ምንም እንኳ በቁጥር ብዙ ቢሆኑም በተጨባጩ ግን ጥቂት ናቸው። ወደ እስልምና ራሳቸውን የሚያስጠጉ አንጃዎችም እስከ 73 አንጃ ድረስ የሚዘልቁ ብዙ ናቸው። በነፍስ ወከፍ ደረጃ አንድ መቶ ሚሊዮንና ከዛም በላይ ቁጥር ያላቸው[23] ሲሆን ከነዚህ መካከል ትክክለኛዋ እስልምና ግን አንዲት ነች። ይህችም የአላህን ብቸኛ አምላክነት ተረድታ በእምነትም ሆነ በበጎ ስራ የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የሶሓቦች ጎዳና የምትጓዝ ነች። ልክ የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በተከታዩ ንግግራቸው እንዳሳወቁን፦ "አይሁዶች ለሰባ አንድ አንጃዎች ተከፋፍለዋል፤ ክርስቲያኖችም ለሰባ ሁለት አንጃዎች ተከፋፍለዋል፤ የእኔ ህዝብም ለሰባ ሦስት ክፍሎች ይከፈላሉ። ከአንዲቷ በቀር ሁሉም የእሳት ናቸው።"
ሰሓቦችም "የአላህ መልዕክተኛ ሆይ! የትኛዋ ናት (ነጃ ምትወጣው)?" በማለት ጠየቁ
"ዛሬ እኔና ባልደረቦቼ ባለንበት አቋም የሆኑት ናቸው።" [24]
[23] ኪታቡ በሚፃፍበት ጊዜ (1395ሒ / 1975 እ. ኤ. አ) ይፋ በነበረው ቆጠራ መሰረት [24] አቡ ዳውድ (3842)፤ ኢብኑ ማጃህ (3226)፤ አልባኒይም በ "ሶሒሑል ጃሚዕ" (1082) እና በ "ሲልሲለቱ ሶሒሓ" (203) ሶሒሕ ብለውታል
ያ የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እና ሶሓቦቻቸው የነበሩበት ጎዳና የ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ ሙሓመዱን ረሱሉሏህ”ን መልእክት በሚገባ በመረዳት አላህን ብቻ በመለመን፣ ስለትም፣ እርድም ለአላህ ብቻ በማድረግ፤ ለከባዱ ለቀላሉም መከራ እሱን ብቻ በመማፀን፤ መጥቀምም ሆነ መጉዳት የሚችለው አላህ ብቻ መሆኑን በማመን፤ አምስቱን የእስልምና ማእዘናትን ለርሱ ብቻ ጥርት አድርጉ በመወጣት፤ በመላእክቶቹ፣ በመጽሐፍቶቹ፣ በመልዕክተኞቹ፣ ከሞት በኃላ ባለው በመቀስቀስ፣ በስራ መተሳሰብ፣ በጀነት፣ በጀሀነም፣ በጎውም መጥፎውም ሁሉም ከላቀው አላህ መሆኑን በቀደር በማመንና ወደ ተግባር በመቀየር ነው።
በማንኛውም መስክ ላይ ቁርአንንና ሐዲሥን ፈራጅ አደርጎ ፍርዳቸውንም ወዶ መቀበል፤ የአላህ ወዳጆችን መውደድ፤ የአላህን ጠላቶች ጠላት አድርጎ መያዝ፤ ወደ አላህ ጥሪ ማድረግ፣ በመንገዱም ላይ ተገቢውን ትግል እያደረጉ በዚህም ላይ አንድ በመሆን፤ የሙስሊሞች የጉዳይ ኃላፊን (መሪን) በመልካም እስካዘዘ ድረስ በመስማትና በመታዘዝ፤ የትም ቢሆኑ እውነት በመናገር፤ የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ባለቤቶችንና ቤተሰቦችን በመውደድና በመወዳጀት፤ የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ባልደረቦችንም በመውደድ፣ ባላቸው ደረጃ ልክ ቅድሚያ በመስጠት፣ አላህ መልካም ስራቸውን እንዲቀበላቸው ለሁሉም (አላህ መልካም ሥራቸውን ለሁልም ይውደድላቸው) ዱዓእ በማድረግ፣ በመካከላቸው ስለተከሰቱ ነገራቶች ራስን በማቀብ፣[25] ሙናፊቆች አንዳንዶቹን ስለሚተቹባቸው ነገር ባለማመን ‐በእርግጥ በትችታቸው የሚፈልጉበት ሙስሊሞችን መለያየት ነው፤ አንዳንድ ሊቃውንቶቻቸውና የታሪክ ጸሐፍቶቻቸው ተታልለው በቅን ልቦና በመጽሐፋቻቸው ልክ እንደሆነ ገልጸውታል ይህ ግን ስህተት ነው።
[25] ማለትም በሶሓቦች መካከል በተነሳ ውዝግብ መሰረት ከመተችትና ከማጣጣል መታቀብ ለማለት ነው።
እነዚያ ራሳቸውን የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ቤተሰቦች እንደሆኑ የሚሞግቱና “ሳዳት” እንደሆኑ የሚቆጥሩ በትክክል የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ዘር መሆናቸውን ሊያረጋግጡ ይገባል። ምክንያቱም አላህ ከወላጁ ውጭ ወደ ሆነ ሌላ አካል ራሱን ያስጠጋን አላህ ረግሞታልና። በትክክል ዘራቸውን ካረጋገጡ የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ጎዳና ተከታዮች ሊሆኑም ይገባቸዋል። ተውሒድን ለአላህ ጥርት በማድረግ፣ ጉልበታቸውንና እግራቸውን እየሳሙ የሰዎች ወደነሱ መዘንበልን ወዶ ባለመቀበል አመፀኝነትን ትቶ ራሳቸውን ከሌሎች ሙስሊሞች ባአባበስም እንኳ መለየት የለባቸውም። ምክንያቱም ያ ሁሉ መልዕክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የነበሩበትን የሚጣረስ በመሆኑ የአላህ መልዕክተኛም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ራሳቸውን ነጻ ያደረጉበት ነውና። አላህ ዘንድ እጅግ የተከበረውም እጅግ አላህን የሚፈራው ነው።
ምስጋና ለአላህ ይገባው, የዓለማት ጌታ ለሆነው, እና እዝነትና ሰላም በነቢያችን ሙሐመድ ላይ እና ቤተሰቡ እና በባልደረቦቹ ላይ ይውረድ
***
ፍርድና ድንጋጌ ማውጣት የአላህ ብቻ ነው መብቱ፤ ይህ ድንጋጌ ባለበትም ሁሉ ፍትህ፣ ርህራሄና በላጭነትም አለ።
ልናምንበትና ተግባራዊ ልናደርገውም ግድ ከሚለን የ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ” ትርጉሞች መካከል ፍርድና ድንጋጌ የአላህ ብቻ መብቶች መሆናቸው ማመን ነው። በመሆኑም ማንኛውም ሰው በየትኛውም ጉዳይ ላይ የአላህን መመርያ የሚቃረን ህግ ሊያወጣ አይፈቀድለትም፤ ለሙስሊምም አላህ ባወረደው ፍርድ ካልሆነ በቀር ሊፈርድ ወይም ከአላህ መመርያ ጋ የሚጋጭ የትኛውንም መመርያም ወዶ ሊቀበልም አይፈቀድለትም። አላህ ሐራም ያደረገውን ሐላል ሊያደርግም ሆነ አላህ ሓላል ያደረገውን ሐራም ሊያደርግም አይፈቀድለትም። ይህንንም ሆን ብሎ የተቃረነ ወይም የወደደ በአላህ የካደ ካፊር ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{አላህም ባወረደው ያልፈረደ ሰው እነዚያ ከሓዲዎቹ እነርሱ ናቸው።} [አል_ማኢዳህ፡ 44] *** አላህ መልዕክተኞቹን የላከበት ኃላፊነት ኃላፊነታቸው የሰው ልጆችን የተውሒድ ቃል ወደ ሆነችው ወደ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ” ጥሪ እንዲያደርጉ እና በመልእክቷም እንዲሰሩበት ነው። እርሱም አላህን ብቻ እንዲያመልኩና ፍጡራንንና መመሪያቸውን ከማምለክ ወጥተው ባላንጣ ሳያደርጉ ለፈጣሪ እና ለመመሪያው ተገዥ እንዲሆኑ ነው። በማስተንተንና ከጭፍን ተከታይነት በመራቅ ታላቁን ቁርአን አስተውሎ ማንበብ የቻለ ይህ ያብራራነው ሙሉ በሙሉ እውነት መሆኑን ይረዳል። አላህም በeርሱና በሰው ልጆች መካከል ያለውን እንዲሁም ፍጡራንም ያላቸውን ቁርኝት ወሰን እንዳበጀለት ይረዳል። አማኝ ከሆነ ባርያው ጋ ያለውንም ቁርኝት በሁሉም ዓይነት የአምልኮ አይነቶች እርሱን እንዲያመልከው በማድረግ አስተሳስሯል፤ በዚህም መሰረት ከርሱ ውጭ ላለ አካል ምንም አይነት የአምልኮ ማጋራትን ላያደርግ ወሰነ። ከነብያቶችና ደጋግ ባርያዎቹ ጋ ያለውን ቁርኝት ደግሞ እነርሱን በመውደድና እነርሱንም በመከተል ያደረገ ሲሆን ያም ጥራት ይገባውና የላቀውን አላህ ከመውደድ በኃላ ተከታይ የሆነ ውዴታ ነው። ከከሃዲያን ጋ ያለውን ቁርኝት ደግሞ እነርሱን በመጥላት አደረገ። አላህ ይጠላቸዋልና። ይህ ከመሆኑም ጋር ግን ፊትናህ (ሽርክ) እስክትጠፋና ሀይማኖት ሁሉ ለአላህ እስኪሆን ድረስ ወደ ቀናው ጎዳና ይመሩ ዘንድ እስልምና ሊብራራላቸውና ወደ እስልምናም ጥሪ ሊደረግላቸው እስልምናን መቀበልንና ለአላህ ህግ ማጎብደድን እንቢ ካሉ ደግሞ ሙስሊሞች ሊፋለሟቸው ተገቢ የሆነን ቁርኝት አደረገ። እነዚህን የተውሒድ ቃል የሆነችውን የ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ” ትርጉሞችን ማንኛውም ሙስሊም በትክክል ሙስሊም ሊሆን ዘንድ በተገቢው መልኩ ሊረዳቸውና በተግባርም ላይ ሊያውላቸው ይገባል።
ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸውን መመስከር ትርጓሜ
ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸውን መመስከር ሲባል ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ወደ ሰው ልጆች ሁሉ የተላኩ የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸው፤ አላህን የሚያመልኩ እንጂ የሚመለኩ አለመሆናቸው፤ የሚታዘዟቸውና የሚከተሏቸው እንጂ የማይስተባበሉ እውነት ተናጋሪ መሆናቸውን መመስከር ማለት ነው። እንዲሁም አላህ ባዘዛቸው አምልኮዎችም ይሁን በተለያየ መስክ ባሉ ፍርድና ድንጋጌዎች፤ አንድን ነገር ሐላልና ሐራም በማድረግም በዚሁ የተከበሩ የአላህ መልዕክተኛ ፈለግ ካልሆነ በቀር መመርያ እንደሌለ ልታውቅና ልትመሰክር ነው። ምክንያቱም መመርያውን ሊያደርሱ ከአላህ የተላኩ መልዕክተኛ ናቸውና፤ አንድ ሙስሊም በነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ጎዳና የመጣን መመርያ ካልሆነ በቀር የትኛውንም ድንጋጌ አይቀበልም። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{መልክተኛውም የሰጣችሁን (ማንኛውንም) ነገር ያዙት፡፡ ከእርሱም የከለከላችሁን ነገር ተከልከሉ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና፡፡}
[አል ሀሽር 7] ከፍ ያለው አላህ እንዲህ ይለናል፡
{በጌታህም እምላለሁ በመካከላቸው በተከራከሩበት ፍርድ እስከሚያስፈርዱህ ከዚያም ከፈረድከው ነገር በነፍሶቻቸው ውስጥ ጭንቀትን እስከማያገኙና ፍጹም መታዘዝንም እስከሚታዘዙ ድረስ አያምኑም፤ (ምእመን አይኾኑም)፡፡}
[አን-ኒሳእ: 65]
የሁለቱ አንቀፆች መልእክት
1‐ አላህ በመጀመርያው አንቀፅ ሙስሊሞች መልዕክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ባዘዛቸው ነገር ሁሉ እንዲታዘዙት፤ ከከለከላቸው ነገርም ሁሉ እንዲከለከሉ እያዘዘ ነው። ምክንያቱ መልዕክተኛው የሚያዘው የአላህን ትእዛዝ የሚከለክለውም የአላህን ክልከላ በመሆኑ ነው። 2‐ በሁለተኛው አንቀፅ ደግሞ ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ ፍፁም በሆነው ማንነቱ እየማለ አንድ ሰው በአላህም ሆነ በመልዕክተኛው ያለው እምነት ትክክል መሆን የሚችለው በግለሰቡና በሌላ አካል[26] ምንም በተፈጠረ ቁጥር ፈራጁን የአላህ መልዕክተኛ እያደረገ በተሰጠው ፍርድም ወዶ በመቀበል በመልዕክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሲማረክ ብቻ እንደሆነ ነው። "የኛ ጉዳይ ወይም ትዕዛዝ የሌለበት ነገር (ሃያምኖታዊ ተግባር) የሰራ ሰዉ ወደርሱ ተመላሽ ነዉ።" [26] በርሱና በሌላ አካል አለመግባባት ሲከሰት ለማለት ነው።
[27] ቡኻሪይ (2697)፤ ሙስሊም (1718)፤ ቃሉ የቡኻሪይ ዘገባ ላይ ያለው ነው።
***
ጥሪ
አንተ አስተዋይ ልቦና የተሰጠህ ሰው ሆይ! የ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ ሙሐመዱ ረሱሉሏህ” ትርጉሟን እስከተረዳህና ይህች የምስክርነት ቃልም የእስልምና ቁልፍ እና የተመሰረተበትም ምሶሶ መሆኗን እስካወቅክ ድረስ ጥርት ባለ ቅን ልቦና እንዲህ በል፦ “አሽሀዱ አን ላ ኢላሃ ኢለሏህ ወአሽሃዱ አነ ሙሐመደን ረሱሉሏህ” (ከአላህ በቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ አለመኖሩን እመሰክራለሁ ሙሐመድም የአላህ መልዕክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ) በልና ከዚያም በምስክርነት ቃሏ ትርጉም ተግባር ላይ ተገኝ። በዱንያም በአኼራም ደስተኝነትን ታጎናፅፍሀለች ከሞት በኃላም በእሳት ከመቀጣት ታድንሀለች።
“ላ ኢላሃ አለሏህ ሙሐመዱን ረሱሉሏህ” ብሎ መመስከር ግዴታ ከሚያደርጋቸው እውነታዎች መካከል በተቀሩት የእስልምና ማእዘናት መተግበር ይገኝበታል። ምክንያቱም አላህ እነዚህን የእስልምና ማእዘናት የደነገጋቸው እነርሱን በእውነትና ጥርት ባለ መልኩ ለእርሱ ብቻ ብለው በመፈፀም እንዲያመልኩት ነው። ሸሪዓዊ በሆነ ምክንያት ካልሆነ በቀር ከነዚህ ማእዘናት አንዱን እንኳ የተወ የ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ” ትርጉም ላይ ክፍተት ፈጥሯል። ምስክርነቱም ትክክል አይደለም።
***
ከእስልምና ማእዘናት ሁለተኛው ማእዘን (ሶላት)
አንተ አስተዋይ ልቦና ያለህ ሰው ሆይ! ከእስልምና ማእዘናት ሁለተኛው ማእዘን ሶላት ነው። ይሀውም በቀንና በሌሊት የሚፈፀሙ አምስቱ የሶላት ወቅቶች ናቸው። እነዚህንም አላህ የደነገጋቸው በእርሱና በአላህ መካከል ቁርኝት የሚፈጥሩ፣ አላህን የሚያዋይበትና የሚማጸንበት ድልድዮችና ሙስሊምንም ከፀያፍና ከብልግና ከልካዮች ይሆኑለት ዘንድ ነው። በዚህም በዱኒያም በአኼራም ደስተኛ የሚሆንበት አካላዊና ስነልቦናዊ እርካታን ይጎናፀፋል።
አላህ ለሶላት አካላዊም፣ የልብስም ይሁን የሚሰገድበት ቦታ ንፅህናን ደንግጓል። በመሆኑም ሙስሊም ንፁህ በሆነ ውኃ ለምሳሌ ሽንትንና ሰገራን ከመሰሉ ግኡዝ ቆሻሾች የሚፀዳ ሲሆን በተጨማሪም ልቡን ከምናባዊ ቆሻሾችም ያፀዳል።
ሶላት የሀይማኖት ምሶሶው ነች። ከሁለቱ የምስክርነት ቃሎች በኃላ እጅግ አሳሳቢዋ ማእዘንም እሷው ነች። በየትኛውም ሙስሊም የሆነ ግለሰብ እድሜው ከደረሰበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ ተጠባብቆ ሊሰግዳት ግዴታ ነች። (የቤተሰብ ኃላፊም) ቤተሰቦቹንና ልጆቹንም እንዲለማመዱ እድሜያቸው ሰባት አመት ከሞላበት ጊዜ ጀምሮ ሊያዛቸው ግዴታ ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ሶላት በምእምናን ላይ በጊዜያት የተወሰነች ግዴታ ናትና።} [አን-ኒሳእ: 103] ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡ {አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ አጥሪዎች፣ ቀጥተኞች ኾነው ሊግገዙት፣ ሶላትንም አስተካክለው ሊሰግዱ ዘካንም ሊሰጡ እንጅ ያልታዘዙ ሲኾኑ (ተለያዩ)፡፡ ይህም የቀጥተኛይቱ (ሃይማኖት) ድንጋጌ ነው፡፡} [አል_በይናህ፡ 5] የአንቀፁ ጥቅል መልዕክት: 1‐ የላቀው አሏህ በመጀመርያው አንቀፅ ሶላት በሙእሚኖች ላይ ቁርጥ ያለ ግዴታ መሆኑን እና ሁሉም ደግሞ በተገደበላት ጊዜ ሊወጧት የሚገባቸው መሆኗን አሳወቀ። 2‐ በሁለተኛው አንቀፅ ደግሞ ልእለ ኃያሉ አላህ የሰው ልጆች ያለባቸው ታላቅ ግዳጅና የተፈጠሩበትም አላማ እርሱን በብቸኝነት እንዲገዙት፣ በርሱም ምንንም ሳያጋሩ ጥርት አድርገው ሊያመልኩት፣ ሶላታቸውንም በሚገባ ሊሰግዱና ዘካንም ለሚገባው አካል ሊሰጡ መሆኑን አሳወቀ። ሶላት በሙስሊም ላይ በየትኛውም ሆኔታ ላይ ሆኖ በስጋትና በህመም ላይ እንኳ ሆኖ ሊቀርለት የማይችል ግዴታው ነው። ቆሞ ይሁን፤ ተቀምጦ ወይም ተጋድሞ ብቻ በተቻለው አኳኃን ሆኖ ይስገድ። በአይኑ ወይም በልቦናው በመጠቆም ካልሆነ በቀር በምንም መልኩ መስገድ የማይችል እንኳ ቢሆን እየጠቆመ ይስገድ። ወንድም ይሁን ሴት ሶላትን ከተወ ሙስሊም እንዳልሆነ ነብዩም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ በማለት አሳውቀዋል፦
"በኛና በነሱ መካከል ያለው ቃል ኪዳን ሶላት ነው። ሶላቱን የተወ ሰው እርሱ ካፊር ነው።" [28]
[28] ቲርሚዚይ (2621)፤ ነሳኢይ (463)፤ አሕመድ (5/346) ላይ ዘግበውታል፤ አልባኒይም በ "ሶሒሑል ጃሚዕ" ሶሒሕ ብለውታል
አምስቱ ሶላቶች እነሱም:
የፈጅር (ሱብሒ) ሶላት፣ የዙህር ሶላት፣ የዓስር ሶላት፣ የመግሪብ ሶላት እና የዒሻእ ሶላት ናቸው።
የፈጅር (የሱብሒ) ሶላት ጊዜው በስተምስራቅ በኩል ጎህ ከቀደደበት ጊዜ የሚጀምር ሲሆን ፀሀይዋ በምትወጣበት ጊዜ ያቆማል። ይሁን እንጅ ሶላቱን ወደ ጊዜው ማለቂያ ማዘግየት አይፈቀድም። የዙህር ሶላት ወቅት ፀሀይ ወደ ምዕራብ ዘንበል ካለችበት ጊዜ የሚጀምር ሲሆን የትኛውም ነገር ጥላው የራሱ እኩል እስከሚሆንበት ጊዜ ድረስ ይዘልቃል። የዓሱር ሶላት ወቅት ደግሞ የዙህር ሶላት ወቅት ካለቀበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ጀምበር መጥለቂያ ሰአት ድረስ ነው። ይሁን እንጅ ሶላቱን ወደ ጊዜው ማለቂያ ማዘግየት አይፈቀድም። ይልቅ መሰገድ ያለበት ፀሀይዋ ገና ሞቅ ደመቅ ባለችበት ጊዜ ሊሆን ይገባል። የመግሪብ ሶላት ደግሞ ፀሀይ ከገባችበት ጊዜ ጀምሮ ቀዩ ጎህ መሰል ነገር ሲጠፋ ነው የሚያልቀው። ይሁን እንጅ ሶላቱን ወደ ጊዜው ማለቂያ ማዘግየት አይፈቀድም። ልክ የመግሪብ ሶላት ወቅት እንዳለቀ ወዲያውኑ የዒሻ ሶላት ወቅት ይጀምርና እስከ እኩለ ሌሊት ደረስ ይዘልቃል። ከእኩለ ሌሊት በኃላ ግን መዘግየት የለበትም።
ሙስሊም የትኛውንም የግዴታ ሶላቱን ከተወሰነለት ጊዜ እስኪወጣ ድረስ ያለበቂ ሸሪዓዊ ምክንያት ቢያዘገይ ትልቅ ወንጀልን ፈፅሟልና በድጋሚ እንደዛ ላያደርግ በተውባ (ንስሀ) ወደ አላህ መመለስ አለበት። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ለሚሰግዱ ወዮላቸው} (4)
{ለእነዚያ እነርሱ ከስግደታቸው ዘንጊዎች ለኾኑት፤ (ሰጋጆች)፡፡}
[አል_ማዑን፡ 4_5]
***
የሶላት ህግጋቶች
የመጀመርያው፡ ጠሀራ (ንፅህና)
አንድ ሙስሊም ወደ ሶላት ከመግባቱ በፊት ንፅህናውን ሊጠብቅ ግድ ነው። በመጀመሪያ ሽንት ወይም ሰገራ ወጥቶት ከነበረ መውጫውን ያፀዳል። ከዚያም ውዱእ ያደርጋል።
በልቡ ንጽህናን ያስባል፤ ይሁን እንጅ በአንደበቱ አይናገረውም። ምክንያቱም ሃሳቡን አላህ ያውቀዋልና፤ መልእክተኛውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አልተናገሩም። ከዚያም ቢስሚላህ ብሎ ይጀምራል። ከዚያም ወደ አፍና አፍንጫው ውኃን በመሳብ አፉንም ተግሞጥሙጦ በመትፋት አፍንጫው ውስጥ ያለውንም ውኃ ያስወግዳል። ከዚያም ሙሉ ፊቱን ይታጠባል። ከዚያም እጆቹን ከቀኝ ጀምሮ ሁለቱንም እጆቹን ክንዱን እና ክርኑንም አካቶ ይታጠባል። ከዚያም በሁለት እጆቹ ጭንቅላቱን በሙሉ ያብስና ጆሮውንም ያብሳል። ከዚያም ሁለት እግሮቹን ከቀኙ ጀምሮ ቁርጭምጭሚቱንም አካቶ ያጥባል። በሚገባ ጠሀራ ካደረገ በኃላ ሽንት፣ ሰገራ ወይም ከመቀመጫ የሚወጣ ንፋስ ከወጣው ወይም ደግሞ በእንቅልፍ ወይም በሌላ ምክንያት ራሱን ከሳተ በኃላ መስገድ ከፈለገ ውዱኡ ስለጠፋ በድጋሚ ተገቢውን የንፅህና ስርአት ይደግማል። አንድ ሙስሊም ወንድም ይሁን ሴት በህልም እንኳ ቢሆን የዘር ፈሳሽ በስሜት ወጥቶት ጁኑብ ከሆነ ሁሉንም ሰውነቱን በማጠብ እራሱን ከጀናባ ያጠራል። እንዲሁም ሴት ልጅ ከወር አበባ ወይም ከድህረ ወሊድ ደም ከጠራች በኃላ ሁሉንም ሰውነቷን በማጠብ እራሷን ማጽዳት አለባት። ምክንያቱም የወር አበባ ላይ ያሉ ሴቶች እና ከወሊድ በኋላ ያሉ እመጫት ሴቶች ሶላታቸው ትክክለኛ ስላልሆነ እና እስኪነፁ ድረስ መስገድም ስለማይገደዱ ነው። በወር አበባ እና በድህረ ወሊድ ደም ሳቢያ ያመለጣቸውን ሶላትም አላህ የተወላቸው ሲሆን ነገር ግን ከዛ ውጭ በሆነ ምክንያት ያመለጣቸውን ግን እነሱም እንደ ወንዱ ማካካስ አለባቸው። ውኃ የሌለው ወይንም ውኃን መጠቀሙ የሚጎዳው ከሆነ ለምሳሌ በሽተኛ የሆነ ሰው ራሱን በተየሙም ያጠራል። የተየሙሙ አኳኃኑም፡- በልቡ ራሱን ለማንጻት አስቦ የአላህን ስም በመጥራት በእጆቹ አንድ ጊዜ አፈሩን መታ ያደርግና ፊቱን በእነርሱ ያብሳል ከዚያም የቀኝ እጁን ጀርባ በግራ እጁ ሆድ እና የግራ እጁን ጀርባ ደግሞ በቀኝ እጁ ሆድ የሚያብስ ሲሆን በዚህም ተገቢውን ጣሀራ ያደረገ ይሆናል ማለት ነው። ይህም ውዱእ ማድረግ ፈልጎ ውሃ ሲጠፋ ወይም መጠቀምን ሲፈራ የሚደረግ ነው። ሁለተኛ፡ የሶላት አኳኃኑም፡-
1- የፈጅር ሶላት፡-
ሁለት ረከዓዎች ሲሆን ማንኛውም ሰጋጅ ሙስሊም ወንድም ይሁን ሴት ፊቱን መካ ወደሚገኘው የተከበረው መስጊድ ቂብላ ያቅጣጭና የፈጅርን (የሱብሒ) ሰላትን ለመስገድ በልቡ ያስባል። ሀሳቡንም በአንደበቱ መናገር አይጠበቅበትም። ከዚያም እንዲህ በማለት ተክቢራውን ያደርጋል፡- "አላህ አክበር" ትርጉሙም አላህ ታላቅ ነው ማለት ነው። ከዚያም የመክፈቻውን ዱዓእ (ዱዓኡል ኢስቲፍታሕ) ያደርጋል፤ ከሚደረግባቸው አኳኃኖችም መካከል፡- «ሱብሓነከሏሁም ወቢሓምዲከ ወተባረከ ኢስሙከ ወተዓላ ጀዱከ ወላኢላሀ ገይሩክ» [ትርጉሙም ጥራትና ልቅና ለአንተ ይሁን አምላኬ ሆይ ምስጋናም ለአንተ ይሁን ስምህም የላቀ ነው ግርማህም ከፍ ከፍ ይበል ካንተ በቀርም አምላክ የለም። ማለት ነው] ብሎ «አዑዙ ቢላሂ ሚነ ሸይጧኒ ሯጂም» ካለ በኃላ ፋቲሓን (አልሓምዱን) በሚከተለው መልኩ ይቀራል።
«ቢስሚልላሂ‐ር‐ሯሕማኒ‐ር‐ሯሒም» [ትርጉሙም: በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በሆነው] (1)
«አልሓምዱ ሊልላሂ ረቢል ዓለሚን» (ትርጉሙም: ምስጋና ለዓለማት ጌታ ለአሏህ የተገባው ነው) (2)
«አር‐ሯሕማኒ‐ር‐ሯሒም» (ትርጉሙም: እጅግ በጣም አዛኝ አዛኝ እጅግ በጣም ሩኅሩህ) (3)
«ማሊኪ የውሚ‐ድ‐ዲን» (ትርጉሙም: የፍርዱ ቀን ባለቤት) (4)
«ኢይያከ ነዕቡዱ ወኢይያከ ነሰተዒን» (አንተን ብቻ እንገዛለን አንተንም ብቻ እርዳታን እንለምንሃለን) (5)
"ቀጥተኛውን መንገድ ምራን፡፡"(6)
«ሲሯጦ‐ል‐ለዚነ አንዓምተ ዓለይሂም ቐይሪል መቕዱቢ ዓለይሂም ወለድዷሊን» (ትርጉሙም: የእነዚያ ፀጋህን የዋልክላቸውን ሰዎች መንገድ በነዚያ የተቆጣህባቸውን እና የተሳሳቱትንም አይደሉም። [አል_ፋቲሓ፡ 1_7] ቁርኣንን በተቻለው ልክ በአረብኛ [29] መቅራት መቻል አለበት። ከዚያም እንዲህ ይበል፡- "አሏሁ አክበር!" ብሎ ራሱን እና ጀርባውን በማጎብደድ የእጆቹን መዳፍ በጉልበቱ ላይ ያድርግ። ከዚያም እንዲህ ይበል፡- «ሱብሓነ ረቢየል ዓዚም» "ትርጉሙም፦ ጥራት ይገባው ለታላቁ ጌታዬ" ከዚያም የሚከተለውን እያለ ካጎነበሰበት ቀና ይላል፡- «ሰሚዐሏሁ ሊመን ሓሚደህ» "ትርጉሙም፦ "አላህ የሚያመሰግኑትን ይሰማል" ከዚያም ተስተካክሎ እንደቆመ እንዲህ ይበል: «ረበና ወለከል ሓምድ» “ጌታችን ሆይ! ምስጋና ላንተ ይሁን።” ከዚያም እንዲህ ይላል: "አሏሁ አክበር" ብሎ በሁለቱ እግሮቹ ጣቶች፣ በጉልበቶቹ፣ በእጆቹ፣ በግንባሩ እና በአፍንጫው ጫፍ መሬት ላይ ተጎንብሶ ሱጁድ ላይ ሳለ እንዲህ ይላል። «ሱብሓነ ረቢየል አዕላ» “ጥራት ይገባው ለላቀው ጌታዬ” ከዚያም ተቀምጦ እንዲህ ይበል: «አሏሁ አክበር» "አላህ ታላቅ ነው" ከዛም ተቀምጦ እንዲህ ይላል: «ረቢ‐ግፊር ሊ» “ጌታ ሆይ፣ ይቅር በለኝ” ብሎ እንዲህም ይላል፡ «አሏሁ አክበር» "አላህ ታላቅ ነው" ይልና እንደገና በምድር ላይ ሱጁድ አድርጎ እንዲህ ይላል፡ «ሱብሓነ ረቢየል አዕላ» “ክብር ለጌታዬ ይሁን።” ከዚያም ተነሥቶ እንዲህ ይበል: «አሏሁ አክበር» "አላህ ታላቅ ነው" ከዚያም በድጋሚ አል-ፋቲሓን ያነባል (ይቀራል) ይህም «አልሓምዱ ሊልላሂ ረቢል ዓለሚን» እስከ መጨረሻው ድረስ ልክ የመጀመሪያው ረከዓ ላይ እንዳለው ይላል። ከዚያም «አሏሁ አክበር» ይልና ሩኩዕ ያደርጋል፣ ከዚያም ቀና ይላል፣ ከዚያም ሱጁድ ያደርጋል፣ ከዚያም ይቀመጣል፣ ከዚያም እንደገና ይሰግዳል፣ ሁሉንም በቦታው ላይ ልክ መጀመሪያ እንዳለው እያለ ይሰግዳል። [29] በዓረብኛው ይቅራ ያልንበት ምክንያትም ቁርኣን ከአረብኛ ውጭ በሌላ ቋንቋ ቢቀራ ቁርኣን አይሆንምና ነው። ስለዚህም እኮ ነው ቁርኣን መልእክቱ እንጅ ቃላቶቹ የማይተረጎሙት። ምክንያቱም ፊደሎቹ እና ቃላቶቹ ቢተረጎሙ ቋንቋው ምጥቀቱ እና ተአምሯዊነቱ ጠፍቶ አንዳንድ ፊደሎቹም ጠፍተው (አላህ የገለፀው አይነት) የአረብኛው ቁርኣን አይሆንም። «አት‐ተሕያቱ ሊላህ ወሶለዋቱ ወጦይባቱ አሰላሙ ዓለይከ አዩሃ‐ን‐ነቢዩ ወረሕመቱሏሂ ወበረካቱሁ አሰላሙ ዓለይና ወዓላ ዒባዲላሂ አስ‐ሷሊሒን አሽሀዱ አን ላ ኢላሃ ኢለሏህ ወአሽሃዱ አነ ሙሓመደን ዓብዱሁ ወረሱሉህ አሏሁመ ሶሊ ዓላ ሙሐመድ ወዓላ አሊ ሙሐመድ ከማ ሶለይተ ዓላ ኢብራሂም ወዓላ አሊ ኢብራሂመ ኢነከ ሓሚዱን መጂድ አሏሁመ ባሪክ ዓላ ሙሐመድ ወዓላ አሊ ሙሐመድ ከማ ባረክተ ዓላ ኢብራሂም ወዓላ አሊ ኢብራሂመ ኢነከ ሓሚዱን መጂድ» “ትርጉሙም:- ልቅና ለአላህ የተገባ ነው፤ አንተ ነብይ ሆይ! (የአላህ) ሶለዋትና መልካም ሁሉ እንዲሁም ሰላም፣ ርህራሄና በረከቱ በአንተ ላይ ይሁን፤ የአላህ ሰላም እና እዝነት፣ በኛ እና በአላህ ጻድቃን ባሮች ላይ ይሁን፤ ከአላህ በስተቀር ሌላ አምላክ እንደሌለም እመሰክራለሁ። መሐመድ ባሪያውና መልእክተኛው መሆናቸውንም እመሰክራለሁ። አላህ ሆይ! በሙሐመድም በመሐመድ ቤተሰብም ላይ ልክ በኢብራሂምና በኢብራሂም ቤተሰቦች እንዳደረግከው ሶለዋት በነሱም ላይ አድርግ። አንተ የተመሰገንህ የተከበርክ ነህና። አላህ ሆይ! መሐመድንና የመሐመድን ቤተሰቦችንም ልክ በኢብራሂም እና በኢብራሂም ቤተሰቦች እንዳሰፈንከው በረካ በእነሱም ላይ አስፍን። አንተ ምስጉን፣ የተከበርክ ነህና።” ከዚያም ይህንን ካለ በኃላ ወደ ቀኙ ዞሮ፡- «አሰላሙ ዓለይኩም ወረሕመቱሏህ» “የአላህ ሰላምና እዝነት በእናንተ ላይ ይሁን።” ይበል ከዚያም ወደ ግራ ዞሮ እንዲህ ይበል: «አሰላሙ ዓለይኩም ወረሕመቱሏህ» “የአላህ ሰላምና እዝነት በእናንተ ላይ ይሁን።” ይበል በዚህም የሱብሒ (ፈጅር) ሶላት ይጠናቀቃል።
2- የዙሁር፣ የዐስር እና የኢሻ ሶላትን በተመለከተ፡-
እያንዳንዳቸው አራት ረከዓዎች ሲሆኑ የመጀመሪያዎቹን ሁለት ረከዓዎች ሁለቱን የፈጅር ረከዓዎች እንደሰገደው ይሰግድና ነገር ግን ከነሱ በኋላ ለተሻሁድ ሲቀመጥ ሰላቱን ሳያጠናቅቅ “አሰላሙ ዓለይኩም ወረሕመቱሏህ”ም ሳይል በፊት እንደገና ቆሞ እንደ መጀመሪያዎቹ ሁለት ረከዓዎች ሁለት ረከዓዎችን በመስገድ እንደገና ለተሻሁድ ተቀምጦ በመጀመሪያ ተቀምጦ ያለውን አሁንም በድጋሚ ይላል። በነብዩ ሙሓመድም ላይ ሶለዋትን ያወርዳል። ከዚያም ልክ በፈጅር (ሱብሒ) ሶላት እንዳደረገው በቀኙ ከዚያም በግራው ያሰላምታል(አሰላሙ ዓለይኩም ወረሕመቱሏህ ይላል)።
3- የመግሪብ ሶላት ደግሞ፡-
የሚሰግደው ሶስት ረከዓ ነው። ሁለቱን ልክ ከላይ እንደተገለፀው የመጀመሪያዎቹን ሁለት ረከዓዎች እንደሰገዳቸው አድርጎ እንደሰገደ ተቀምጦ ልክ ለሌሎቹ ሶላቶች በተቀመጠበት ጊዜ እንዳለው በማለት ነገር ግን ሳያሰላምት ይልቁንም ለሶስተኛ ረከዓ በመነሳት ከዛ በፊት እንዳለውና እንዳደረገው በማለትና በመስራት ከዚያም(ከመጨረሻው ረከዓ) ሁለተኛውን ሱጁድ ከሰገደ በኋላ ተቀመጦ ከዚያ በፊት (በሁለተኛው ረከዓ) ያለውን በማለት ከዚያም በመጀመርያ ወደ ቀኝ ዞሮ ከዚያም ወደ ግራ ዞሮ ያሰላምታል (እየዞረ አሰላሙ ዓለይኩም ወረሕመቱሏህ ይላል)። ሰጋጁ በሩኩዕ እና በሱጁድ የሚለውን ቢደጋግመው በላጭ ይሆንለታል።
ወንዶቹም እነዚህን አምስት የግዴታ ሶላቶች በመስጂድ ውስጥ በጀመዓ መስገድ ግዴታቸው ነው። በአንድ ከነሱ ቁርአንን በመቅራት በላጭ የሆነው በሶላት ውስጥ ከነሱ የበለጠ እውቀት ያለው እና በሃይማኖቱ በጣም ጥሩ የሆነው ኢማም መሪነት ይሰግዳሉ። ኢማሙ (የሚያሰግደው) ከሩኩዕ በፊት ቆሞ ሳለ ባለው ቂርአት በፈጅር ሶላት፣ በመቕሪብ እና በዒሻእ ሶላቶች ሁለት ሁለት የመጀመርያዎቹ ረከዓዎች ላይ ድምፁን ከፍ አድርጎ መቅራት ይኖርበታል። ከሱ በኃላ ያሉት ተከታዮች ደግሞ በጥሞና ማዳመጥ ይገባቸዋል።
ሴቶች ደግሞ በቤታቸው ውስጥ ተከናንበውና ተሰትረው ነው የሚሰግዱት። መላ ሰውነታቸውን፣ እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ሳይቀር ይከናነባሉ። ምክንያቱም ከፊቷ በስተቀር ሁሉም ሀፍረተ ገላ ነዉና ከሰዎች እንድትሸፈንም ታዝዛለች። ምክንያቱም ትታወቅበትና ጉዳትም ሊያስከትልባት ይችላልና። በመሆኑም አንዲት ሙስሊም ሴት መስጂድ ውስጥ መስገድ ከፈለገች ምንም አይነት ተቃውሞ የለም ሽቶም ሳትቀባ ተከናንባ ከወጣች እና ከወንዶች ጀርባም ከሰገደች (በዚህ አኳኃን) ሙስሊሟ ሴት ወደ መስጂድ ሂዳ መስገዷን የሚከለክል ምንም አይነት ከልካይ የለም። ይህንንም አኳኃን ተላብሳ ሊሆን ይገባታል ያልነው እነሱንም በሷ ራሷንም በነሱ እንዳይፈተኑ ሲባል ነው።
ሙስሊሙ በተመስጦ፣ በጥልቅ ትህትና እና ልቦናውን ሰብስቦ ለአላህ መስገድ አለበት። እንዲሁም ሲቆም፣ ሲጎነበስም ይሁን ሱጁድ ሲወርድ በተረጋጋ መንፈስ ሊሆን ይገባዋል። በሶላቱ ውስጥ መጣደፍም ሆነ መጫወትም የለበትም። አይኑንም ወደሰማይ ማንጋጠጥ በቁርአንና የሶላት አዝካሮችን ለማለት ካልሆነ በቀርም መናገርም የለበትም። ሁሉም ነገር ቦታውን ጠብቆ ሊሆን ይገባዋል። [30] ምክንያቱም የላቀው አላህ ሶላትንም የደነገገው እርሱ ሊወሳበት ነውና።
[30] አንድን ሰው ለማስጠንቀቅ ወይም ምላሽ ለመስጠት ካልፈለገ በቀር፤ ያኔም እንዲህ ነው የሚለው፡ ኢማሙ በድርጊት፣ በመጨመር ወይም በመቀነስ ላይ አንዳች ስህተትን ቢሰራ ተከታዩ ለኢማሙ "ሱብሓነሏህ" በማለት እንዲነቃ ይናገረዋል። ሶላት ሰጋጁ ለሚያሰግደው ሰው ያነቃበታል። ሴት ልጅ በመናገር ሳይሆን በጭብጨባ ታነቃለች፤ ምክንያቱም ድምጿ ፈታኝ ነውና።
በዕለተ ጁምአ ሙስሊሞች ሁለት ረከዓ የጁምዓ ሰላት ይሰግዳሉ። ኢማሙ ልክ እንደ ፈጅር ሰላት ድምጹን ከፍ አድርጎ ቁርአን ይቀራሉ። ከሶላቱ በፊትም ኢማሙ ሙስሊሞችን የሚያስታውሱበት እና ስለ ሃይማኖታቸው የሚያስተምርባቸው ሁለት ኹጥባዎችን ያደርጋሉ። ወንዶችም ኢማሙ ዘንድ በኹጥባው መገኘት ይገባቸዋል። የጁምዓ ቀን ዙህር ሰላት ይኸው ነው።
***
ከእስልምና ማእዘናት ሦስተኛው የእስልምና ማእዘን (ዘካ)
አላህም የገንዘብ መጠኑ ኒሷብ (ሸሪዓዊው የሀብት ልኬት) የሚሞላ ገንዘብ ያለው ሙስሊም ሁሉ በየአመቱ ዘካ እንዲከፍል አዝዟል። በቁርአን እንደተብራራው ዘካ ሊሰጣቸው መብት ላላቸው ለድሆች እና ለሌሎችም ሊሰጥ ይገባዋል። [31] ኒሷብ ማለት፡- ኒሷብ በወርቅ ሲተመን ሀያ “ሚሥቃል” ሲሆን በብር ማእድን ደግሞ ሁለት መቶ “ዲርሀም” ወይም ያንኑ የሚመጥን የወረቀት ምንዛሪ ነው። የንግድ ሸቀጦች ማለትም ሁሉም አይነት እቃዎች ዋጋቸው ኒሷብ ላይ ደርሶ አንድ አመት ካለፈ ባለቤቱ ዘካቸውን መክፈል አለበት። የእህል እና የፍራፍሬ ኒሷብ ሶስት መቶ ሷዕ ነው። ለሽያጭ የሚዘጋጁ ሪል እስቴቶችም ዘካ የሚወጣላቸው በዋጋ ተመናቸው ሲሆን ለኪራይ ብቻ የሚዘጋጁ ሪል ስቴቶች ግን በኪራይ ተመናቸው ብቻ ነው ዘካ የሚከፈልባቸው። ኒሷቡ የሞላ ወርቅ፣ ብር(ማእድኑ)ና የንግድ ዕቃዎች ዘካ በአመት ከ2.5% ማለትም የአንድ አሥረኛ ሩብ የዘካ መጠን መክፈል አለበት። ያለምንም ችግር በመስኖ ከሚለማው ለምሳሌ በወንዞች፣ በምንጭ ወይም በዝናብ ውሃ የሚለማ እህልና ፍራፍሬ 10% በአስቸጋሪ ውኃ ለምሳሌ በክሬን እየተሳበ በሚመጣ ውኃ ከሚለማ ደግሞ የአንድ አስረኛ ግማሽ 5% ነው።
የእህልና ፍራፍሬ ዘካ የሚሰጥበት ጊዜ ሲበሰብ ነው። በአመት ሁለት ወይም ሶስት ጊዜ የሰበሰበ እንደ ሆነ በእያንዳንዱ ጊዜ ዘካውን መክፈል አለበት። ከግመል፣ ላምና በግ ላይም ዘካ አለ። መጠናቸውም በእስልምና የአሕካም ኪታቦች ውስጥ ተብራርቷልና ይከልሱት። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ አጥሪዎች፣ ቀጥተኞች ኾነው ሊግገዙት፣ ሶላትንም አስተካክለው ሊሰግዱ ዘካንም ሊሰጡ እንጅ ያልታዘዙ ሲኾኑ (ተለያዩ)፡፡ ይህም የቀጥተኛይቱ (ሃይማኖት) ድንጋጌ ነው፡፡}
[አል_በይናህ፡ 5]
ዘካ መክፈል የድሆችን ነፍሳቸውን ያጣፍጣል፣ ፍላጎታቸውን ያሟላል፣ በነሱና በሀብታሞች መካከል ያለውን የፍቅር ቁርኝትን ያጠነክራል።
የእስልምና ሃይማኖት በሙስሊሞች መካከል የማህበራዊ ቁርኝትን እና የገንዘብ ትብብርን በዘካ ወሰን ላይ ብቻ የተገደበ አይደለም። ይልቁንም አላህ ባለጠጎችን በረሃብ ጊዜ ለድሆች እንዲመግቧቸው አዟል ጎረቤቱ እየተራበ የእርሱን መጥገብ እንኳ ከልክሏል። ሙስሊሙ ዘካተል ፊጥርንም እንዲያወጣ ግዴታ ተጥሎበታል። እርሱም በዒድ አልፊጥር ቀን የሚሰጠው በሀገሪቱ ከሚበላው የምግብ አይነት በነፍስ ወከፍ ደረጃ የጨቅላ እና የአገልጋይ እንኳ ሳይቀር አስተዳዳሪው በእያንዳንዱ ግለሰብ አንድ ሷዕ የወጣለታል። አላህ የትኛውም ሙስሊም ለአንዳች ነገር ከማለ በኃላ የማለበትን ጉዳይ ካልተወጣው ለመሐላው ተፀፅቶ የመሀላ ማካካሻ እንዲከፍል አዟል።[32] አላህ የምፅዋት ስራዎችን አበረታትቷል። በአላህ መንገድ ለሚለግሱ ለጋሾችም ሁሉ በላጭ የሆነ መልካምን ምንዳ እንደሚመነዳቸው ብሎም ምንዳቸውንም እጥፍ ድርብ እንደሚያደርግላቸው ቃል ገብቶላቸዋል። የመልካም ስራ ምንዳውም ከአስር እጥፍ እስከ ሰባት መቶ እጥፍ ከዛም በላይ ብዙ እጥፍ ድርብ ነው። [32] የመሐላ ማካካሻው ባሪያን ነጻ በማውጣት ወይም አሥር ድሆችን በመመገብ ወይም በማልበስ መካከል ምርጫ የተሰጠው ሲሆን እንኝህን ማግኘት የማይችል ከሆነ ደግሞ ሦስት ቀን የመፆም ግዴታ አለበት። ***
ከእስልምና ማእዘናት አራተኛው የእስልምና ማእዘን (ጾም)
የረመዷንን ወር መፆም:‐ ይኸውም በሂጅሪያ አመት አቆጣጠር ዘጠነኛው ወር ነው።
የጾም አኳኃን፡-
ሙስሊም የሆነ ሰው የሌሊቱ ጎህ ከሚቀድበት ሰአት በፊት ቀደም ብሎ ካለው ጊዜ ጀምሮ መፆምን በማሰብ ከመብላት፣ ከመጠጣትና ከግብረ-ስጋ ግንኙነት ፀሀይ ጠልቃ ፆሙን እስኪያቋርጥ ድረስ በመታቀብ ነው። ይህንንም የሚያደርገው የረመዳን ወር እስኪጠናቀቅ በየለቱ ነው። በዚህም የሚከጅለው የላቀው አላህን ማስደሰትና ማምለክ ፈልጎበት መሆን ይኖርበታል።
በጾም ውስጥ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ጥቅሞች ያሉት ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ በዋነኝነት፡-
አላህን ማምለክ እና ትእዛዙን ማክበር ነው። ለአላህ ሲል ፍላጎቱን፣ መብሉን እና መጠጡን ይተዋል። ይህም የላቀው አላህን መፍራት ከሚገለፅባቸው ሰበቦች መካከል ነው።
የጾም የጤና፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ጠቀሜታዎች በተመለከተ እጅግ በጣም ብዙ ናቸው። በትክክለኛ እምነት እና ኢማን ላይ ሆነው የሚጾሙ ብቻ ናቸው የሚደርሱበት። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{እናንተ ያመናችሁ ሆይ ጾም በነዚያ ከናንተ በፊት በነበሩት (ሕዝቦች) ላይ እንደ ተጻፈ በናንተም ላይ ተጻፈ (ተደነባ) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና።}
{የተቆጠሩን ቀኖች (ጹሙ)። ከእናንተም ውሰጥ በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የኾነ ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን መጾም አለበት። በእነዚያም ጾምን በማይችሉት ላይ ቤዛ ድኻን ማብላት አለባቸው። (ቤዛን በመጨመር) መልካምንም ሥራ የፈቀደ ሰው እርሱ (ፈቅዶ መጨመሩ) ለርሱ በላጭ ነው። መጾማችሁም ለናንተ የበለጠ ነው፤ የምታውቁ ብትኾኑ (ትመርጡታላችሁ)።}
{(እንድትጾሙ የተጻፈባችሁ) ያ በርሱ ውስጥ ለሰዎች መሪ ከቅን መንገድና (እውነትን ከውሸት) ከሚለዩም ገላጮች (አንቀጾች) ሲኾን ቁርኣን የተወረደበት የረመዳን ወር ነው። ከእናንተም ወሩን ያገኘ ሰው ይጹመው። በሽተኛ ወይም በጉዞ ላይ የኾነም ሰው ከሌሎች ቀኖች ቁጥሮችን (በልኩ) መጾም አለበት። አላህ በእናንተ ገሩን (ነገር) ይሻል። በእናንተም ችግሩን አይሻም። ቁጥሮችንም ልትሞሉ አላህንም ቅኑን መንገድ ስለመራችሁ ታከብሩትና ታመሰግኑት ዘንድ (ይህን ደነገግንላችሁ)።
[አልበቀራህ: 183-185]
*** የላቀው አላህ በቁርኣን እና መልእክተኛውም ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በሐዲሥ ካብራሯቸው የፆም ድንጋጌዎች መካከል፦
1- በሽተኛና መንገደኛ ሰው ፆማቸውን ለዕለቱ ይተውና ከረመዷን በኋላ ባሉት ሌሎች ቀናት ያለፈባቸውን ፆማቸውን ይፆሙታል። እንዲሁም የወር አበባ ላይ ያሉ ሴቶችና የድህረ ወሊድ ደማቸው ያልቆመ ሴቶችም እንዲሁ ፆማቸው ትክክለኛ ፆም ስላልሆነ ለዕለቱ ፆማቸውን ይተውና በሌላ ጊዜ ያልፆሙባቸው ቀናቶችን ያካክሳሉ። 2- እርጉዝ እና የምታጠባ ሴትም እንደዚሁ ለራሳቸውም ሆነ ለልጆቻቸው ስጋት ከፈጠረባቸው ፆማቸውን አፍርሰው በሌላ ጊዜ ቀዷ ያወጡታል። 3- ፆመኛ ሰው ፆሙን ረስቶ ቢበላ ወይም ቢጠጣና ከዚያም ቢያስታውስ አፉ ላይ ያለውን ይትፋና ፆሙን ይቀጥል ፆሙ ትክክለኛ ፆም ነው። ምክንያቱም በመርሳት፣ በስህተት እና በመገደድ የተደረገን ነገር አላህ ለነብዩ መሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ህዝብ ይቅር ብሎላቸዋልና።
***
ከእስልምና ማእዘናት አምስተኛው የእስልምና ማእዘን (ሀጅ)
በሕይወታችን አንድ ጊዜ ወደ ተቀደሰው የአላህ ቤት የሚደረግ ጉዞ ሲሆን ከዛ በላይ የሚደረግ ከሆነ በግል ፈቃደኝነት የሚደረግ ተወዳጅ ተግባር ነው። በሐጅ ውስጥ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ጥቅሞች አሉት፦
የመጀመሪያው፡ የሐጅ ስርአት በነፍስ፣ በሥጋና በገንዘብ የላቀው አላህን ማምለክ ነው።
ሁለተኛው: የሓጅ ስርአት ከየቦታው የተሰባሰቡ ሙስሊሞች አንድ ቦታ ላይ፣ አንድ አይነት ልብስ ለብሰው በተመሳሳይ ጊዜ አንድ ጌታን ለማምለክ መሰባሰብን ይዟል። በዚህ ስርአት በመሪና ተመሪ፣ በሀብታምና ድሃ፣ በነጭና ጥቁር መካከል ልዩነት አለመኖሩ ሁሉም በመካከላቸው ልዩነት የሌላቸው የአሏህ ፍጡሮችና ባሪያዎቹ መሆናቸው እጅጉን ይጎላል። በዚህም አጋጣሚ ሙስሊሞች እርስ በራሳቸው ይተዋወቁበታል ይተባበራሉም፤ አሏህም ሁሉንም ከሞት ቀስቅሶ አንድ ሜዳ ላይ የሚሰበስብበትን ቀን ያስታውሱበታል፤ ሁሉም አሏህን በመታዘዝ ከሞት በኋላ ለሚመጣው ነገርም ይዘጋጁበታል።
ሙስሊሞች የትም ቢሆኑ በሶላታቸው ሁሉ እንዲቅጣጩባት ባዘዘበት ካዕባ - የሙስሊሞች ቂብላ - ዙርያ የመዞር አላማው፤ በመካ ሌሎች ቦታዎች ላይ በተወሰነላቸው ጊዜ የመቆም አላማው፡ በዓረፋ፣ በሙዝደሊፋ እና በሚና የሚያደርጉት ቆይታ፤ የዚህ ሁሉ ዓላማው የላቀው አላህን በእነዚያ ቅዱሳን ቦታዎች አላህ ባዘዘበት መልኩ ለማምለክ ነው።
ካዕባ ራሱም ይሁን እነዛ ቅዱሳን ቦታዎችና ፍጥረታት ሁሉ ግን አይመለኩም፣ አይጠቅሙምም፣ አይጎዱምም። አምልኮ የሚደረገውም ለአላህ ብቻ ነው፤ ጠቃሚውም ጎጂውም አላህ ብቻ ነው። ስለዚህም አላህ ሙስሊሞችን ሓጅ እንዲያደርጉ ባያዛቸው ኖሮ የእነርሱ ሓጅ ማድረግ ባልተፈቀደላቸው ነበር። ምክንያቱም አምልኮ በአመለካከት እና በፍላጎት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን አላህ በኪታቡ ወይም በመልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሱና የተላለፈ ትእዛዝ ሲኖር ብቻ ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ለአላህም በሰዎች ላይ ወደርሱ መሄድን በቻለ ሁሉ ላይ ቤቱን መጎብኘት ግዴታ አለባቸው። የካደም ሰው አላህ ከዓለማት ሁሉ የተብቃቃ ነው።}
[አሊ-ዒምራን፡ 97][33]
[33] መሀይሞች ወደ ቅዱሳን መቃብርና ወደ ስፍራው በመሔድ የሚያደርጉት ጉዞማ የኃያሉ አላህ ትእዛዝና የመልእክተኛውን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ትእዛዝ መጣስ ነው። የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦ "ከሶስቱ መስጊዶች በስተቀር መንገደኛ ስንቁን አጥብቆ ሊጓዝ አይገባውም: አል-መስጂድ አል-ሐራም፣ ይህ የእኔ መስጊድ እና አል-መስጂድ አል-አቅሳ ናቸው። (ቡኻሪ (1189) እና ሙስሊም (1397) ከአቡ ሁረይራህ ሀዲስ ዘግበውታል።)
ዑምራም እንዲሁ ለሙስሊም በህይወት ዘመኑ አንድ ጊዜ ከሐጅ ጋርም ይሁን በማንኛውም ጊዜ ግዴታው ሲሆን በመዲና የነብዩን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) መስጊድ መጎብኘት ግን በሐጅም ሆነ በማንኛውም ጊዜ ግዴታ አይደለም። ይልቁንም የሚበረታታ ነው፤ የሰራ ሰው ምንዳውን ያገኝበታል፤ ያልሰራም አይቀጣበትም። “ሐጅ ያደረገና ያልጎበኘኝ እኔን አቅልሎኛል” የሚለው ሓዲሥ ግን ትክክለኛ (ሶሒሕ) ሓዲሥ አይደለም። ነገር ግን የአላህ መልእክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) [34] ላይ የተቀጠፈ ሓዲሥ ነው።
[34] እንደዚሁም፡ ተከታዩ ሓዲሥም: "እኔ ባለኝ ደረጃ አላህን ተማፀኑ፤ በአላህ ዘንድ ያለኝ ደረጃ ሰፊ ነውና" እና ተከታዩ ሓዲሥም፡ "በድንጋይ መልካም የሚያስብ ሰው ይጠቅመዋል" ሁሉም የተቀጠፉ ሀሰተኛ ሐዲሶች እንዲሁም በየትኛውም ታማኝ የሐዲስ ኪታቦች ውስጥ የማይገኙ ይልቁን እነዚህና መሰል ሓዲሦች ጠሞ አጥማሚዎች ሌላ በማያውቅባቸው ቦታ ሆነው ወደ ሽርክና ቢድዓ በሚጠሩ የተሳሳቱ ሰዎች መጽሐፍ ውስጥ ነው የሚገኙት።
ለመዘየር ተብሎ ጉዞ ከሚወጣባቸው መስጂዶች መካከል አንዱ ይሀው መስጅድ ነው። በመሆኑም ጎብኝው ደርሶበት ሰላምታ ቢሰጥና የነብዩን ( ﷺ) ቀብር ቢጎበኝና እንዲህ በማለት ሰላምታ ቢያቀርብም ይደነገግለታል፡ በትህትና እና ዝቅ ባለ ድምፅ "አሰላሙ ዓለይክ ያ ረሱለሏህ" ብሎ ሰላምታን ከሰጠ በኃላ ይንቀሳቀስ እንጅ ምንም ነገር አይጠይቀውም። እሳቸውም - ﷺ - ህዝባቸውን እንዳዘዙት እና ሶሓቦችም - ረዲየሏሁ ዓንሁም - እንዳረጉት ያድርግ።
እነዚያም በነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) መቃብር ላይ ልክ ሶላት ላይ እንዳሉ ሆነው እጅግ በሰመጠ ፍርሀት ሆነው የሚቆሙት እና ፍላጎታቸውንም ከሳቸው የሚለምኑት ወይም ለጭንቀታቸው የነብዩን እርዳታ የሚሹ ወይም ከአላህ ጋር እንዲያማልዷቸው ነብዩን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የሚመፀኑ እነዚህ በአላህ ያጋሩ ሙሽሪኮች ናቸው። ነቢዩም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከእነርሱ የጸዱ ናቸው። በመሆኑም ማንኛውም ሙስሊም ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ዘንድም ይሁን ሌላው ዘንድ ይህንን ከማድረግ ሊጠነቀቅ ይገባዋል። ከዚያም የሁለቱን ባልደረቦቻቸውን የአቡበክርን እና የዑመርን (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና) መቃብሮችን ይጎብኝ። ከዚያም የአል-በቂዕ እና የሸሂድ ሰዎች ይጎብኝ። ለሙስሊሞች የተደነገገው መቃብር የሚጎበኝበት ስርአት ጎብኚ ለሙታኑ ሰላምታን ያቀርባል፤ ለነሱም ዱዓ አድርጎ አላህን ይማፀንላቸዋል፤ በሞትም ተገስፆ መመለስ ነው።
የሐጅና ዑምራ አኳኃኑ ይህ ነው።
ሓጃጁ መጀመሪያ ጥሩውን እና ህጋዊውን ሲሳዩን ይመርጣል። ከተከለከለው ሲሳይም ይጠነቀቃል። ምክንያቱም የሐራም ሲሳይ የባለቤቱን ሐጅ እና ዱዓ ተቀባይነት እንዳያገኝ ምክንያት ነውና። መልዕክተኛውም በሓዲስ እንዲህ ብለዋል፡-
"ከሓራም ገንዘብ የበቀለ ሥጋ ሁሉ፣ ለእሳት ይበልጥ የተገባ ነው።" (35)
የተውሂድ እና የኢማን ጓድ የሆኑ ባልደረቦችንም ይመርጣል።
[35] በአል-ጦበራኒ በአል-አውሳት (4480) ዘግበውታል፣ እና አል-በይሀኪ “ሹዓብ አል-ኢማን” (2/173/2) ዘግበውታል፣ አልባኒ ደግሞ በአል-ሲልሲላህ አል- ሰሂሃህ (6/212)።
*** የሐጅና ዑምራ ኢሕራም ማድረጊያ ስፍራዎችና ጊዜያት
በመኪና እና በመሳሰሉት ተጓዥ ከሆነ ሚቃት እንደደረሰ እዛው ኢሕራም ያደርጋል። በአውሮፕላን የሚጓዝ ከሆነ ደግሞ ሲቃረብ ገና ከማለፉ በፊት ኢሕራም ያድርግ። ነቢዩﷺ ሰዎች ኢሕራም እንዲያደርጉባቸው ያዘዙበት ሚቃት (መቼት) አምስት ሲሆኑ እነሱም፡-
1- ዙል-ሑለይፋ (አቢያር አሊ) ለመዲና ሰዎች።
2- አል-ጁህፋህ (ራቢግ አቅራቢያ) ለሻም፣ ግብፅ እና ሞሮኮ ህዝቦች ነው።
3- ቀርን አል-ማንዚል (አል-ሰይል ወይም ዋዲ ሙሕሪም) ለነጅድ እና ለጧኢፍ ሰዎች እና በነሱ አቅጣጫ ወደ መካ ለሚገባ ነው።
4- ዛቱ‐ኢርቅ (ለኢራቅ ሰዎች)።
5- የለምለም ለየመን ሰዎች።
በነዚህ በተጠቀሱት ነዋሪ ሳይሆን በነሱ የሚያልፍም በሚያልፍበት ሚቃት ነው ኢሕራም የሚያደርገው። የመካ ሰዎች እና ቤታቸው ከሚቃቶቹ የቀረበ ቦታ ላይ የሆኑ ሰዎች ኢሕራም የሚያደርጉት በቤታቸው ነው።
*** የኢሕራም አኳኃን
ከኢሕራም በፊት ራሱን ማጥራት፣ መፅዳት እና ሽቶ መቀባቱ ተወዳጅ ይሆንለታል። ከዚያም ሚቃቱ ላይ ሲሆን የኢሕራም ልብሱን ይለብሳል። በአውሮፕላን ተሳፋሪ ከሆነ ደግሞ ገና በአገሩ እያለ ተዘጋጅቶ ይወጣና ከዚያም ልክ በሚቃት ቦታው ላይ ሲደርስ ወይ በአቅራቢያው ሲጠጋ ኒያውንም ይላል ተልቢያውንም[36] ያደርጋል። የወንዶች የኢሕራም ልብስ ያልተሰፋ ብትን ሽርጥና ግልድም ሲሆን ጭንቅላቱን ሳይሸፍን በነሱ ሰውነቱን ይሸፍንባቸዋል።
ሴት ልጅ ለኢሕራም ተብሎ የተለየ የልብስ አይነት የላትም። መልበስ ያለባት እንደሁልጊዜዋ ሰዎች በማናቸውም መልኩ ቢመለከቷት የማይፈተኑበት ልብሶችን ነው። ወደ ኢሕራም ስትገባ እንደ ጭንብልና ጓንት ያሉ የተሰፉ ልብሶችን አትለብስም። ነገር ግን አንዳች ልብስ በጭንቅላቷ ላይ ጣል ታደርግና ወንዶችን ስታይ ፊቷን ትሸፍንበታለች። ልክ የምእመናን እናቶች እና የመልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ባልደረቦች ሚስቶችም ሲያደርጉት እንደነበረው ማለት ነው።
[36] ተልቢያውን ያደርጋል፡- ማለትም እንዲህ ይላል፡ ለበይከ ሐጀን ወይም ለበይከ ዑምራ: ማለትም በዘለቄታዊ ለአላህ ምላሽ ሰጭ መሆንን ማወጅ ነው።
ከዚያም ሓጅ. ድራጊው የኢሕራም ልብሱን ከለበሰ በኋላ በልቡ ዑምራ ለማድረግ በማሰብ እንዲህ በማለት ተልቢያውን ያደርጋል። “አሏሁመ ለበይከ ዑምራ” ይልና በሷው ተመቱዕ [37] አድርጎ ከተጣቀመ በኃላ ወደ ሓጅ ይሸጋገራል።
ተመቱዕ የሚባለው ስርአት በላጩ ነው። ምክንያቱም መልእክተኛው ﷺ ባልደረቦቻቸውንም ያዘዙበትና አጥብቀው የመከሩበት ነውና። እንዲሁም ትእዛዙን ከመፈፀም ወደ ኋላ የሚሉ ሰዎችን ደግሞ ገስፀውታል። ምናልባት ግን “ሀድይ” የያዘ ሰው ካልሆነ በስተቀር [ 38]፣ እንዲህ ያለው እሳቸው ﷺ እንዳደረጉት ቃሪን እንደሆነ ነውና የሚቀረው።
ቃሪን፡- ይህ ማለት ተልቢያውን ሲያደርግ እንዲህ የሚል ነው: “አሏሁመ ለበይከ ዑምረተን ወሓጀን” እርድ በሚከናወንበት እለት እርዱን እስከሚያከናውን ድረስ ከኢሕራሙ አይወጣም። [37] ተመቱዕ: ይህ ማለት በሐጅ ወቅት ዑምራን የሚያከናውን ሲሆን ከዚያም ከኢሕራም ሙሉ በሙሉ ይወጣና በኢሕራም ጣሉበትን ክልከላዎች ተፈቅደውለት "ይጣቀማል"። ከዚያም በስምንተኛው ቀን ለሐጅ እንደገና ኢሕራም ያደርጋል። ይህ ማለት ሐጅና ዑምራን አንድ ላይ የሚያከናውን ሲሆን ነገር ግን የሐጅ ሥራዎችን ብቻ ነው የሚፈፅመው። ይሁን እንጅ ኒያው ዑምራንም አስከትሎ እንደሚያከናውን ነው የሚያደርገው። [38] “ሀድይ”፡- ሓጅ አድራጊው ግመል፣ ከብት፣ በግ ወይም ፍየል እርድ መስዋእት አድርጎ ምጽዋት የሚሰጥበትና ለራሱም የሚበላበት ስርአት ነው።
ሙፍሪድ: ሐጅ ለማድረግ ብቻ አስቦ እንዲህ ይላል፡- “አሏሁመ ለበይከ ሐጀን”
***
ሙሕሪም የሆነ ሰው የሚከለከላቸው ነገሮች አንድ ሙስሊም ኢሕራም ለመግባት ኒያውን ካደረገ በኃላ የሚከለከላቸው ነገሮች፦ 1- የግብረ ሥጋ ግንኙነት እና እንደ በስሜት መሳም፣ በስሜት መነካካት ፣ ስለዚያ ማውራት፣ ለጋብቻ መታጨት እና የጋብቻ ውል መፈፀም(ኒካሕ ማሰር)። በመሆኑም ኢሕራም ውስጥ የገባ ሰው አያገባምም አያጋባምም። 2- ፀጉርን መላጨት ወይም ከፀጉር አንዳች ያክልን እንኳ መቀነስ። 3- ጥፍርን መቁረጥ 4- ለወንድ ጭንቅላት ላይ በሚጣበቅ ነገር ጭንቅላትን መሸፈን፤ ይሁን እንጅ በአንዳች ከለላ፣ በድንኳን፣ በመኪና መሰል ነገር መከለል ግን ችግር የለውም። 5- ሽቶ መቀባትም ይሁን ሽቶ ሽቶ መሽተት 6 - የየብስ አደን፤ በዚህም መሰረት ማደንም ይሁን ወደ አደኑ ማመላከት አይፈቀድለትም። 7- ለወንዶች የተሰፋ ልብስ መልበስ፤ ለሴትም ቢሆን ለፊቷ እና ለእጆቿ የተሰፋ ነገርን መልበሷ የተከለከለ ነው። ወንዶች ጫማ መልበስ ያለባቸው ሲሆን ያላገኘ ኹፍ መልበስ ይኖርበታል።
ከነዚህ ክልከላዎች መካከል አንዱንም ባለማወቅ ወይም በመርሳት የፈፀመ ከሆነ ከማስወገድ ውጭ በእርሱ ላይ ሌላ ግዴታ የለበትም። ሙሕሪም የሆነ ሰው ወደ ካዕባ ሲደርስ ከጥቁሩ ድንጋይ (ሓጀረል አስወድ) ጎን ጀምሮ የመግቢያ[39] ጡዋፉን ሰባት ዙር ይዞራል። ይህም የዑምራ ጠዋፉ ነው። ለእርሱ ቀላል በሆነለት ሁሉ አላህን ያወሳል ይለምናል እንጅ ለጠዋፍ የተወሰነ የዚክርም ይሁን የዱዓእ አይነት የለውም። [40] ከዚያም ከቻለ ከመቃሙ ኢብራሂም ጀርባ ካልቻለ ደግሞ ሓረም ውስጥ በተመቸው ቦታ የጠዋፍ ሁለት ረከዓዎችን ይሰግዳል [41]። ከዚያም ሰዕይ (ሶምሶማ) [42] ወደሚደረግበት ቦታ ይሄድና በአል-ሰፋ ለመጀመር የ “ሰፋ” ኮረብታ ላይ ወጥቶ ወደ ቂብላ በመዞር “አሏሁ አክበር” “ላ ኢላሃ ኢለሏህ” እያለ አላህን እያወሳና እየተማፀነ ይቆያል። ከዚያም ወደ አል-መርዋህ በመሮጥ በላዩ ላይ ወጥቶ ወደ ቂብላ በመዞር ተክቢራውን እያደረገ አላህን በማውሳት እና በመማጸን ቆይቶ ከዚያም በድጋሚ ወደ አል-ሰፋ ይመለሳል። በዚህ መልኩ ሰባት ዙሮችን እየዞረ እስኪያጠናቅቅ ድረስ ይዞራል። ከሰፋ ወደ መርዋ ሲሄድ አንድ ዙር ከመርዋ ተመልሶ ወደ ሰፋ ሲሄድ ደግሞ ሌላ ዙር አድርጎ እየቆጠረ ሰባትን እስኪያጠናቅቅ ይመላለሳል። ከዚያም ፀጉሩን ያሳጥር፤ ሴቲቱም እንዲሁ ከፀጉሯ ጫፍ ላይ የጣት አንጓ ያህል ትቆርጣለች። ተመቱዕ የሚያደርግ ሰው በዚሁ ዑምራውን ጨርሶ ኢሕራሙን ይፈታና በኢሕራም ምክንያት የተከለከላቸው ነገሮች ሁሉ የተፈቀዱ ይሆኑለታል። [39] ማለትም ወደ ተከበረው ቤት(መስጅደል ሓረም) መግባት፣ ይኸውም መካ ውስጥ የሚገኘው ታላቁ መስጊድ ነው። [40] በሁለቱ ምሶሶዎች መካከል ካልሆነ በቀር፤ የዛኔ በተከታዩ የአላህ ቃል ውስጥ የተጠቀሰውን የመጣውን ነው የሚለው፦ (ጌታችን ሆይ በቅርቢቱ ዓለም መልካሙን ነገር በመጨረሻይቱም ዓለም መልካም ነገርን ስጠን ከእሳትም ቅጣት ጠብቀን) [አል-በቀራህ፡ 201]።
[41] የኢብራሂም (ዐለይሂ-ሰላም) መቆሚያ ነው።
[42] ሰዕይ ማድረጊያ ሲባል: ሶምሶማና ሩጫ የሚደረግበት ቦታ ሲሆን በሰፋ እና መርዋ መካከል በእግር ሶምሶማ እና ሩጫ ማድረግ ነው። እነኝህ ሁለቱ ኮረብታዎች ናቸው።
አንዲት ሴት ኢሕራም ውስጥ ከመግባቷ በፊትም ይሁን ከገባች በኃላ የወር አበባ ቢያጋጥማት ወይም ብትወልድ እንደሌሎች ሑጃጆች ተልቢያዋን በዑምራ እና በሓጅ አቆራኝታ ተልቢያ በማድረግ ቃሪንን ነው የምትፈፅመው። ምክንያቱም የወር አበባና የድህረ ወሊድ ደም መፍሰስ ኢሕራምንም ይሁን በቅዱስ ቦታዎች ላይ መቆምንም ስለማይከለክሉ ነው። ይልቁን የሚከለክሉት ጡዋፍን ብቻ ነው። በመሆኑም ከጡዋፍ በስተቀር ሑጃጆች የሚያደርጉትን ነገር ሁሉ ታደርጋለች። ጡዋፉን ግን ንፁህ እስክትሆን ድረስ ታዘገየዋለች። ሰዎች ለሐጅ ኢሕራም ከመግባታቸው በፊትና ወደ ሚና ከመሄዳቸው በፊት ንፁህ ከሆነች ትተጣጠብና ጠዋፍንም ሰዕይንም ታደርጋለች፤ ፀጉሯን ታሳጥራለች፤ የዑምራዋ ኢሕራምንም ትፈታለች። ከዚያም ከሌሎቹ ጋር በስምንተኛው ቀን ለሐጅ ኢሕራም ታደርጋለች። ነገር ግን እሷ ንፁህ ከመሆኗ በፊት ስምንተኛው ቀን ደርሶ ሰዎች ኢሕራም ካደረጉ “ቃሪን” ስርአት የምታከናውን ሆና ኢሕራሟ ላይ ሳለች አብራ ከሌላው ጋ ተልቢያዋን ታደርጋለች።ከዚያም እሷም ሌሎቹ ሓጃጆች ከመውጣታቸው ጀምሮ እስከ ሚና ድረስ ያለውን፣ በዓረፋ ሜዳ መቆምንና የሙዝደሊፋ ስርአቶችን፣ የጠጠር ውርወራውን፣ እርድ በሚከናወንበትም ቀን እርዷን ማከናወንና ከፀጉሯም ማሳጠር አብራ ከሌሎቹ ጋ ታከናውናለች። ከዚያም ንፁህ ስትሆን ትተጣጠብና የሓጅን ጠዋፍንና “ሰዕዩ”ን ታከናውናለች።
ይህ ጠዋፍና ሰዕይ ለሐጅና ዑምራዋ በቂ ነው። ይህ ለምእመናን እናት ዓኢሻ (አላህ መልካም ሥራዋን ይውደድላትና) ያጋጠማትና ነቢዩም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከሰዎች ጋር ሆና ጠዋፈል ኢፋዷዋንና ስዕይዋን እንዳደረገች ንፁህ ከሆነች በኃላ ያደረገችው ጠዋፍና ሰዕይ ለሓጅዋም ለዑምራዋም በቂ እንደሆነ (ዓኢሻን) ያሳወቁበት ጉዳይ ነው። ምክንያቱም በዑምራ እና በሐጅ መካከል ቂራን የሚያደርግ ሰው እንደሙፍሪድ ከአንድ ጊዜ በላይ ጠዋፍም[43] ይሁን ሰዕይ የሌለው በመሆኑ ነው። የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ግልፅ ያደረጉት በመሆኑ እና በተከታዩ ሌላ ሓዲሥም እንዲህ ያሉ በመሆናቸው ነው: “ዑምራ እስከ ትንሳኤ ቀን ድረስ ወደ ሀጅ ገባች።” አላህ ይበልጡን ያውቃል።
[43] ጠዋፉን በዒድ ቀን ወይም ከሱ በኋላ ነው የሚያደርገው። የመጀመርያው የመግቢያ ጡዋፍ አል-ቁዱም ተብሎ የሚጠራውን በመለከተ ተጨማሪ ነው። ሰዕይ ደግሞ ለሙፍሪድም ይሁን ለቃሪን ከጠዋፈል ቁዱም ጋር አብሮ አስቀድሞት ከሆነ በቂው ነው። ያኔ ሰዕይ ካላደረገ ደግሞ ከጠዋፍ አል‐ኢፋዷ ጋር አብሮ በዒዱ ቀን ወይም ከዚያ በኃላም ቢሆን ሰዕዩን ያደርጋል።
የዙልሒጃህ ወር ስምንተኛው ቀን ከመጣ ሑጃጆች በመካ ማረፊያቸው ሆነው ለሓጅ ኢሕራም ያደርጋሉ። ልክ በሚቃት ንፅህናቸውን ጠብቀው ኢሕራም እንዳደረጉት ማለት ነው። ከዚያም የኢሕራም ልብሳቸውን ይለብሱና ሴትም ይሁን ወንድ የሓጅ ኒያቸውን አድርገው እንዲህ በማለት ተልቢያቸውን ያደርጋሉ: "አሏሁመ ለበይከ ሓጀን"፤ እርድ በሚከናወንበት እለት[44] ከሙዝደሊፋ ወደ ሚና ተመልሶ የጀመረተል ዓቀባህ ጠጠር ውርወራና ወንድም ፀጉሩን ወደ መላጨት ሴቷም ፀጉሯን ወደማሳጠር እስኪመለሱ ድረስ በኢሕራም ከተከለከላቸው ነገሮች እንደታቀበ ይዘልቃል።
[44] እርድ የሚከናወንበት እለት(የውመ‐ን‐ነሕር) ማለት የዙልሂጃ አስረኛው ቀን ያው የኢዱ ቀን ነው። እንደዛ የተባለውም ሑጃጆች ያመጡትን “ሀድይ” እርድ የሚያከናውኑበት ቀን በመሆኑ ነው።
ሑጃጆች በስምንተኛው ቀን ኢሕራም ካደረጉ ከሑጃጆች ጋር አብሮ ወደ ሚና ይወጣና እዚያው ያድራል። ከዚያም ቀስር አድርጎ(ማሳጠር የሚቻሉ ሶላቶችን በተፈቀደው መልኩ እያሳጠረ) ጀምዕ ሳያደርግ(ሁሉንም በሰአቱ) እያደረገ እያንዳንዱን ሶላት ይሰግዳል። የአረፋ ቀን ፀሀይ ከወጣች ከሑጃጆች ጋር ወደ ነሚራህ በመጓዝ ከኢማሙ ጋር የዙህር እና የዓሱር ሶላት “ጀምዕ” እና “ቀስር” ተደርጎ እስከሚሰገድ ድረስ ይቀመጣል። ከዚያም ፀሀይ ከጠለቀች በኋላ ወደ አራፋት ያመራል። በቀጥታ ከሚና ወደ ዓረፋ አልፎ መቀመጥም ይችላል። አራፋትም ሁሉ መቆሚያ ነው።
በዓረፋ የሚቆይ ሓጅ አድራጊ ሁሉ የላቀው አላህን ደጋግሞ ማውሳት፣ ዱዓእ ማድረግ እና ኢስቲግፋር (ምህረትን) መጠየቅን ሊያበዛ ይገባል። ወደ ተራራ ሳይሆን ወደ ቂብላ ይቅጣጭ። ምክንያቱም ተራራው የዓረፋ አንድ አካል ብቻ እንጅ ሌላ ባለመሆኑ እላዩ ላይ መውጣቱ እንደ አምልኮ ሊታይ አይገባውም። ድንጋዮቹንም መሳለምና መታሸትም አይፈቀድም። ምክንያቱም ይህ የተከለከለ ቢድዓ ነውና። ሑጃጆች ፀሀይ እስክትጠልቅ ድረስ ከአረፋ አይውጡ፤ ከዚያም ፀሀይ ከጠለቀች በኋላ ሑጃጆች ወደ ሙዝደሊፋ ይሄዳሉ። እዚያው ከደረሱ በኃላም መግሪብና ዒሻእን “ጀምዑ ታእኺር” አድርገው ዒሻእንም አሳጥረው ይሰግዱና በዚያው ያድራሉ። ከዚያም ጎህ ሲቀድ ፈጅርን ሰግደው አላህን እያወሱ ቆይተው ከዚያም ፀሐይ ሳትወጣ ወደ ሚና ያቀናሉ። ወደ ሚና ሲደርሱም ፀሀይ ከወጣች በኋላ ሽንብራ የሚያካክሉ ከዛ ከፍም ዝቅም የማይሉ ሰባት ጠጠሮችን በ“ጀምረት አል-ዓቀባ” ይወረውራሉ። ጫማ ነገር መወርወር የተፈቀደ አይደለም። ምክንያቱም ይህ ሸይጧን በሚያጌጠው የሸይጧን መጫወቻ መሆን ነው። ሸይጧንን በትክክል ማስቆጨት[45] የሚቻለውም: የመልእክተኛውን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ትእዛዝና መመሪያን በመከተል አላህና መልእክተኛው የከለከሉትን በመተው ነው። [45] ሰይጣንን ማስቆጨት ሲባል፡- ከዚያም የጠጠር ውርወራውን ካደረጉ በኃላ ሓጅ አድራጊዎች ያመጡትን “ሀድይ” ይሰዋሉ፤ ከዚያም ወንዱም ጭንቅላቱን ይላጫል፤ ሴቷም (ፀጉሯን) ታሳጥራለች። በርግጥ ወንድም ቢሆን (ፀጉሩን) ቢያሳጥረው ይፈቀድለታል። ነገር ግን መላጨቱ ሶስት እጅ የተሻለ ነው። ከዚያም ከሴቶች በስተቀርም በኢሕራም የተከለከለው ነገር ሁሉ ለሱ የተፈቀደለት ሆኖ ልብሱንም ይለብሳል። ከዚያም ወደ መካ ይተማሉ። የሓጅ ጠዋፉንና ሰዕዩን ያደርጋል። በዚህም ሂደት ባለቤትን ጨምሮ በኢሕራም የተከለከላቸው ነገሮች ሁሉ መልሰው ይፈቀዱለታል። ከዚያም ወደ ሚና ተመልሶ የዒዱን ቀንና ተከታዮቹን ሁለት ቀናቶችን ከነሌሊታቸው ግዴታ ሚና ላይ ማሳለፍ ይጠበቅበታል። በአስራ አንደኛውና በአስራ ሁለተኛው ቀናቶች ፀሀይ ዘንበል ካለች በኃላ ሶስቱንም የጠጠር ውርወራውን ያደርጋል። መጀመርያ ለሚና ቅርብ ከሆነችው ከትንሻ ይጀምራል፤ ከዚያም መካከለኛው ጋ፤ ከዚያም በዒድ እለት ውርወራውን ባደረገበት ጀመረቱል ዓቀባህ ላይ ጠጠሮቹን ይወረውራል። በእያንዳንዱ ሰባት ጠጠሮችን ይወረውራል፤ ለእያንዳንዱ ጠጠርም ተክቢራውን እያደረገ ይወርውር። የድንጋዮቹን ጠጠሮቹን በሚና ካረፈበት ማረፊያው [46] ነው የሚለቅማቸው። በሚና ማረፊያ ቦታ ማግኘት ያልቻለ ድንኳኖቹ በሚያልቁበት ቦታ ያርፋል። [46] ማለትም፡ ለመቆኖሪያ ቦታ ማለታችን ነው። በ12ኛው ቀን የጠጠር ውርወራውን ካደረገ በኃላ ሚናን ለቆ መውጣት ከፈለገ መብቱ የተጠበቀ ነው። እስከ አስራ ሶስተኛው ቀን ድረስ ቢቆይ የተሻለ ይሆንለታል። ከዚያም ፀሀይ ዘምበል ካለችም በኃላ ጠጠሩን ይወረውራል። መንቀሳቀስ ከፈለገ ደግሞ በተከበረው መስጅድ የመሰናበቻ ጠዋፉን ያደርግና ከዚያም በቀጥታ ጉዞውን ያደርጋል። እናም በወር አበባ ወይንም በወሊድ ደም ያለች ሴት የሓጅ ጠዋፍንና ሰዕይን አድርጋ ከነበረች የመሰናበቻ ጠዋፍ ማድረግ የለባትም። ሓጅ አድራጊው ይዞት የመጣውን “ሀድይ” እርዱን እስከ አስራ አንደኛው ወይንም እስከ አሥራ ሁለተኛው ወይም እስከ አሥራ ሦስተኛው ቀን ድረስ ቢያዘገይ ይፈቀድለታል። የሓጅ ጠዋፉንና ሰዕዩንም ከሚና እስኪወርድ ድረስ ቢያዘገየውም የተፈቀደ ነው። ይሁን እንጅ በላጩ ባሳለፍነው መልኩ ቢፈፀም ነው። ምስጋና ለአላህ ይገባው, የዓለማት ጌታ ለሆነው, እና እዝነትና ሰላም በነቢያችን ሙሐመድ ላይ እና ቤተሰቡ እና በባልደረቦቹ ላይ ይውረድ *** እምነት የላቀው አላህ በአንድ ሙስሊሙ ላይ በእርሱ እና በመልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከማመን በተጓዳኝ በእስልምና ምሰሶዎችም እንዲያምን ግዴታ አድርጎበታል። በተጨማሪም በመላእክቱ[47]፣ ቁርአንን መደምደሚያቸው አድርጎ በመልዕክተኞቹ ባወረዳቸው መጽሐፍት[48]፣ በቁርአኑም ሌሎቹን የሻረበትና በእነሱ ላይም ተቆጣጣሪያቸው አድርጎ ማውረዱን እንዲያምኑ ግዴታ አድርጓል። እንዲሁም ከመጀመርያቸው እስከ መደምደሚያቸው ነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ድረስ እንዲያምኑም ግዴታ አድርጓል። ምክንያቱም ተልዕኳቸውም አንድ ነው፤ ሃይማኖታቸውም አንድ ነው እርሱም እስልምና ነው፤ የላካቸውም የአለማቱ ብቸኛው አምላክ አላህ ነው። በመሆኑም ሙስሊሙ አላህ በቁርኣን ውስጥ የጠቀሳቸው መልእክተኞች ወዳለፉት ህዝቦቻቸው የተላኩ የአላህ መልእክተኞች መሆናቸውን ማመን እና ሙሐመድም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) መደምደሚያቸው እንዲሁም ወደ ሰዎች ሁሉ የተላኩ የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን ማመን ይጠበቅበታል። በዚህም መሰረት ከነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) መላክ በኋላ ያሉ ሰዎች ሁሉ፣ አይሁዳውያን፣ ክርስቲያኖች እና በሌሎች ሃይማኖቶች ያሉ ሰዎችም ጭምር የሳቸው ህዝብ ናቸው። ምክንያቱም በምድር ላይ ያለ ሰው ሁሉ እርሱን የመከተል ግዴታ ያለበት የነብዩ ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ህዝብ ነው። [47] መላእክቶች፡ የላቀው አላህ ከብርሃን የፈጠራቸው ነፍሶች፤ ከአላህ በቀር ቁጥራቸውን ማንም የማያውቀው እጅግ ብዙ ናቸው። ከእነሱ መካከል ከፊሎቹ በሰማያት ውስጥ አሉ፤ ከነሱም መካከል በሰው ልጆች ላይ ኃላፊነት የተሰጣቸው አሉ። [48] ማለትም ሙስሊሙ አላህ በመልክተኞቹ ላይ ያወረደው መፅሃፍ እውነት መሆኑን፤ ከቁርኣን በቀር ከነሱ ምንም የቀረ ኪታብ እንደሌለ ያምናል። በአይሁዶችና በክርስትያኖች እጅ የሚገኙት ተውራትና ኢንጂልም ቢሆኑ ያለባቸውን መምታታት በመንተራስ የራሳቸው ድርሰት ነው ለማለት ያስደፍረናል። እንዲህም በማለታቸው ምክንያት፡ “አማልክት ሦስት ናቸው፤ ዒሳም የአላህ ልጅ ነው።” በማለታቸው ነው። እውነታው ግን አምላክም አንድ አላህ ብቻ ነው፤ ዒሳም በቁርኣን እንደተገለጸው የአላህ ባርያና መልእክተኛ ነው። በኪታቦቹ ውስጥ የተወሱ የአላህ ቃላትም ቢኖሩ እንኳ በቁርኣን ተሽረዋል። ነቢዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በዑመር (አላህ ሥራቸውን ይውደድላቸው) እጅ ላይ የተውራትን ቃል የያዘች ብጣቂ ወረቀት ባዩ ጊዜ ተቆጥተው እንዲህ ነበር ያሉት፡ "እያመነታህ ነውንዴ ኢብኑል ኸጧብ ሆይ?! በአላህ ይሁንብኝ ወንድሜ ሙሳ በህይወት ቢኖር ኖሮ እኔን ከመከተል በቀር ምንም አማራጭ አይኖረውም ነበር[01]" [02] ከዚያም ዑመር ወረቀቱን ወረወረና እንዲህ አለ: “የአላህ መልእክተኛ ሆይ የአላህን መሀርታ ለምኑልኝ።” አህመድ (3/387) ከጃብር ቢን አብዱላህ ዘግበውታል፤ አልባኒም በአል-ኢርዋእ ኪታባቸው (1589) የሓዲሡ ደረጃው ሓሰን መሆኑን ገልፀዋል። ሙሳ፣ ዒሳም ይሁን ሌሎቹ መልክተኞች በሙሉ መሐመድን - ﷺ - ተከትሎ እስልምናን ከማይቀበል ሁሉ የጠሩ ናቸው። ምክንያቱም ሙስሊም በመልእክተኞች ሁሉ አምኖ የሚከተላቸው ስለሆነ ነው። በሙሐመድ - ﷺ - አምኖ በመከተል ወደ እስልምና ሀይማኖት ያልገባ ሰው አንዳቸውን እንደሚከተል እንኳ ቢሞግት በሁሉም መልክተኞች አስተባብሎ የካደ ካፊር ነው። በርግጥ የዚህ ማስረጃዎችን ቀደም ብለን በምዕራፍ ሁለት ላይ ተመልክተነዋል። የአላህ መልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦
"[01] የሙሐመድ ነፍስ በእጁ ባለችው ጌታ ይሁንብኝ: ከዚህ ሕዝብ የሆነ ማንኛውም አይሁዳዊም ይሁን ክርስቲያን ስለኔ ሰምቶ ከዚያም አላህ እኔን በላከበት ሳያምን አይሞትም የእሳት ሰው ካልሆነ በቀር።"[49]
[49] ሙስሊም (153) እና አህመድ (2/317) ዘግበውታል።
ሙስሊሙም ከሞት በኋላ ባለው ትንሳኤ፣ በስራ መተሳሰብ፣ የስራ ምንዳ፣ ጀነትና ጀሃነም እንዳለ ማመን ግዴታው ነው። በላቀው አላህ ውሳኔ ማመንም እንዲሁ ግዴታው ነው።
በቀደር ማመን ሲባል፡-
አንድ ሙስሊም የላቀው አላህ ሁሉንም ነገር እንደሚያውቅና የባርያዎቹንም ድርጊት ሰማያትንና ምድርን እንኳ ከመፍጠሩ በፊት አዋቂ እንደሆነ፤ ያንኑም እውቀት እርሱ ዘንድ ባለው በለውሐል መሕፉዝ (የተጠበቀው ሰሌዳ) ውስጥ በፅሁፍ እንዳሰፈረው ሊያምን፤ አላህ የፈለገው ነገር እንደሚሆን አላህ የማይፈልገው ነገር ደግሞ እንደማይሆን ሊያውቅ፤ የላቀው አላህ ባሮቹንም እንዲታዘዙት አድርጎ ፈጥሮ ለእነሱም ግልፅ ያደረገላቸው መሆኑን፤ እርሱን ከማመፅም የከለከላቸው እንደሆነ፤ እንዲሁም እርሱን ማምለክ ትእዛዙንም መፈፀም የሚችሉበትን አቅምና ፈቃድም እንደሰጣቸው፤ ለመልካም ስራቸው ውጤትም መልካም ምንዳን እንዳዘጋጀላቸው እርሱን በማመፃቸው ደግሞ ለቅጣቱ እንደሚያጋልጣቸው ግልፅ ማድረጉን ማመን ይገባዋል።
የባርያው ፈቃድ ለአሏህ ፈቃድ ተከታይ ሲሆን አሏህ ለባሮቹ አስቀድሞ ምንም አይነት አማራጭም ይሁን የተለየ ፍላጎት እንዳይኖራቸው አድርጎ ጭራሽ እንደውም ከነርሱ ፍላጎት ውጭ፣ በዝንጋታቸው፣ በስህተታቸውና ተገደው የሚያደርጓቸው የሆኑ እንደ ድህነት፣ ህመም፣ መከራና መሰል አሏህ የወሰናቸውን ጉዳዮች በማስመልከት አሏህ ሰዎችን የሚይዝበትና ለምን ብሎ የሚቀጣበትም ሳይሆን ይልቁን በመከራ፣ ድህነትና ህመም ላይ ታግሶ የአሏህ ውሳኔ መሆኑን አምኖ ለተቀበለ አሏህ ታላቅ ምንዳን የሚመነዳባቸው ናቸው።
ይህ ያስቀደምነው ሁሉ ሙስሊም ሊያምንበት የሚገባው ነው።
ከሙስሊሞች መካከል እጅግ በጣም ኢማን ያላቸው፤ ለአላህ እጅጉን ቅርብ የሆኑትና በጀነት ውስጥም ከፍተኛው ደረጃን የሚጎናጸፉት ሙሕሲኖች (በጎ ሰሪዎች) ናቸው። እነዚያም አላህን የሚያመልኩት፣ የሚያልቁት፤ እንደሚያዩት ሆነው ለአላህ ጥልቅ ፍራቻ ያላቸው፤ በምስጢርም ሆነ በግልጽ የማያምፁት፤ የትም ቢሆኑ እንደሚያያቸው እና ከሥራቸውም፣ ከንግግራቸውም ይሁን ከሐሳባቸው አንዳችም እንደማይደበቅበት የሚያምኑ በመሆናቸው ትእዛዙን ይፈፅማሉ፤ እርሱን ከማመፅም የሚታቀቡ፤ ምናልባት አንዳቸው በስህተት የአላህን መመሪያ እንኳ ቢጥሱ በቅንነት እና በቶሎ ወደ አላህ በተውባ (በንስሀ) በመመለስ ለስህተታቸውምተፀፅተው የአላህን መሀርታ የሚለምኑ ናቸው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{አላህ ከእነዚያ ከሚፈሩትና ከእነዚያም እነሱ መልካም ሠሪዎች ከኾኑት ጋር ነውና።} [አን_ነሕል፡ 128] *** የእስልምና ሀይማኖት ፍፁምነት የላቀው አላህ በተከበረው ቁርአን እንዲህ ብሏል፦ {ዛሬ ሃይማኖታችሁን ለናንተ ሞላሁላችሁ፤ ጸጋዬንም በናንተ ላይ ፈጸምኩ፤ ለእናንተም ኢስላምን ከሃይማኖት በኩል ወደድኩ።}
[አል ማኢዳህ 3]
ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡
{ይህ ቁርኣን ወደዚያች እርሷ ቀጥተኛ ወደ ኾነችው መንገድ ይመራል። እነዚያንም በጎ የሚሠሩትን ምእመናን ለእነሱ ታላቅ ምንዳ ያላቸው መኾኑን ያበስራል።}
[አል-ኢስራእ: 9]
የላቀው ልኡሉ ጌታችን አላህ ስለቁርአን እንዲህ ብሏል፦
{መጽሐፉንም ለሁሉ ነገር አብራሪ፣ መሪም፣ እዝነትም፣ ለሙስሊሞችም አብሳሪ ሆኖ ባንተ ላይ አወረድነው።}
[አን ነሕል 89]
ሶሒሕ በሆነ ሀዲስም ነብዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል፡-
"ሌቷ እንደቀኗ ፍንትው ባለች ጎዳና ላይ ነው በርግጥ የተውኳችሁ፤ ከኔ በኋላ ጥፋ ያለው ካልሆነ በቀር የሚጠፋበት ጎዳናም አይደለም።" [50] የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦ "እስከያዛችኋቸው ድረስ መቼም የማትሳሳቱባቸው ሁለት ነገሮችን ለናንተ ትቸላችኋለሁ። እነሱም የአላህ ኪታብ እና የነብዩ ሱና ናቸው።" [51] አቡዳውድ (4607)፤ በተመሳሳይ መልልኩ ቲርሚዚይ (2676)፤ ኢብኑ ማጃህ (43) ዘግቦታል የተጠቀሰው ቃልም በኢብኑ ማጃህ ዘገባ ያለው ነው፤ ከተሰነ ልዩነት ጋ አሕመድም ዘግቦታል (17142)፤ አልባኒይም በሶሒሕ ኢብኑ ማጃህ (41) ሶሒሕ ብለውታል። ማሊክ(3338)፤ አልባኒይም በ "ሶሒሑል ጃሚዕ" (2937) ሶሒሕ ብለውታል ባሳለፍናቸው አናቅፆች፡- በመጀመሪያ አንቀጽ ላይ የላቀው አላህ ለሙስሊሞች ሃይማኖታቸውን እስልምናን እንዳሟላላቸውና እንከንም እንደሌለው ጭማሪም እንደማያስፈልገው፤ በመሆኑም ለሁሉም ጊዜ፣ ቦታና ሕዝብ ተስማሚ እንደሆነ ነው ያሳወቀን። ለዚህ ታላቅ፣ የተሟላ እና ገራገር ሀይማኖት በመግጠም፤ ሙሐመድንም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) መልዕክተኛው አድርጎ በመላክ፤ እንዲሁም እስልምናን በማላቅ እና ሙስሊሞችን በጠላታቸው ላይ በመርዳት ፀጋውን እንዳሟላላቸው አሳወቀን። እስልምናንም ከሀይማኖት በኩል ለሰዎች የወደደላቸው ሀይማኖት በመሆኑ መቼም የማይቆጣበትና ከእርሱ ውጭ ሌላን የማይቀበልበት ብቸኛ ሀይማኖት መሆኑንም አሳወቀ። በሁለተኛው አንቀፅ ላይ ደግሞ ታላቁ ቁርኣን ለዚች አለም ጉዳዮችም ይሁን ለሀይማኖታዊ ጉዳዮች ትክክለኛ እና ፈዋሽ ማብራርያ የያዘ የተሟላ የህይወት መስመር መሆኑን አሳወቀ። ቁርአን ያመላከተበት ካልሆነ በቀር ምንም አይነት ደግነት፤ ቁርአን ያመላከተበት ካልሆነ በቀር ምንም አይነት ክፋትም የለም። እያንዳንዱ ጉዳይ ይሁም ጣጣ ሁሉ ያረጀ. ይሁን እንግዳ ለወደፊት የሚመጣም ቢሆን ትክክለኛ እና ፍትሀዊ መፍትሄው በቁርዓን ውስጥ ይገኛል። የትኛው መፍትሄ በሚል ስም የቀረበ ሁሉ ቁርኣናዊ መፍትሄ ጋ የሚጣረስ ከሆነ አላዋቂነት እና በደል ብቻ ነው። ስለዚህ እውቀት፣ እምነት፣ ፖለቲካ፣ የአስተዳደርና የፍርድ ስርዓት፣ ስነ ልቦና፣ ማህበራዊነት (sociology)፣ ኢኮኖሚ፣ የወንጀል መቅጫ ስርአት እና ሌሎችም የሰውን ልጅ የሚያስፈልጉት ነገሮች ሁሉ አላህ ባወረደው ቁርኣን እና በላካቸው መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አንደበት በተሟላ መልኩ ያብራራው ነው። ልክ የላቀው አላህ ቀደም ብለን ባወሳነው አንቀፅ ላይ በሚከተለው መልኩ እንዳሳወቀን ማለት ነው፦ ((ወደ አንተም መጽሐፉን ለሁሉም ነገር ገላጭ አድርገን አወረድን)) [አን-ነሕል፡ 89] በሚቀጥለው ምእራፍ የእስልምና ሃይማኖት ፍፁምነት (ሙሉነት) እና አካታች፣ የተሟላና ቅን አካሄድ በዝርዝር አጭር መግለጫ ተሰጥቶበታል። *** ምዕራፍ አራት - የእስልምና ሥርዓተ ትምህርት አንደኛ: በእውቀት ረገድ: አላህ ለሰው ልጅ ከምንም በፊት ቅድሚያ እንዲሰጠው ያስተላለፈለት ትእዛዝ እውቀትን መማር ነው፤ የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {እነሆ ከአላህ ሌላ አምላክ አለመኖሩንም ዕወቅ። ስለ ስህተትህም ለምእመናንም ምሕረትን ለምን። አላህም መዘዋወሪያችሁን፣ መርጊያችሁንም ያውቃል።}
(ሙሐመድ፡ 19)
ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡
{አላህ ከናንተ እነዚያን ያመኑትንና እነዚያንም ዕውቀትን የተሰጡትን በደረጃዎች ከፍ ያደርጋል። አላህም በምትሰሩት ሁሉ ውስጠ ዓዋቂ ነው።}
[አል ሙጃዲላ 11]
አላህ እንዲህ ይላል:
{"ጌታየ ሆይ! እውቀትንም ጨምርልኝ" በል።} [ጧሀ: 114] አላህ እንዲህ ይላል: {የማታውቁ እንደ ኾናችሁ የእውቀት ባለቤቶችን ጠይቁ።}
[አል_አንቢያእ፡ 7]
የመልእክተኞችም መደምደሚያ ሙሐመድ (ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) በትክክለኛ ሐዲስ እንዲህ ብለዋል፡-
"እውቀትን መፈለግ በእያንዳንዱ ሙስሊም ላይ ግዴታ ነው።" [52]
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦
"ዓሊም የሆነ ሰው ዓቢድ ከሆነ ሰው በላይ ያለው ብልጫ ጨረቃዋ ሙሉ በምትሆንበት ቀን ያለችው ጨረቃ ከሌሎቹ ከዋክብቶች አንፃር እንዳላት ብልጫ ነው።" [53]
[52] ኢብኑ ማጃህ (224)፤ ጦበራኒይም በ "ሶጊር" [22] ላይ ዘግበውታል፤ አልባኒይም በ"ሶሒሑል ጃሚዕ" (3808) እና (3809) ላይ ሶሒሕ ብለውታል።
[53] ቲርሚዚይ (2322)፤ ኢብኑ ማጃህ (4112) ላይ ዘግበውታል፤ አልባኒይም በ "ሶሒሑል ጃሚዕ" (1609) ሶሒሕ ብለውታል።
እውቀት በእስልምና ከአስፈላጊነቱ አንፃር የተለያየ ክፍል አለው:
ወንድም ይሁን ሴት በነፍስ ወከፍ ደረጃ በማንኛውም ሰው ላይ ያለ የግዴታ ግዴታ ነው። ማንም ቢሆን ባለማወቁ ይቅርታ የማይደረግለት የሆነው የእውቀት ክፍል ሲሆን ይሀውም የላቀው አላህን እና መልእክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲሁም ከእስልምና ማወቁ በመሰረታዊነት ግዴታ የሚሆነውን ማወቅ ነው። [54]
[54] ይህ ባለፉት ሶስት ምዕራፎች በዝርዝር ተመልክተነዋል።
ክፍል ሁለት፡- በበቂ ሁኔታ የሚፈፅመው ከተገኘ ኃጢያቱ ከሌላው በሚነሳ መልኩ ግዴታ የሆነ (ፈርዶል ኪፋያ)፤ በቀሪው ሰው ላይ የሚበረታታ ብቻ እንጂ ግዴታ አይሆንም። ይሀውም ባለቤቱን ለማስተማር፣ ለዳኝነትና እና ፈትዋ ለመስጠት ብቁ የሚያደርገው የእስልምና ሸሪዓ ድንጋጌዎችን ማወቅ ነው። እንዲሁም ሙስሊሞች ለሕይወታቸው አስፈላጊ የሆኑ የኢንዱስትሪዎች እና ሙያዎች እውቀትን ማወቅም እዚሁ ነው የሚመደበው።
ሁለተኛ፡ በእምነት ረገድ፡-
የላቀው አላህ መልእክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሁሉም የአላህ ባሪያዎች መሆናቸውን እንዲገልጹ አዘዛቸው። ስለዚህም እርሱን ብቻ ማምለክ አለባቸው። አምልኮታቸውም ያለ አማላጅ በቀጥታ ከአላህ ጋር እንዲቆራኙ አዘዛቸው። ይህም ቀደም ብለን “ላ ኢላሃ ኢለሏህ” ምን ማለት እንደሆነ ስናብራራ አሳልፈናል። በአላህ ላይ ብቻ እንዲመኩ ከርሱ በቀር ማንንም እንዳይፈሩ እርሱንም ብቻ እንዲከጅሉ አዘዛቸው። ምክንያቱም ጠቃሚና ጎጂው እርሱ ብቻ ነውና። ልክ ቀደም ብለን እንደገለፅነው አላህ ራሱን በገለፀበትና መልእክተኛውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አላህን በገለፁበት የፍጹምነት ባህሪያት ሊገልጹት ነው።
[55] ለማለት የተፈለገው፡- ይኸውም እንደ ሙታን ባሉ ፍጡራን እና የልዑል አላህ ኃይል በሌላቸው ጣዖታት ዘንድ አይፈራም ተስፋም አይጣልም ለማለት ነው። ነገር ግን ፍጡር ሆነውም የሚያስፈሩ እንደ አንበሳ እና ሌቦች ያሉትን መፍራት ወይም ኃላፊነት የሚሰማቸው እና ለጋስ ያሉ እርዳታ የመስጠት ችሎታ ያላቸው ሰዎች ላይ ተስፋ ማድረግ፤ የማያስወቅሱ ተፈጥሯዊ ፍርሃትና ተስፋ ናቸው።
ሶስተኛ: በሰዎች መካከል ስላለው ቁርኝት:
አላህ ሙስሊሙን የሰውን ልጅ ከክህደት ጨለማ ወደ እስልምና ብርሃን ለማዳን የሚታገል ደግ ሰው እንዲሆን ነው ያዘዘው። ለዚህም ነው ይህንን መጽሐፍ ፅፌ ለማሰራጨት ጥረት ያደረግኩት፤ ከግዴታዎቼ ቢያንስ የተወሰነውን ለመወጣት ስል ነው።
አላህም አንድን ሙስሊም ከሌላው ጋር የሚያስተሳስረውን ቁርኝት በአላህ ላይ ያለ የኢማን ቁርኝት እንዲሆን አደረገ። በመሆኑም አላህንና መልዕክተኛውን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የሚታዘዙ የአላህ ደጋግ ባሮች የፈለገ ሩቅ እንኳ ቢሆኑ ሊወዳቸው ይገባል። አላህንና መልክተኛውን የሚያምፁትን ከሀዲያንን ደግሞ የፈለገ ቅርብ እንኳ ቢሆኑ ሊጠላቸው ይገባል። ይህችው ነች የተበታተኑ ሰዎችን የምታቆራኘውና የተለያዩ ሰዎች የምታስተሳስረው፤ ይህም ዘርን፣ ሀገርን፣ ቁሳዊ ጥቅማ ጥቅምን መሰረት አድርጎ ከተመሰረተውና ቶሎ ከሚፈርሰው የቁርኝት አይነት በተለየ መልኩ ነው። ሁሉን ቻይ አላህ አለ: {በአላህና በመጨረሻው ቀን የሚያምኑትን ሕዝቦች አላህንና መልክተኛውን የሚከራከሩትን ሰዎች፤ አባቶቻቸው፣ ወይም ልጆቻቸው፣ ወይም ወንድሞቻቸው፣ ወይም ዘመዶቻቸው ቢኾኑም እንኳ የሚወዳጁ ኾነው አታገኛቸውም፡፡} [አል_ሙጃዲላ፡ 22] ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡ {አላህ ዘንድ የተወደደው ሀይማኖት እስልምና ነው።} [አል-ሑጁራት፥13] ጥራት የተገባውና የላቀው አላህ በመጀመርያው አንቀፅ እያለን ያለው፡ በአላህ የሚያምን አማኝ የአላህ ጠላቶችን ከሰዎች መካከል እጅግ በጣም ቅርብ ቢሆኑም እንኳ አይወዳቸውም።
ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ በሁለተኛው አንቀፅ እያለን ያለው ደግሞ፡ ከሚያከብራቸው ሰዎች መካከል እርሱ ዘንድ እጅግ የተከበረው ከየትኛውም ዘር እና ቀለምም እጅግ አላህን የሚታዘዘው ነው።
የላቀው አላህ ከጠላትም ሆነ ከወዳጅም ጋር ፍትህን አዝዟል። በራሱ ላይ በደልን እርም አድርጎ በባሮቹም መካከል እርም አደረገው። ይልቁንም መተማመንንና እውነተኝነትን አዘዘ። ተንኮልንም ክልክል አድርጎ ወላጆችን ማክበርን፣ ዝምድናን መቀጠል፣ ለድሆች በጎ መዋልንም፣ በበጎ አድራጎት ሥራ መሳተፍን አዟል። ለእንስሶች እንኳ ሳይቀር ለሁሉም በጎ ማድረግ አዘዘ፤ ማሠቃየትን ሓራም አድርጎ መልካም ነገር እንድናደርግ አዞናል።[56] ይሁን እንጅ እንደተናካሽ ውሻ፣[57] እባብ፣ ጊንጥ፣ አይጥ ፣ ጭልፊት እና እስስት ያሉ ጎጂ እንስሶች ከክፋታቸው ለመዳን ሲባል ይገደላሉ። ይሁን እንጅ ማሰቃየት አይፈቀድም።
(56) ለማረድ የተፈቀደን እንስሳ እንኳን በሚታረድበት ጊዜ ቢላዋው እንዲሳል እና የሚታረደውን ቶሎ እረፍት የሚሰጥ መሆን እንዳለበት የአላህ መልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አዘዋል። የሚታረድበት ቦታም ጉሮሮው ነው። ደሙ እስኪወጣ ድረስ ጉሮሮውን እና የደምስሮቹን ይቆርጣል። ግመሎችም አንገት ስር በመውጋት ነው የሚታረዱት። ነገር ግን በኤሌክትሪክ ኃይል ወይም ጭንቅላት በመምታት እና መሰል በሆነ መልኩ መግደል ግን የተከለከለ ነው። (በተከለከለ መልኩ የታረደን) መብላቱም አይፈቀድም።
[57] ይህ ሰዎችን የሚጎዳ አረመኔ ውሻ ነው። በዚህም መሰረት ሁሉንም የዱር እና ጎጂ አራዊትም በዚሁ ይጠቃለላሉ።
አራተኛ፡ ለአማኝ ሰው አላህ እንደሚያየውና እንዲሁም ልባዊ መካሪም እንዳለው፡-
የታላቁ ቁርኣን አንቀጾች አላህ ሰዎችን በያሉበት ሁሉ እንደሚመለከታቸው እና ስራቸውን ሁሉ እና ሀሳባቸውንም እንደሚያውቅ እና ስራቸውንና ንግግራቸውን እንደሚቆጥርላቸው እና መላእክቶቹም ከእነሱ ጋር ሆነው ሰዎች በድብቅም ይሁን በግልጽ የሚያደርጉትን ሁሉ የሚመዝግቡ መሆናቸውንም ይገልፃሉ። አላህም በሚሠሩትና በሚናገሩት ነገር ሁሉ እንደሚጠይቃቸው፤ በቅርቢቱ ሕይወት ሰዎች ቢያምፁት ትእዛዙንም ቢጥሱ አሳማሚ ቅጣቱንም እንደሚቀጣቸው ግልፅ አድርገዋል። ይህም በአላህ ለሚያምን ሁሉ እርሱን ከማመፅ እንዲታቀቡ የሚያደርግ ታላቅ ማስጠንቀቂያ ይሆነዋል። በዚህም ምክንያት የላቀውን አላህ ፍራቻ ወንጀልን ከመዳፈር ይታቀባሉ።
አላህን የማይፈራና ኃጢአትን መሥራት በቻለ ጊዜ ሁሉ ኃጢአትን የሚሠራ ሰው ገና በቅርቢቱ ሕይወት ሳለ የሚገታው የሆነን ወሰን ያደርግለታል። ይሀውም አላህ ሙስሊሞችን በመልካም እንዲያዝዙ ከመጥፎም እንዲከለከሉ አዟል። ማንኛውም ሙስሊም ሌላ ሰው ሲሰራ ላየው ኃጢአት እንዳይሰራ በእጁ መከልከል ካልቻለ በምላሱ እስከሚከለክለው ድረስ በአላህ ፊት ተጠያቂ እንደሆነ ይሰማዋል። አላህም የሙስሊሞችን አሚር [58] መመሪያውን ለሚጥሱ አምላካዊ ፍርድ (ሓድ) እንዲያቆሙባቸው አዟል። ይሀውም ወንጀል ፈፃሚውን ጋር ተመጣጣኝ የሆነ ቅጣት ነው። ይህም የላቀው አላህ በቁርኣን የአላህ መልእክተኛም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በሐዲስ ያብራሩት ሲሆን ወንጀለኞችም ላይ እንደፈፀም አዘዋል። በዚህም ነው ፍትህን፣ ደህንነትን እና ብልጽግናን ማረጋገጥ የሚቻለው።
[58] ማለትም አስተዳደርና መሪው ለማለት ነው።
አምስተኛ: በመስተጋብራዊነት እና በህበረተሰባዊ ትብብር ረገድ:
ቀደም ሲል በዘካ እና ምጽዋት ምዕራፍም ላይ እንደተገለጸው አሏህ ሙስሊሞችን በቁሳቁስም ይሁን በአገልግሎት እንዲተባበሩ አዟል። ብሎም የላቀው አሏህ በየትኛውም መልኩ ሙስሊምን ማስቸገርን ከልክሏል። በመንገድ ዳር ባለ ነገር እንኳ ሙስሊምን ማስቸገር እርም ያደረገው ነገር ነው። ሙስሊሙም ቢሆን ያየውን አስቸጋሪ ነገር በሌላ ሰው የተደረገ ቢሆን እንኳ እስካየው ድረስ እንዲያስወግድ አዞታል። በዚህም በጎ ላደረገው መልካም ምንዳን እንደሚመነዳው ቃል ገባለት፤ ልክ ለጥፋተኛው በቅጣት እንደዛተበት ሁሉ ማለት ነው።
አላህ ሙእሚን የሆነ ሰው ለራሱ የሚወደውን ለወንድሙም እንዲወድ ለራሱ የሚጠላውንም ለወንድሙም እንዲጠላ አዟል። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፡-
{በበጎ ነገርና አላህን በመፍራትም ተረዳዱ። ግን በኃጢአትና ወሰንን በማለፍ አትረዳዱ። አላህንም ፍሩ። አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና።}
[አል-ማኢዳህ: 2]
አላህ እንዲህ ይላል:
{ ምእመናኖች ወንድማመቾች ናቸው፡፡ በሁለት ወንድሞቻችሁም መካከል አስታርቁ፡፡ ይታዘንላችሁም ዘንድ አላህን ፍሩ።}
[አል_ሑጁራት፡ 10]
አላህ እንዲህ ይላል:
{ከውይይታቸው በምጽዋት ወይም በበጎ ሥራ ወይም በሰዎች መካከል በማስታረቅ ከሚያዙ ሰዎች ውይይት በስተቀር በብዙው ውስጥ ደግ ነገር የለበትም። ይኸንንም (የተባለውን) የአላህን ውዴታ ለመፈለግ የሚሠራ ሰው ታላቅ ምንዳን እንሰጠዋለን።}
[አን-ኒሳእ: 114]
የአላህ መልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦ "አንዳችሁም ለራሱ የሚወደውን ለወንድሙ እስካልወደደ ድረስ እምነቱ አልተሟላም።" [59] እርሳቸውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በሕይወታቸው መጨረሻ ላይ በመሰናበቻው የሐጅ ጉዞ ወቅት ባደረጉት ታላቁ ኹጥባቸው [60] እንደተናገሩት፣ ከዚህ ቀደም ያስተላለፉትን ትእዛዝ በማጠናከር እንዲህ ብለዋል፡-
"ሰዎች ሆይ! ጌታችሁ አንድ ነው። አባታችሁም አንድ ነው። አረቦችም አረብ ካልሆኑት አረብ ያልሆኑትም ከአረቦች፤ ቀዩ ከጥቁሩ ወይም ጥቁሩም ከቀዩ አላህን በመፍራት ካልሆነ አይበላለጡም።" አሉና "ተልእኮየን አድሻለሁን?" በማለት ጥያቄያቸውን አስከተሉ፤ ሶሓቦችም 'በርግጥም አድርሰዋል የአላህ መልዕክተኛ ሆይ!" በማለት መለሱ። [61]
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህም ብለዋል፦
"ጌታችሁን እስክትገናኙ ድረስ ደማቸሁም ንብረታችሁም እንዲሁም ክብራችሁ ልክ እንደዚህ ወር እንደ ዛሬው ቀን እንደዚሁ ሀገር የተከበረ እርም ነው። (መልእክቱን) አላስተላለፍኩምን?" ሲሉ፡- ሱሓቦችም “አዎ” ብለው መለሱላቸው። እሳቸውም እጃቸውን ወደላይ ከፍ አድረገው፡- ‘አላህ ሆይ! መስክር’ አሉ።" [62]
[59] ቡኻሪይ (13)፤ ሙስሊም (45)፤ ቃሉ በሙስሊም ዘገባ ላይ ያለው ነው።
[60] እነዚህ የነብዩ ( ﷺ) ሓዲሦች በተሰባሰቡባቸው ኪታቦች ውስጥ ተበታትነው የሚገኙ ጥቅል መልእክት ያላቸው ሓዲሦች ናቸው።
[61] አሕመድ (22978) ዘግበውታል፤ አልባኒይም በ "ሲልሲለቱ ሶሒሓ" (6/199) ሶሒሕ ብለውታል
[62] ቡኻሪይ (105)፤ ሙስሊም (1718)፤ ቃሉ የቡኻሪይ ዘገባ ላይ ያለው ነው።
ስድስተኛ፡ በሀገር ውስጥ ፖለቲካ ረገድ፡-
አላህ ሙስሊሞችን በአሚርነት ላይ ቃል ኪዳን ገብተውለት የሚመራቸው መሪ እንዲሾሙ አዟቸዋል። አንድ ህዝብ ይሆኑ ዘንድ እንዲሰበሰቡና እንዳይለያዩም አዟቸዋል። አላህም ኢማማቸውን እና መሪዎቻቸውን አላህን በማመፅ ላይ እስካላዘዙ ድረስ እንዲታዘዟቸው አዟል። ምክንያቱም ፈጣሪን በማመፅ ላይ ለፍጡር መታዘዝ የለምና።
አላህ አንድ ሙስሊሙ የእስልምና ሀይማኖትን በግልጽ ለመፈፀም፣ ወደ እስልምና ጥሪ ለማድረግ በማይችልበት ሀገር ውስጥ ከሆነ ወደ ሙስሊም ሀገራት እንዲሰደድ አዞታል።[63] ማለትም ጉዳዮች ሁሉ በእስልምና ህግ የሚዳኙበት እና አንድ ሙስሊም መሪ አላህ ባወረደው መመሪያ የሚገዛበት ሀገር ነው።
[63] አዞታል ስንል የሚችል ከሆነ ማለታችን ነው።
እስልምና የክልል ድንበሮችን ወይም ሀገራዊ አልያም ህዝባዊም ይሁን ብሄራዊ ዳርድንበሮችን እውቅና አይሰጥም። ይልቁንም የሙስሊም ዜግነቱ እስልምና ነው፤ ባርያዎቹ ሁሉም የአላህ ባሪያዎች ናቸው፤ ምድሪቱም ሙስሊም ያለምንም ተቃውሞ የሚንቀሳቀስባት የአላህ ምድር ነች። ይህ የሚሆነው ግን አንድ ሙስሊም የአላህን የሙጥኝ ብሎ አጥብቆ እስከያዘ ድረስ ነው። ባንዳች ነገር ተቃርኖ ከተገኘ ግን በአላህ ፍርድ ይፈረድበታል። የአላህ ህግ (ሸሪዓ) እውን ሆኖ ተግባራዊ ቢደረግና ፍርዱም ቢተገበር [64] የሰዎችን ሰላም እና መረጋጋት ማስፈን ይኖር ነበር፤ ደማቸውም በከንቱ አይፈስም ክብራቸውም በከንቱ አይዘለፍም፤ ሀብታቸውን እና መልካም ነገራቸውን ሁሉ ማረጋገጥ በተቻለ ነበር። ልክ ከመመርያዋ መዛነፍም ክፋትን ሁሉ ሰብስባ እንደያዘችው ማለት ነው።
[64] “ሓድ” ወይም “ሑዱድ” ማለት በእስልምና ህግ የተወሰኑ ወንጀሎችን ለፈጸሙ ሰዎች የተወሰኑ ቅጣቶች ናቸው።
አላህ ለአእምሮም ጥበቃ አድርጓል: ይኸውም አስካሪዎችን፣ አደንዛዥ እጾችን እና አነቃቂ ንጥረ ነገሮችን[65] በመከልከል፤ እንዲሁም አስካሪ መጠጥ ለሚወስዱ ሰዎችም “ሓድ” ይሀውም ይህንን ባደረገ ቁጥር (40-80) ግርፋትን የመግረፍ ፍርድን በማበጀት፤ ይህንንም ያደረገው ሰውየውንም ለማዳን፣ አእምሮውንም ለመጠበቅ እና ሰዎችንም ከክፋቱ ለመታደግ ነው። [65] አነቃቂ ንጥረ ነገሮች የሰውነት፣ የአእምሮም የነርቭም መድከም እና መዛል የሚያስከትሉ ንጥረ ነገሮች ናቸው። የላቀው አላህ የሙስሊሞችን ደም ጥበቃ አድርጎለታል: ይህም ፍትሃዊ ያልሆነውን ድንበር አላፊ በስራው ልክ በመቅጣት ነው። ስለዚህም ነፍሰ ገዳይ ይገደላል፤ የቁስሎች መመሳሰል (አይን ላጠፋ አይኑ ይጠፋል) አይነት ህግ የተደነገገ ነው። ልክ ሙስሊሙ ከራሱ፣ ከክብሩና ከገንዘቡ እንዲከላከል የተደነገገ እንደሆነው ሁሉ። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ለእናንተም ባለ አእምሮዎች ሆይ! በማመሳሰል (ሕግ) ውስጥ ሕይወት አላችሁ። ትጠነቀቁ ዘንድ (ገዳይን መግደል ተደነገገላችሁ)።} የአላህ መልዕክተኛ ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም እንዲህ ብለዋል: "ለሀብቱ ሲል የተገደለ ሰው ሰማዕት ነው፤ ለሃይማኖቱ ሲል የተገደለም ሰማዕት ነው፤ ለደሙ ሲል የተገደለም ሰማዕት ነው፤ ለቤተሰቡ ሲል የተገደለም ሰማዕት ነው።" [66] [66] አቡዳውድ (2/275)፤ ነሳኢይ (2/316)፤ አሕመድ (1652) ዘግበውታል፤ አልባኒይም በ "ሶሒሕ ተርጊብ ወተርሂብ" (1411) እና በ "ሶሒሑል ጃሚዕ" (4172) ሶሒሕ ብለውታል።
አላህ የሙስሊሞችንም ክብር ጥበቃ አድርጎለታል: ተገቢ በሆነ መልኩ ካልሆነ በቀር አንድን ሙስሊም በሚጣላው ነገር ስሙን ከማንሳት ከማማት በመከልከል እና ሙስሊምን ስነ ምግባራዊ እንከንን በሚገልፅ ወንጀል ለሚዘልፍ ስም አጥፊ “ሓድ” ደንግጓል፤ ለምሳሌ፡ ሸሪዓዊ በሆነ ማስረጃ ማረጋገጥ በማይችልበት መልኩ በዝሙት እና በሰዶማዊነት ሰውን መዝለፍ።
አላህ የዘር ሐረግ በሕገወጥ መልኩ ከመቀላቀል ጥበቃ አድርጎለታል [67]። የሰዎችንም ክብር በሥነ ምግባራዊ ጉድለት እንዳይጠለሽ ዝሙትን ሓራም በማድረግ ብሎም ከከባባድ ኃጢአቶች በመቁጠር ጥበቃ አድርጎለታል። ዝሙት በሚፈፅም ሰው ላይም በቂ ቅድመ ሁኔታዎች ከተሟሉ አጥፊውን የሚያግድ ቅጣት አድርጓል።
(67) አላህ ዘሮች ከመጥፋታቸውና ከመቀላቀላቸውም ጠበቃቸው። ሰው በዝሙት ምክንያት ከአባቱ ውጭ በሌላ ሰው ይጠራም ነበር።
አሏህ የሰው ገንዘቡንም ጥበቃ አድርጎለታል: ስርቆትን፣ ማጭበርበርን፣ ቁማርን፣ ጉቦን እና ሌሎች የተከለከሉ መጣቀሚያዎችን ሓራም በማድረግ፤ ሌባና ወንበዴ ላይም ባደረገው ከባድ ቅጣት፤ ይሀውም ቅድመ ሁኔታዎቹ ከተሟሉ (የተፈረደበት አካሉ) እንዲቆረጥ ወይም በቂ ቅድመ ሁኔታዎቹ ካልተሟሉ ደግሞ ሌላ ሊገታው የሚችልን ከባድ ቅጣት በማድረግ የሰውን ገንዘብ ጥበቃ አድርጎለታል። እነዚህን የመሰሉ “ሑዱድ” የደነገገው ዐዋቂ ጥበበኛ የሆነው አላህ ነው። እርሱም ፍጥረታቱ የሚስተካከልበትን ሁኔታ ይበልጥ ዐዋቂው ነው፤ እርሱም ይበልጥ አዛኙም ነው። እነዚህን የ“ሓድ” ቅጣቶችን የሙስሊም ወንጀለኞችን ኃጢአታቸውን የሚያሰርዙበት (መሀርታን የሚያገኙበት) እና ለህብረተሰቡ ደግሞ ከወንጀሎኞቹም ይሁን ከሌላው ክፋት የሚታደጉበት አደረገላቸው። የገዳይን መገደል እና የሌባን እጅ መቁረጥ የሚያወግዙት የእስልምና ጠላቶች እና አስመሳዮች እያወገዙ ያሉት ካልተቆረጠ በሽታው ወደ መላው ማህበረሰብ ሊዛመት በሚችል ህመም የተለከፈን የሰውነት አካል መቁረጥን ነው።[68] የሚገርመው ደሞ በተመሳሳይ ጊዜ ንጹሃን ሰዎችን ለግፍ ዓላማቸው ብለው መግደልን የሚቀበል ህሊና ያላቸው መሆናቸው ነው።
[68] ይህ የጠቀስነው ጉዳይ አንድ በሽተኛ ለአካሉ ደህንነት ሲባል የታመመውንና የበሰበሰ አካሉን በሽተኛውም ቤተሰቡም ፈቅደው በራሱ ምርጫ ከሚቆረጠው የተሻለ ምክንያታዊነት ነው።
ሰባተኛ: በውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ረገድ:
አላህ ሙስሊሞችን እና የጉዳይ ባለቤቶቹም (የሀገር መሪዎች) ሙስሊም ያልሆኑትን ወደ እስልምና እንዲጋብዙ አዟል። በእነርሱ በኩል ከክህደት ጨለማ ወደ አላህ የእምነት ብርሃን እንዲድኑ፤ እና በዚህ አለማዊ ህይወት ቁሳዊ አረንቋ ከመስመጥ እና ሙስሊሞች ብቻ በእውነት የሚያገኙት ከሆነው መንፈሳዊ ደስታ ከመነፈግ እንዲድኑ ሲባል ነው። ስለዚህም አላህ ለሙስሊሙ ያዘዘው ይሀው ትእዛዝ የሰው ልጅ ሁሉ ሁሉንም ሰው በመልካምነቱ የሚጠቅም እንዲሆን የሚያደርግ መመርያ ነው። ይህም ሰው ሰራሽ ከሆኑ መመርያዎች በተለየ መልኩ ነው፤ ጥረታቸው ጥሩ ዜጋ ከማፍራት የዘለለ አይደለምና። ይህ ደግሞ መመርያቸው ብልሹ እና ጎዶሎ ለመሆኑ እስልምና ደሞ የተስተካከለ እና ፍጹም ለመሆኑ ማሳያ ነው።
አላህ ሙስሊሞችን እስልምናንና ሙስሊሞችንም ለመጠበቅ እና የአላህን ጠላትና ጠላቶቻቸውንም ፊት ላለመስጠት በቻሉት አቅም ልክ ለአላህ ጠላቶች እንዲዘጋጁ አዘዛቸው። ልክ ጉዳዩ በእስልምና ህግ እይታ አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ሙስሊሞች ከእስልምና ውጭ ከሆኑ ሰዎች ጋር ቃል ኪዳን ቢያስሩም እንደፈቀደው ሁሉ ማለት ነው። በዚህም መሰረት ጠላቶቻቸው የገቡትን ቃል ኪዳን ማፍረስ ካልጀመሩ ወይም ቃል ኪዳኑን ለማፍረስ ግድ የሚያስብል ነገር በመፈፀማቸው ቃልኪዳናቸው ካልፈረሰ በቀር ሙስሊሞች የገቡትን ቃል ኪዳን ማፍረስም ክልክል ተደርጎባቸዋል። (ተገቢ የሆነ ጦርነት ቢደረግ እንኳ) ሙስሊም ካልሆኑት ጋር ጦርነቱን ከመጀመራቸው በፊት አላህ ጠላቶቻቸውን እስልምናን ይቀበሉ ዘንድ ጥሪ አንዲያደርጉላቸው ሙስሊሞችን አዘዛቸው። አሻፈረን ብለው ካመፁ ለአላህ ህግ እንዲያጎበድዱና[69] “ጂዝያ” እንዲከፍሉም ይጠይቋቸዋል፤ በእምቢተኝነታቸው ከፀኑ ያኔ “ፊትናም” [70] እስኪወገድና ሀይማኖትም ሁሉ ለአላህ እስኪሆን ድረስ መጋደል ግድ የሚል ይሆናል። [69] በእስልምና አስተዳደር ስር ያሉ ሙስሊሞች ዘካ እንደሚሰጡት ሁሉ ሙስሊም ያልሆኑት ደግሞ ጂዝያ ይከፍላሉ። = ይሀውም ከአዋቂ ወንዶች የሚወሰድ የተወሰነ የገንዘብ መጠን ሲሆን ለሴቶች፣ ለህጻናት፣ ለእብዶች፣ ለአዛውንቶችና ለድሆች ተብሎ ግን አይከፈልም። “ጂዝያ” እጅግ በጣም ጥቂት የገንዘብ መጠን ሲሆን በነብዩ ﷺጊዜ በየአመቱ አንድ ዲናር ነው የነበረው፤ ይህም ሀብታም በአመት አንዴ ጣል የሚያደርገው እጅግ በጣም ትንሽ የገንዘብ መጠን ነው። ይህም በእስልምና መንግሥት ጥበቃ ሥር ሆነው ለሚያገኙት ደህንነቱ የተጠበቀ ኑሯቸው፤ አጠቃላይ የህይወት እንቅስቃሴያቸውና በእስልምና የተፈቀዱ የስራ ዘርፎችን ሰርተው ለሚያገኙት ሲሳይ፤ ደህንነቱ ለተረጋጋ ሰላም፤ ለነሱም፣ ለገንዘባቸውና ለክብራቸውም ከሙስሊሞች በኩል ለሚደረግላቸው ጥበቃ ሲባል የሚከፍሉት ነው። ይህ ሁሉ ታዲያ ለቤተክርስቲያናቸውና ለሃይማኖታቸው ከሚደረግላቸው ጥበቃ በተጨማሪ ነው። ሙስሊሞቹ ሙስሊም ላልሆኑት መብታቸውን ማስከበር ቢያቅታቸውና ከጠላታቸው ቢሳናቸው ሙስሊም ላልሆኑት ያ “ጂዝያ” ገንዘባቸውን ይመልሱላቸዋል። “ጂዝያ” የሰጡበት ቅድመ መስፈርት አልተሟላላቸውምና። ይህም ቅድመ መስፈርት ጥበቃ ሊደረግላቸው ነበር። ይሁን እንጅ ሙስሊም ያልሆኑት ሰዎች ሙስሊሞቹ ሀገራቸውን ከጠላት ሲከላከሉ አብረው ተሳትፎ ካደረጉ ሙስሊሞቹም ጂዝያ የመክፈል ግዴታቸውን ያነሱላቸዋል። የሀገሪቱ አስተዳደርም በሀገሪቱ ያሉ ሙስሊም ያለሆኑ ድሆችም እንደሙስሊሙ እገዛና እንክብካቤ ያደርግላቸዋል። [70] “ፊትና” የሚሆነው ሰዎች እስልምናን እንዳይደርሳቸው በማድረግ እና ወደ እስልምና ለመግባት ማንም ሳያስገድዳቸው መግባት ለሚፈልጉ ሰዎች ነፃነታቸውን በመንፈግ ነው። [ልብ በል: ጂሀድ የሚኖረው ይህ የተባለው “ፊትና” ሲከሰት ነው።] በትግል ጊዜ አሏህ ሕፃናትን፣ ሴቶችን፣ አረጋውያንን እና በቤተ መቅደሳቸው ውስጥ ያሉ መነኮሳትን መግደልን ሙስሊሞችን ከልክሏቸዋል። ምናልባት ከአመፀኞቹ ጋር በሐሳብ ወይም በድርጊት አስተዋፅኦ ያበረከተ ካልሆነ በስተቀር (አስተዋፅኦ ካለው በአስተዋፅኦው ልክ የሚገባውን ይሰጠዋል።) ምርኮኞችንም በበጎ ሁኔታ እንዲይዙ አዘዛቸው። በዚህም መሰረት የሙስሊሞች ዘመቻ አላማ አምባገነንነትና ስልጣንን መቆናጠጥ አለመሆኑን እንረዳለን። ይልቁን እውነትን ማሰራጨትና ለፍጡራን ማዘን እንዲሁም የሰው ልጆች ፍጡራንን ከሚያመልኩበት የጨለማ ማጥ ፈጣሪን ብቻ ወደ ሚያመልኩበት ማውጣት ነው።
ስምንተኛ: በነጻነት ረገድ፡- (ሀ) የእምነት ነፃነት፡- በእስልምና ሀይማኖት ውስጥ የላቀው አሏህ በእስልምና አገዛዝ ስር ለሚኖሩ እስልምና ከተብራራላቸውና ወደ እስልምናም ጥሪ ከተደረገላቸው በኃላ ሙስሊም ላልሆኑ ሰዎች የእምነት ነፃነትን ሰጥቷቸዋል። እስልምናን መቀበልን ቢመርጥ ስኬቱም ሆነ መዳኑ ለራሱ ነው። በነበረበት ሀይማኖት ቢቀጥል ደግሞ ክህደቱም፣ እድለቢስነቱም፣ ስቃዩም ይሁን የእሳት ቅጣቱ ለራሱ ነው። በዚህም በቂ የሆነ ማስረጃ ስለተደረገለት አሏህ ፊት እስልምናን ላለመቀበሉ ማምለጫ ሰበብ የለውም። ያኔ ሙስሊሞችም አንድ ቅድመ ሁኔታ አድርገው በእምነቱ ላይ እንዳለ ይተውታል። ይህም የተዋረደ ሆኖ “ጂዝያ”ን ሊከፍል፣ ለእስልምና ህግጋትም ሊያጎበድድ፣ በሙስሊሞች ፊትም የክህደት መገለጫውን ይፋ ላያደርግ ነው።
ሙስሊሙን በተመለከተ እስልምና ከገባ በኋላ ክህደት ከሱ (ሊያኗኑር የሚችል) ተቀባይነት አይኖረውም። ከካደም ቅጣቱ ሞት ነው። ምክንያቱም እውነትን በሚገባ ካወቀ በኋላ በመካዱ ለመቆየት የማይመች ሆኗል። ምናልባት ግን በተውባ ወደ አላህ በመመለስ እስልምናን ካልያዘ በቀር። [ 71]
[71] ከእምነት በኃላ ክህደት፡ ማለት እስልምናን በክህደት መተው ነው። እስልምናን በፅኑ እምነት የመረጠ ማንም ሰው ያንን አያደርግም፣ የትኛውንም ሀይማኖትም ሆነ ስልጣኔም ከእስልምናው አያስቀድምም። ምክንያቱም የትኛውም ስልጣኔ የእስልምናን ፍፁምነትና ተአምራዊነቱን ስለማይደርስ ነው። እናም ከእምነት በኃላ ክህደት ካሉት ፋናዎች መካከል በሙስሊሙ ማህበረሰብ ውስጥ ሁከትን መቀስቀስና ወደ ክህደት መገፋፋት ወይም ስሜትንና ቁሳዊነትን ማህበራዊ ጥቅማ ጥቅምን ማሳደድ ነው። ታዲያ በዚህ መልኩ ከእስልምና መውጣት ከታላቁና እጅግ አንገብጋቢው መለኮታዊ ቃል ኪዳን መውጣት ነው። ይህም በዛሬ ጊዜ በአብዛኞቹ አገሮች በአገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛው ወንጀል የአገር ክህደት ወንጀል መሆኑና ለዚህም ቅጣቱ የሞት ፍርድ ከመደረጉ ጋር ተመሳሳይ ነው። እናም በዚህ መሠረት ከሃዲውም እንዲሁ የሱን ጦስ ከማህበረሰቡ ማስወገድ የሚቻለው ወንጀለኛው በሞት ፍርድ ቅጣት በመንቀል ብቻ እስከሚሆንበት ደረጃ በመድረሱ ነው። ይሁን እንጅ በእስልምና ህግ መሰረት የከሀዲውን ሁኔታም ይሁን የተጣለበትን ፍርድ የማፅደቁ ነገር በአስተዳዳሪው እጅ ብቻ ያለ ጉዳይ ነው። ከእምነት በኃላ ክህደት የተጠረጠረውንም በግፍ ላለመበደል የሙስሊሙን ማህበረሰብ ሃይማኖትንም ለመጠበቅ ሲባል በተቀመጡ ረቂቅ የሆኑ እርምጃዎችን መሰረት በማድረግ ነው ፍርዱ የሚፀናበት።
ክህደቱም እስልምናን ከሚያፈርሱ ነገሮች መካከል አንዱን በመፈፀም ከሆነ ነገሩን በመተው፣ በመጥላት እና ከላቀው አላህ ምህረትን በመጠየቅ ከዚያ አጥፊ ተውባ አድርጎ መመለስ ይችላል።
እስልምናን የሚያፈርሱ ብዙ ናቸው። በጣም የሚታወቁት ግን፦ በአላህ ማጋራት፦ ይህም ሲባል አንድ ሰው እንደ መቃረቢያ አድርጎ የሚማፀነውና መቃረቢያ የሚያደግለት ወደ አላህ እንዲያቃርበኝ በሚል ሰበብ ቢሆንም እንኳ ከአላህ ሌላ አምላክ አድርጎ መያዝ ነው። ሲያሻው የአምላክነትና የአምልኮ ፅንሰ ሀሳብን በመረዳቱ በቀጥታ በስሙም በእውነታውም አምላክ ብሎ እየጠራ ልክ እንደ ጃሂሊያዎቹ አጋሪዎች ወደ አላህ ያቃርቡን ዘንድ ከምስሉ ጀርባ ላሉት ደጋግ ሰዎች ነው የምናመልከው እንደሚሉት ሆኖ እያወቀ ያምልከው፤ አለዚያም ደግሞ ከአላህ ጋር ማምለክ መሆኑን ሳይረዳ ባእድ አምልኮ መሆኑንም ሳያውቅ ልክ በሙስሊሙ መካከል ሆነው በአላህ እንደሚያጋሩት እና አላህን ብቻ እንዲያመልኩ ጥሪ ሲደረግላቸውም ሽርክ የሚሆነው ለጣኦት ስትሰግድ ብቻ ወይንም ከአላህ ውጭ ላለ አካል አምላኬ ነው ስትል ነው እያሉ ሽርክ እንደሚፈፅሙት አይነቱ ሳያውቅም ያጋራ ሽርክ ነው። እነሱ ማለት ልክ አስካሪ መጠጥ እየጠጣ አስካሪ መጠጡን በሌላ ስም እንደሚጠራው አይነት ሰው ናቸው። ሁኔታቸውን በማስመልከት ቀደም ብለን ማብራርያ አሳልፈናል። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{አላህንም ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ ያጠራህ ሆነህ ተገዛው።} (2)
{ንቁ! ፍጹም ጥሩ የኾነው ሃይማኖት የአላህ ብቻ ነው። እነዚያም ከእርሱ ሌላ (ጣዖታትን) ረዳቶች የያዙት «ወደ አላህ ማቃረብን እንዲያቀርቡን እንጅ ለሌላ አንገዛቸውም» (ይላሉ)። አላህ በዚያ እነርሱ በእርሱ በሚለያዩበት ነገር በመካከላቸው ይፈርዳል። አላህ እርሱ ውሸታም ከሓዲ የኾነን ሰው አያቀናም።} (3)
[አዝ_ዙመር፡ 2_3]
ከፍ ያለው አሏህ እንዲህ ብሏል፡
{ይህ ጌታችሁ አላህ ነው። ንግሥናው የእርሱ ብቻ ነው። እነዚያም ከእርሱ ሌላ የምትግገዟቸው የተምር ፍሬ ሽፋን እንኳ አይኖራቸውም።} (13) {ብትጠሩዋቸው ጥሪያችሁን አይሰሙም። ቢሰሙም ኖሮ ለእናንተ አይመልሱላችሁም። በትንሣኤም ቀን (እነርሱን በአላህ) ማጋራታችሁን ይክዳሉ። እንደ ውስጠ ዐዋቂው ማንም አይነግርህም።} [ፋጢር፡ 13_14] 1_ እንደ ሙሽሪኮች ላሉም ይሁን እንደ አይሁድና ክርስትያኖች፤ አምላክ የለም ባዮችና እሳት አምላኪዎች እንዲሁም ጣኦት አምላኪዎች ያሉ ሌሎችም አላህ ካወረደው ውጭ በሆነ ህግ የሚፋረዱ፣ የአላህን ህግ ወደው የማይቀበሉ ከሃዲያን አላህ ከሃዲያን መሆናቸውን አውጆ ሳለ ከሀዲያን መሆናቸውን ያልተቀበለ እሱ ራሱ ከሀዲ ሆኗል። 2_ ትልቁን ሽርክ የሚያስከትል ድግምት ኩፍር መሆኑን ካወቀ በኋላ የሰራም ይሁን መሰራቱን የወደደ ካፊር ነው። 3_ ከእስልምና ውጭ የሆነ የትኛውም ስርአት ወይንም ሀይማኖት ከእስልምና የተሻለ እንደሆነ፤ ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ይዘውት ከመጡት ፍርድ ሌላ የተሻለ ፍርድ እንዳለ፤ ወይም አላህ ካወረደው ውጭ በሆነ ህግ መፍረድ ይቻላል ብሎ ማመን 4_ ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን)ን ወይም ከእርሳቸው መመርያ መሆኑን ያወቀውን አንዳች ነገርን መጥላት 5_ ከእስልምና መሆኑ በሚታወቅ ነገር መሳለቅ (72) [72] በአላህ ወይም ከመልእክተኞቹ በአንዳቸውም መሳለቅ፤ ወይ በሙሐመድ፣ ወይ በሙሳ፣ ወይም በዒሳ (የአላህ ሰላትና ሰላም በሁሉም ላይ ይስፈን) በአንዳቸው እንኳ መሳለቅ 6_ የእስልምናን ከፍታ መጥላት፤ ወይም ዝቅ ሲል መደሰት 7_ እነርሱን የተወዳጀ ከከሀዲያን መሆኑን እያወቀ ከከሃዲያን ጋር መወዳጀት 8_ በየትኛውም ጉዳይ ከነብዩ ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም መምሪያ መውጣት ትክክል እንዳልሆነ እያወቀ ከሳቸው መመርያ ውጭ መሆን
9_ ለእስልምና ጀርባን መስጠት፡ ከተገሰፀ በኋላ እስልምናነ ላይረዳውም ላይሰራበትም ጀርባ መስጠት ኩፍር ነው።
10_ በእስልምና ወጥ በሆነ መልኩ ስምምነት ያለበትን አምሳዮቹም ይጠፋቸዋል ተብሎ የማይታሰብን ፍርድ ማውገዝ ክህደት ነው። ለነዚህ ለጠቀስናቸው በቁርአንም ይሁን በሓዲሥ በርካታ ማስረጃ አላቸው። ለ. የሀሳብ ነፅነት፡ በእስልምና የትኛውም ሰው ከእስልምና አስተምህሮት ጋ እስካልተጋጨ ድረስ የሀሳብ ነጻነት ተሰጥቶታል። እስልምና ሙስሊሞችን የወቃሽን ወቀሳም ሳይፈሩ የትም በማንም ፊት ቢሆኑ ለአላህ ብለው እውነታን ብቻ እንዲናገሩ አዟል። ይህንንም ታላላቅ ከሚባሉ ጂሃዶች ይቆጥረዋል። የሙስሊም መሪዎችንም ምክር እንዲለገሱ ከመጥፎ ነገርም እንዲቆጠቡ አዟል፤ በመጥፎ ከሚመክራቸውም ሰው በመልካም ምክር እንዲታደጉ አዟል፤ ይህ ደግሞ እጅግ ታላቁና ያማረው የሃሳብ ነፃነት ስርአት ነው። ይሁን እንጅ ከእስልምና ድንጋጌ ጋር የሚጣረስ የሆነ ሃሳብ ግን ይፋ ሊደረግ የሚችልበት ምክንያት የለም፤ ምክንያቱም እውነትን ለማጥፋት የሚደረግ ውድመት፣ ብክለትና ጦርነት ነውና።
መ. ሰብአዊ ነፃነት፡ አላህ ንፁህ በሆነው እስልምና ሸሪዓ ወሰን እስከሆነ ድረስ በእስልምና ሰብአዊ ነፃነትን ሰጥቷል። በመሆኑም የሰው ልጅ - ወንድም ይሁን ሴት - በራሱ እና በሌሎች መካከል በሚያደርገው መስተጋብር ማለትም በመግዛትና በመሸጥ፣ ስጦታ በሚሰጠውም፣ በሚለግሰውም ይቅር በሚለውም ሁሉ ነፃነት አለው። ለወንድም ሆነ ለሴት የትዳር አጋር የመምረጥ ነፃነትንም ሰጥቷል፤ ስለዚህም ሁለቱም ያልተመቻቸውን ሰው እንዲያገቡ አይገደዱም። ይሁን እንጅ ሴቲቱ በዲኗ የማይመጥናትን ወንድ ከመረጠች ግን በዚህ በኩል ዝም ልትባል አትችልም። ይህም እምነቷን እና ክብሯን ለመጠበቅ፤ ለእሷ እና ለወደፊቱ ቤተሰቧም መስተካከል ሲባል ነው። የሴቲቱ ወሊይ - በዘር ከወንዶች እጅግ በጣም የሚቀርባት ወይም የሱ ተወካዩ - የጋብቻ ውልን የሚፈጸመው እርሱ ነው። ምክንያቱም ሴት ራሷን አታገባምና ምክንያቱም አመንዝራነትን ያስመስልባታልና ነው። ወሊዩ ባሏን እንዲህ ይለዋል: እስልምና ለአንድ ሙስሊም አላህ ከደነገገለት ገደብ በላይ እንዲያልፍ አይፈቅድለትም። ምክንያቱም እርሱም ሆነ እርሱ ያካበተው ነገር ሁሉ የአላህ በመሆኑ ኣጠቃላይ እንቅስቃሴውም ለባሮቹ እዝነት ይሆን ዘንድ በደነገገው የአላህ ህግ ገደብ ውስጥ መሆን አለበት። በዚህም መሰረት የአላህን መመርያ አጥብቆ የያዘ በእርግጥ ቀናውን ጎዳናም ተመርቷል ስኬትንም ተጎናፅፏል። መመርያውን የጣሰ ደግሞ እድለቢስ ሆኖ ጠፍቷል። ስለዚህም ነው አላህ ዝሙትንና ግብረ ሰዶማዊነትን በጥብቅ የከለከለው፤ ሙስሊሙ እራሱን ማጥፋቱም አላህ እሱን የፈጠረበትን አፈጣጠር መለወጡም ተከልክሏል። የፂም ቀድሞ ቀመስን ማሳጠር፣ ጥፍርን መቁረጥ፣ የብልት ዙርያ ፀጉር መላጨት፣ የብብት ፀጉርን መንቀልንና መገረዝን ግን አላህ ያዘዘበት ጉዳይ ነው። የአላህ ጠላቶች በሚለዩበት ሁኔታ መመሳሰልን አላህ ሙስሊሞችን ከልክሏቸዋል። ምክንያቱም በውጫዊ ጉዳዮች እንኳ መምሰል እና በውጫዊ ጉዳዮች (ገጽታዎች) እንኳ እነሱን መመሳሰል ልቦናዊ በሆኑ ጉዳዮችና እነርሱንም መውደድ ያስከትላልና።
አላህ የሚፈልገው ሙስሊሙ የትክክለኛ ኢስላማዊ አስተምህሮ ውጤት ምንጭ እንዲሆን እንጂ የማንም ሃሳብና አመለካከት ለቃሚ እንዲሆን አይደለም። አላህም ሙስሊሙ ጥሩ አርአያ እንዲሆን ነው እንጂ የሚፈልገው ተጎታች መንጋ እንዲሆንም አይደለም። ትክክለኛ ኢንዱስትሪዎች እና ቴክኒካል እውቀትን በተመለከተ እስልምና የሚያዘው እነሱን መማር እና በእነሱ መጠቃቀምን ነው። ለዛ ጉዳይ ቀዳሚው ሙስሊም ያልሆነ ቢሆን እንኳ፤ ምክንያቱም ሁሉንም የሚያሳውቀው አላህ ነውና። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ሰውን ያላወቀውን ሁሉ ያሳወቀ ሲኾን።}
[አልዓለቅ፡ 5]
ይህ አንድ ሰው በነጻነቱ ተጠቃሚ ከሚሆንባቸው፤ ክብሩን ከሚጠብቅባቸው እና ከራሱም ይሁን ከሌላው ክፋት የሚታደግበት ከፍተኛው የምክር እና ማስተካከያ ደረጃ ነው።
(መ) የመጠለያ ነፃነት፡-
አላህም ለሙስሊሙ የመጠለያ ነፃነት ሰጥቶታል። ስለዚህም ማንም ሰው ያለ (ባለቤቱ) ፈቃዱ መግባት እና ካለ ፍቃዱም ወደ መጠለያው መመልከት የለበትም።
(ሠ) ሲሳይ የመሰብሰብ ነፃነት፡-
አላህ ለሙስሊሙ በደነገገለት ገደብ ውስጥ ገቢና ወጪ እንዲያደርግ ነፃነት ሰጥቶታል። ስለዚህም ራሱንና ቤተሰቡን ለማብቃቃት፣ በጽድቅና በምጽዋት ለመለገስ ያስችለው ዘንድ ሰርቶ ሲሳዩን እንዲሰበስብ አዘዘው። ይህ በእንዲህ እንዳለ የተከለከሉ ገቢዎችንም እርም አድርጎበታል። አራጣ፣ ቁማር፣ ጉቦ፣ ስርቆት፣ የጥንቆላ ገንዘብ፣ ጥንቆላ፣ ዝሙት፣ ሰዶማዊነትን የመሳሰሉትን ሁሉ ከልክሏል። አላህ ከተከለከሉ ነገሮች የሚገኝ ገቢንም ለምሳሌ የተንቀሳቃሽ ህያዋን (እንስሳት) ምስሎች ዋጋ [73]፣ የአስካሪ መጠጥ፣ የአሳማ እና የተከለከሉ የሙዚቃ መሳሪያዎች እና የዘፈን እና የዳንስ ክፍያ ሁሉ ሓራም አድርጓል። ልክ ከነዚህ ነገሮች ሲሳይን መፈለግ ሓራም እንደተደረገው ሁሉ ከነሱ የመጣን ገንዘብ ለወጪ መጠቀምም አይቻልም። በመሆኑም ማንኛውም ሙስሊም በተደነገገው መልኩ ካልሆነ በቀር መለገስ እንኳ የለበትም። ይህ ደግሞ ሰው ገንዘቡን ገቢም ወጪም የሚያደርግበትን መንገድ የተብቃቃና ስኬታማ ሆኖ የሚኖርበትን የኑሮ ዘዴ የመምከር፣ የመምራትና የማስተካከል ትልቁ ደረጃ ነው።
[73] በእጅ የተሳሉ ወይም ከእንጨትም ይሁን ከሌሎች ነገሮች ላይ የተጠረቡ ወይም በሸክላ እና በሌሎች ነገሮች የተቀረጹ የተንቀሳቃሽ ፍጡራን ምስሎች ሁሉ “ሙሶዊር” ለሆኑ ሰዎች በመጣው ዛቻ የሚካተቱ ናቸው።
ዘጠነኛ: በቤተሰብ ረገድ:
የላቀው አላህ ቤተሰብን በእስልምና ሸሪዓ አማካኝነት አጥብቆ ለያዘው ሰው የደስተኝነትን ሰበብ ሊያረጋግጥ በሚችል እጅግ በተሟላ ሥርዓት አደራጅቶታል። ለወላጆች - እናትና አባት - ባጠገቡ ከሆኑ በመልካም ንግግር እና በርቀት ከሆነ ደግሞ በዘላቂነት (በዘውታሪነት) መጠየቅ፣ እነርሱን ማገልገል፣ ጉዳያቸውን ማከናወን፣ ሁለቱም ወይም አንዳቸው የገንዘብ ችግር ካለባቸው በገንዘብ እየለገሱ እነርሱን በማረጋጋት መልካምነትን ደነገገ። ወላጆቹን ችላ ለሚልም አላህ የዛተበት ሲሆን ለእነርሱ በጎ ለሚያደርገውም ደስተኝነትን ቃል ገብቶለታል። ትዳርንም ደንግጎ የመደንገጉን ጥበብም ባወረደው መጽሐፍና በላከው ነብይ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አንደበት ግልፅ አደረገ።
***
የጋብቻ መደንገግ ጥበብ
1- ትዳር ለጥብቅነት ታላቅ አስተዋፅኦ ያበረክታል፤ ብልትን ከሓራም ‐ከዚና‐ ይጠብቃል፤ አይንም ሓራምን ነገር ከማየት ይጠብቃል።
2- በትዳር በኩል ለእያንዳንዱ የትዳር ጓደኛ በትዳር አጋሩ ሰላምና መረጋጋት ያገኛል፤ ምክንያቱም አላህ በመካከላቸው ፍቅርንና እዝነትን አድርጓልና።
3- በጋብቻ የሙስሊሞች ቁጥር ንፁህና የተስተካከለ በሆነ መልኩ ተገቢ የቁጥር መብዛትን ያስገኛል። 4- በትዳር ውስጥ እያንዳንዱ የትዳር ጓደኛ ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ የሰጠውን ተፈጥሮ በሚመጥን መልኩ ኃላፊነታቸውን በመወጣታቸው አንዱ ሌላውን ያገለግላል። በመሆኑም ወንዱ ለባለተቤቱና ለልጆቹ ወጪ መሸፈኛ የሚሆን ሲሳይን ለማምጣት ከቤቱ ወጥቶ በመስራት ገንዘብ ያገኛል። ሚስትም በፊናዋ በቤት ውስጥ ሆና ትፀንሳለች፣ ታጠባለች፣ ልጆችን ትንከባከባለች፣ ለባለቤቷም ምግብ፣ ቤቷን እና አልጋዋን ታሰናዳለች። በዚህም ሁኔታ ባልየው ደካክሞት ተጨንቆ እንኳ ወደ ቤቱ ቢገባ ድካምና ጭንቀቱ ለቆት በባለቤቱና በልጆቹ ይፅናናል። የሁሉም ኑሯቸው ያማረና አስደሳች ይሆናል። ሴት ልጅ ለራሷ የሚሆን ሲሳይ ፍለጋም ይሁን ባሏን ለማገዝ መስራቷ ‐ባልና ሚስት ከተስማሙ‐ ምንም አይነት ተቃውሞ የለበትም። ይሁን እንጅ ይህ የምትሰራው ስራ ከባእድ ወንዶች ጋ ቅልቅል የሌለበት ከወንዶች የራቀ መሆን አለበት በሚል ቅድመ መስፈርት የተገደበ ነው። ይህም ወይ በቤቷ ይሆናል፤ ወይም በራሷ እርሻም ወይም በቤተሰቦቿ አልያም በባሏ እርሻም መስራት ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጅ በፋብሪካ፣ በቢሮ፣ በሱቅ ወይም በመሳሰሉት ውስጥ ከወንዶች ጋር እንድትቀላቀል የሚያጋልጣት በሆነ ስራ መስራት ግን ለሴት ልጅ አይፈቀድላትም። ይህች ሴት ራሷ ይህንን መስራት ብትመርጥ እንኳ ለባልዋም ሆነ ለወላጆቿና ለዘመዶቿ ሊፈቅዱላት አይገባም። ምክንያቱም ያ ራሷንም ይሁን ማህበረሰቡን ለብልሹነት ያጋልጣልና።
ሴት በቤቷ ውስጥ ራሷን እስካቀበች ድረስ፣ የባለጌ እጆች ወደ እርሷ በማይዘረጉበት የደህንነቷ ክልል ሆና ከለላ ታገኛለች፤ አታላይ ዓይኖችም አያዩአትም። ነገር ግን በሰዎች መካከል ከወጣች፣ ያን ጊዜ በተኵላዎች መካከል እንዳለች በግ ሆና ትጠፋለች፤ ምናልባትም ብዙም ሳትቆይ እነዚያ ባለጌዎች ክብሯን ይቀረማመቱታል።
ባል በአንዲት ሚስት ካልተብቃቃ፡ አላህ ከአንድ በላይ ማግባትን በመካከላቸው በቻለው ልክ መኖርያቸውን፣ ወጪያቸውን መሸፈንና አብሯቸው ማደርን በፍትህ ማስፈን በሚል ቅድመ መስፈርት እስከ አራት ብቻ ፈቅዶለታል። ይሁን እንጅ የልብ ስራ የሆነውን ውዴታ ግን ቅድመ መስፈርት አይደለም። ምክንያቱም ሰው ችሎታው የሌለውና የማይወቀስበት ጉዳይ እንዲሁም ጥራት ይገባውና የላቀው አላህም በተከታዩ ቃሉ የማይቻል ፍትህ ብሎ የገለፀው ነውና፦ {በሴቶችም መካከል ምንም እንኳን ብትወዱም እኩል ልታደርጉ አትችሉም።}
[አን-ኒሳእ: 129]
ይህ ፍቅርን እና ከእርሱ ጋር የተያያዘን ጉዳይ የሚመለከት ነው። ይህ አይነቱ አለመረጋገጡ ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ ከአንድ በላይ ለማግባት እንደ እንቅፋት አልቆጠረውም። ምክንያቱም አይቻልምና። አላህም ከአንድ በላይ ማግባትን የደነገገው ለመልእክተኞቹም እንደነርሱው የሚቻል የሆነውን ፍትህ ማስፈን ለሚችሉ ሰዎች ነው። ምክንያቱም ጥራት ይገባውና አላህ ለእነርሱ የሚጠቅማቸውን ነገር ዐዋቂ በመሆኑ ለወንዶችም ለሴቶችም የሚበጀውም እርሱው ነው። ይህ የሆነበት ምክንያት ጤነኛ ወንድ የፆታ ዝንባሌ ስላለው በእርሱ ምክንያት የአራት ሴቶችን ፍላጎት ማሟላት ሰለሚችልና ከሓራም እንዲጠበቁ ሊታደጋቸውም የሚችል በመሆኑ ነው። እንደ ክርስቲያኖች [74] እና እንደሌሎቹም እንዲሁም እስልምናን እንደሚሞግቱ አንዳንድ አላዋቂዎች እንደሚጣሩበት ራሱን በአንዲት ሴት ብቻ ቢገድብ የሚከተሉት ብልሽቶች ይከሰታሉ።
[74] የአላህ ነቢይ ኢሳ (የአላህ ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ከአንድ በላይ ማግባትን አልከለከሉም ይልቁንም የከለከሉት ክርስቲያኖች ራሳቸው ስሜታቸውን በመከተል ናቸው።
መጀመሪያ: ባልየው ለአላህ ታዛዥ እና አላህን የሚፈራ አማኝ ከሆነ መነፈግ (መከልከል) እየተሰማው ህይወቱን ሊመራ ይችላል። ነፍሱም ለሓላሉ ያላት ፍላጎት ይታገዳል። ምክንያቱም አንዲት ብቻ ከሆነች እርግዝናዋም በመጨረሻው ወራት፣ የወሊድ ደም መፍሰስ፣ የወር አበባ እና ህመምም በህጋዊ ሚስቱ ላይ ያለውን ፍላጎት ያቅብበታል። በዚህም አግብቶም የሆነ ያክል የህይወት ጊዜውን ሚስት እንደሌለው እየሆነ ለመኖር ይገደዳል። ይህ ግን የምትመስጠው፣ የሚወዳትና የምትወደው (ፍላጎቱን የምታሟላለት) ከሆነች ነው፤ ጭራሽ የማትስበው ከሆነችማ ችግሩ ከዚህም የባሰ ነው።
ሁለተኛው: ባልም ለአሏህ የማይታዘዝ ከዳተኛ ከሆነ ደግሞ ዝሙት ይሰራና ሚስቱንም ይተዋታል። ከአንድ በላይ ማግባትን ከሚያወግዙት ብዙዎቹ በዝሙት የሚጨማለቁ ገደብ የለሽ በሆነ ከአንድ በላይ ማግባት ላይ ያሉ ከዳተኞች ናቸው። ከዚህም የባሰው ደግሞ አሏህ የፈቀደው መሆኑን እያወቀ የተደነገገውን ከአንድ በላይ ማግባትን የሚቃወምና የሚያነውር ከሆነ ከእስልምና የወጣ ከሀዲ ይሆናል።
ሶስተኛ: ከአንድ በላይ ማግባት ከተከለከለ ብዙ ሴቶች ከጋብቻና ዘራቸውንም ከማስቀጠል ይነፈጋሉ። ከእነሱም መካከል ሚስኪን የሆነችዋ ጨዋ ሴት ተነፍጋ የሚትኖር ስትሆን ባለጌና ስድ የሆነችዋም ወንዶች በክብሯ የሚጫወቱባት ሴተኛ አዳሪ ትሆናለች።
እንደሚታወቀው ሴቶች ከወንዶች ይበዛሉ። ምክንያቱም ወንዶች ለሞት ተጋላጭነታቸው ከፍተኛ ነውና። ይህም በጦርነቶች እና አንዳንዴ ለአደጋ በሚያጋልጣቸው የመተዳደሪያ ሥራቸው ምክንያት ነው። እንዲሁም ሴቶች ገና የጉርምስና እድሜያቸው እንደደረሱ ጀምሮ ለትዳር ዝግጁ እንደሆኑ ይታወቃል፤ ወንዶች ግን ሁሉም ዝግጁ አይሆኑም። ምክንያቱም ብዙዎቹ መህር (የጋብቻ ጥሎሽ) የመክፈል አቅም ስለማይኖራቸውና እና በትዳር ሕይወት ውስጥ የሚኖሩ ወጪዎች ወዘተ ለመሸፈን አቅም ስለማይኖራቸው ማግባት አይችሉም። ... ወዘተ
በዚህም መሰረት እስልምና ለሴቶች ፍትሀዊ እንደሆነና ምህረትን እንደሚያደርግላቸው ማወቅ ይቻላል። ህጋዊ የሆነውን ከአንድ በላይ ማግባትን የሚቃወሙት ግን የሴቶች፣ የመልካምነትና የነብያትም ጠላቶች ናቸው። ከአንድ በላይ ማግባት የነብያቶች (የአላህ ሰላም በሁሉም ላይ ይሁን) ፈለግ ነው። ምክንያቱም ሴቶችን ሲያገቡና አላህ ለእነርሱ በደነገገላቸው ገደብ ተገድበው ሚስቶችን ከአንድ በላይም ያገቡ ነበርና።
ሚስት ባሏ ሌላኛዋን ሲይዝ የሚሰማትን ቅናት እና ሀዘን በተመለከተ ስሜታዊነት ብቻ ነው። ስሜታዊነት ደግሞ በማንኛውም ጉዳይ ላይ ከመመርያ ይልቅ ቅድሚያ መስጠት ትክክል አይደለም። አንዲት ሴት ከጋብቻ ውል በፊት ባሏ ሌላ ሴት እንዳያገባባት እንደቅድመ መስፈርት ማስቀመጥ ትችላለች። ቅድመ ሁኔታውን ከተቀበላት የመገደብ ግዴታ አለበት። እሷ እያለች ሌላ ሊያገባባት ከወሰነ እሷ የመቆየትም የመለያየትም አማራጯ ይጠበቅላታል። እሱም ለመህር የሰጣትን ነገር አያስመልስም።
በትዳር ጓደኞች መካከል በተለይ አለመግባባትና መቃቃር ከተፈጠረ፣ አንደኛው የትዳር ጓደኛ ሌላኛውን የማይወድ ከሆነ ፍቺን አላህ ደንግጎታል። ኑሯቸው የስቃይና የጭቅጭቅ እንዳይሆን ሲባል፣ ሁለቱም የሚመቻው አይነት ሰው አግብተው የዱንያ ቀሪ ህይወታቸውንም ሁለቱም በእስልምና ላይ ሳሉ ከሞቱ ደግሞ አኼራቸውንም[75] ያማረ ለማድረግ ሲባል አላህ ፍችንም ደንግጓል።
[75] ደጋግ ሙስሊም ሴቶች (ያላገቡ ወይም ያልተፈቱ ሆነው ከሞቱ) አላህ ከትንሳኤና ሂሳብ በኃላ ጀነት ካስገባቸው በጀነት ውስጥ ካሉ ሙስሊሞች መካከል የፈለጉትን ያስመርጣቸውና ያሻቸውን ያገባሉ። አንዲት ሙስሊም ሴት በዱንያ ሳለች ከአንድ ጊዜ በላይ አግብታ ከነበረች አላህ ለጀነት ካላቸው የዱንያ ባሎቿ መካከል የወደደችውን ታገባለች።
አስረኛ: በጤና ረገድ፦
የእስልምና ህግጋት ሁሉንም የህክምና መርሆዎችን አካትቶ ነው የመጣው። በታላቁ ቁርኣን እና በመልእክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሓዲሥ የብዙ ስነልቦናዊ እና አካላዊ በሽታዎች ገለፃ እንዲሁም ቁሳዊ እና መንፈሳዊ ሕክምናቸውም ተብራርቶ ይገኛል። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ከቁርኣንም ለምእመናን መድኃኒትና እዝነት የሆነን ነገር አወረድን።}
[አል_ኢስራእ፡ 82]
የአላህ መልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦
"አላህ ፈውሱንም ያወረደለት ካልሆነ በቀር ምንም አይነት በሽታን አላወረደም፤ የሚያውቅ ያውቀዋል ያላወቀ አያውቀውም።" [76]
[76] አሕመድ (1 / 377، 413، 453)፤ ኢብኑ ማጃህ (2 / 340)፤ ኢብኑ ሒባን (1394)፤ እንዲሁም ሓኪም (4 / 196) ዘግበውታል፤ አልባኒይም በሲልሲለቱ ሶሒሓህ ሶሒሕ ብለውታል (451)
የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ብለዋል፦
"ተካከሙ በሓራም ነገር ግን አትተካከሙ"[77]
ይህንንም ኢማም ኢብኑል ቀይም “ዛዱል መዓድ ፊ ሀድይ ኸይሪል ዒባድ” በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ በዝርዝር ገልፀውታል። ስለዚህ እባኮትን ይህን የተወሳውን መጽሃፍ በጣም ጠቃሚ፣ ትክክለኛ እና ሁሉን አቀፍ በሆነ መልኩ እስልምናን ከሚያብራሩ እና የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ታሪክን ከሚዳስሱ ኪታቦች መካከል አንዱ በመሆኑም (ያንብቡት) ይከልሱት።
[77] አቡ ዳውድ (3874)፤ አልባኒይም በሶሒሑል ጃሚዕ (1762) ሶሒሕ ብለውታል
አስራ አንድ: ሰዎች የሚያስፈልጋቸውን ውሃ፣ ምግብ፣ መሰረተ ልማት፣ የከተማቸውና የመንደራቸውን ደህንነት የሚያረጋግጡበት ስርአት፣ ፅዳት፣ የመንገድ ቁጥጥር፣ ማጭበርበርን እና ውሸትን መዋጋት እና የመሳሰሉትን ዋስትና የሚሰጥ ታላቅ ሀይማኖት ነው። ይህ ሁሉ ታዲያ በእስልምና ውስጥ በግልፅ ተብራርቷል።
አስራ ሁለት: ድብቅ ጠላቶችን ስለማጋለጥና እነርሱን መታገያ መንገዶች: የላቀው አላህ በተከበረው ቁርኣን ላይ ለሙስሊም ባሪያው ለእነርሱ ከተጎተተላቸውና ከተከተላቸው በዱንያም ሆነ በአኼራው ወደ ጥፋት የሚጎትቱት ጠላቶች እንዳሉት አሳውቆ አስጠንቅቆታል። ከዛም ራሱን የሚያድንበትን መንገድም አብራርቶለታል። እነዚህ ጠላቶችም፦
የመጀመሪያቸው፡- የተረገመው ሰይጣን: የተቀሩትን ሌሎች ጠላቶችን ነድቶ በሰው ላይ የሚያንቀሳቅሰው፤ የአባታችን አደምና የእናታችን ሓዋእ ጠላት የሆነው፤ ከጀነትም እንዲባረሩ ያደረጋቸው፤ እስከመጨረሻ ዘለአለማዊው የሰው ዘር ጠላት፤ በክህደት ላይ ጥሎ ከራሱ ጋር ‐የእሳት ጓድ ለማድረግ ሁሌም የሚጣጣር‐ ወደ ክህደት መዝፈቅ የተሳነውን እንኳ ቢያንስ አላህን እንዲያምፅ አድርጎ ለቅጣትና ለአላህ ቁጣ የሚዳርግ ነው።
ሰይጣንም በሰው ልጅ ውስጥ እንደ ደሙ የሚዘዋወር፤ በልቦናው ውስጥ የሚንሾካሾክ፤ ከታዘዙት ለመጣል ክፋትን የሚያጊያጊጥ መንፈስ ነው። ከእርሱ መጥራት የሚቻለውም ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ በቁርአንም በግልጽ እንዳስቀመጠው፣ አንድ ሙስሊም ሲቆጣ ወይም ገና ኃጢአት እንዲሰራ ሲያሳስበው “አዑዙ ቢላሂ ሚነሽ‐ሸይጧኒ‐ር‐ሯጂም” “ከተረገመው ሰይጣን በአላህ እጠበቃለሁ።” በማለት ቁጣውንም አይታዘዝ ከአመፁም ራሱን ይቆጥብ። የሚሰማው ክፋትም መንስኤው ሰይጣን እንደሆነና ይህንንም የሚያደርገው እሱን ለጥፋት በመዳረግ ከዚያ በኋላ እራሱን ነፃ ነኝ ለማለት ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፡-
{ሰይጣን ለናንተ ጠላት ነው። ስለዚህ ጠላት አድርጋችሁ ያዙት። ተከታዮቹን የሚጠራው ከእሳት ጓዶች እንዲኾኑ ብቻ ነው።}
[ፋጢር፡ 6]
ሁለተኛ ጠላት፡- ስሜታዊነት፡ አንድ ሰው እውነትን ለመካድ የሚመጣበት ፍላጎት፣ ሌላ ሰው ይዞት ከመጣም ውድቅ ለማድረግ የሚጥርበት፣ የአላህንም ፍርድ ለመቃወም ፍላጎት የሚጭርበትም ከዚሁ የተነሳ ነው። ምክንያቱም እውነት የስሜት ተቃራኒ ነውና። እንዲሁም ከእውነት እና ከፍትህ ይልቅ ስሜትን ማስቀደምም ስሜታዊነት ነው። ከዚህ ጠላት መዳኛው መንገድ አንድ ባርያ ስሜቱን ከመከተል እንዲጠብቀው የላቀው አላህን መማፀን፤ ለስሜቱም ምላሽ አለመስጠትና አለመከተል ነው። ይልቁንም እየመረረውም እንኳ እውነቱን ማለትና መቀበል ነው ያለበት። እንዲሁም ከሸይጧንም በአላህ መጠበቅ ያስፈልጋል።
ሶስተኛውኛ ጠላት፡- በመጥፎ የምታዝ ነፍስ፡ በመጥፎ ከምታዝባቸው ተጨባጮች መካከል አንድ ሰው እንደ ዝሙት፣ አስካሪ መጠጥ መጠጣት እና ያለ ህጋዊ ሰበብ በረመዷን ፆም ማፍረስ እና ሌሎች አላህ የከለከላቸው ነገሮችን ለማድረግ የሚነሳሳው ከዚሁ ነው። ከዚህ ጠላት የመዳኛ መንገዱ ከራሱና ከሰይጣን ክፋት ሁሉን ቻይ በሆነው አላህ መጠበቅ እና ይህን የተከለከለውን ምኞት ከመፈፀም መታቀብ። ልክ ቢበላውና ቢጠጣው የሚጎዳው የሆነን ነገር ከመብላትና ከመጠጣት እንደሚቆጠበው ሁሉ የአላህን ውዴታ ከመፈለግ እነዚህን ከመሰሉ ስሜታዊነትም መቆጠብ ነው። ይህን መሰሉ የተከለከለው ምኞት ጊዜያዊ እንደሆነና የሚያስከትሉት የልብ ስብራት እና ጸጸት ረዥምና ዘላቂ መሆኑን ያስታውስ።
አራተኛው ጠላት: የሰው ሸይጧን፡ አመፀኞች የሆኑ ሰይጣን የተጫወተባቸው የሰው ልጆች ናቸው። የተወገዘን ነገር እያደረጉ ከእነርሱም ጋር ለተቀመጡት የሚያጊያጊጡ ናቸው። ከዚህም ጠላት የመዳን መንገዱ ከዚህ አይነቱ መጠንቀቅ እና አብሮም አለመቀማመጥ ነው።
አስራ ሶስት: በከፍተኛ ዓላማ እና ስኬታማ ሕይወት ረገድ፡ ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ ሙስሊም ባሮቹን ያቀናበት (ያመላከተበት) ከፍተኛው አላማ ይህቺ የዱንያ ህይወትና በውስጧ ያለው ጠፊ ማታለያዎች አይደሉም። ይልቁንም፣ ለእውነተኛው እና ዘውታሪው የወደፊት ዝግጅት ነው፣ ይሀውም ከሞት በኋላ ያለው የአኼራው ሕይወት ነው። በመሆኑም ቅን የሆነ ሙስሊም በዚህ ህይወት ውስጥ የሚሰራው ለቀጣይ ህይወቱ መጠቀሚያ እና ለቀጣይ ህይወቱ የሚዘራበት እንደሆነ እንጂ የዚህችን አለም ኑሮ የአላማው ጥግ ድርጎ እንዲይዛት አይደለም።
ቀጣዩን የላቀው አላህ ቃል ያስታውሳል፡-
{ጋኔንንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም።}
[አዝ-ዛሪያት 56]
ቀጣዩንም የላቀው አላህ ቃል፦
{እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ። ማንኛይቱም ነፍስ ለነገ ያስቀደመችውን ትመልከት። አላህንም ፍሩ። አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው።}
{እንደነዚያም አላህን እንደረሱትና ነፍሶቻቸውን እንዳስረሳቸው (ሰዎች) አትኹኑ። እነዚያ እነርሱ አመጸኞቹ ናቸው።}
{የእሳት ጓዶችና የገነት ጓዶች አይተካከሉም። የገነት ጓዶች እነርሱ ምኞታቸውን አግኚዎች ናቸው።}
[አል_ሓሽር፡ 18_20]
የላቀው አላህ እንዲህ ይለናል፦
{የብናኝ ክብደት ያክልም መልካምን የሠራ ሰው ያገኘዋል።}
{የብናኝ ክብደት ያክልም ክፉን የሠራ ሰው ያገኘዋል።}
[አዝ-ዘልዘላህ 7-8]
ቅን ሙስሊም አላህ ባርያዎቹን ወደ ፈጠረበት አላማ የሚመራባቸውን እነዚህንና መሰል ታላላቅ የአላህ አንቀፆችን እንዲሁም ያለ ጥርጥር የሚጠብቃቸውን የወደፊቱ ህይወት ያስታውሳል። ስለዚህም አላህን ብቻ ጥርት አድርጎ በማምለክ፣ የአላህን ውዴታ ፈልጎ፣ በዚህች አለም አላህን በመታዘዙ መከበርንና በአኼራው ደግሞ የክብር ሀገር የሆነችውን ጀነት ለመግባት ተስፋ በማድረግ አላህን የሚያስደስተውን ነገር እያደረገ ይዘጋጃል። አላህም በዚህ ህይወት መልካም ህይወትን በመለገስ ያስከብረዋል። ባርያውም በአላህ ጥበቃና ከለላ ስር ሆኖ በአላህ ብርሀን እያየ ይኖራል። አላህ እንዲያደርግ ያዘዘውን የአምልኮ ተግባራትን እያከናወነ የላቀውን አላህ በማነጋገር የአምልኮ እርካታውን ያጣጥማል። አላህን በልቡና በአንደበቱ በማስታወስም ልቡን ያረካል።
በንግግሩም ሆነ በሥራው ለሰዎች ደግ ያደርግላቸዋል፤ ለዚህም ከመካከላቸው ከተከበሩ ሰዎች ለበጎነቱ ሲመሰክሩና ደስ የሚያሰኘውንም ነገር ዱዓእ ሲያደርጉለት ይደርሰውና ልቡ ይበልጡን ለኢማኑ ገር ይሆናል። ከዝቃጭ ምቀኞች ደግሞ ለደግነቱ ወቀሳ ይደርሰዋል፤ ይሁን እንጅ ይህ ወቀሳ ለእነሱም ጭምር ደግ ከመሆን አያቅበውም። ምክንያቱም የአላህን ፊት እና ምንዳ ብቻ ነውና የሚፈልገው። የአላህ መልክተኞችን በሚያስታውሰው መልኩ የዲንና የዲን ሰዎች ጥላቻ የተሞሉ ከሆኑ ክፉ ሰዎችም ሲሳለቁበትና ጉዳትንም ሲያደርሱበት ይመለከታል ይሰማልም፤ በዚህም ታዲያ ይህ ለአላህ ሲል በሚያደርገው ነገር የመጣበት መሆኑን በማወቁ እስልምናን ይበልጥ መውደዱንና በእሱ ላይ ያለውን ፅናት ይበረታል።
በላቡም እስልምናንና ሙስሊሞችን ለማገልገል፤ አላህንም በሚገናኝበት ጊዜ ለቅንነቱና ለመልካም ኒያው አላህ መልካም ምንዳውን ይቸረው ዘንድ፤ ራሱንም ቤተሰቡንም የሚጠቅምበትን ጥሩ ሲሳይ አግኝቶ በዛው ምፅዋቱን እየለገሰ ኑሮውም የተብቃቃ ልቦና ባለቤት፣ የተከበረና ቆፍጣና ሆኖ ይኖር ዘንድ ለምልካምነቱም ምንዳውን ከአላህ ብቻ በመከጀል በቢሮም ይሁን፣ በእርሻ፣ በመደብር ወይም በፋብሪካ ውስጥም ይሠራል። ምክንያቱም አላህ ብርቱንና ባለሞያ አማኙን ይወዳልና። ሲበላም ሲጠጣም ሲተኛም አላህን በመታዘዝ ላይ ይታገዝበት ዘንድ በመሆኑ ያለገደብ አያደርገውም።
ከሚስቱ ጋር እንኳ የሚኗኗረው እሷንም ራሱንም አላህ ከከለከለው ነገር ለመታቀብ፣ ኖረም ሞተም ዱዓእ የሚያደርጉለትን ደጋግ ልጆችን በመውለድ መልካም ስራው እንዲቀጥልለትና የሙስሊሞችን ቁጥር በማብዛት ለዚህም አጅር እንዲያገኝበት ነው። የሚያገኛቸው ፀጋዎችም የላቀው አላህን መመርያ በመታዘዝ ላይ እየታገዘባቸው እና ከአላህ ብቻ መሆኑን እውቅና በመስጠት ምስጋናውን ያቀርባል። በዚህም ከአላህ መልካም ምንዳን ያገኝበታል። አንዳንድ ጊዜ የሚያጋጥመው ረሃብ፣ ፍርሃት፣ በሽታና መከራ ሁሉ የትግስቱን ልክና ለአላህ ቀደር ያለውን ውዴታ (አላህ የበለጠ ሁሉን አዋቂ ከመሆኑም ጋ) [78] ምን ያክል እንደሆነ ለማወቅ ከአላህ ዘንድ የሆነ ፈተና መሆኑን ይረዳል። ስለዚህም አላህ ለታጋሾች ያዘጋጀውን ምንዳ በማሰብ ፈተናውን ይታገሳል፣ ወዶ ይቀበላል፣ በሁኔታውም ሁሉ አላህን ያመሰግናል። በዚህም ልክ ህመምተኛ የመድሀኒትን መራራነት ፈውስን ተስፋ በማድረግ ወዶ እንደሚቀበለው ይሀው ባርያም የደረሰበትን ችግር ቀለል አድርጎ ይቀበለዋል።
[78] አላህ ከባሮቹ (መካከል) ማን እንደሚታዘዘውና ማንስ እንደሚያምፀው ከመመርያውም በፊት እያወቀ ትእዛዝና ክልከላውን ያስተላልፍላቸዋል። ይህን የሚያደርገውም ሁሉም በስራው እንዳገኘው ግልጽ ለማድረግ ነው። በመሆኑም ክፉ ሰው “ጌታዬ ባልሠራሁት ኃጢአት ነውና የቀጣኝ በድሎኛል” ሊል አይችልም። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ጌታህም በባሮቹ ላይ በዳይ አይደለም} [ፉሲላት፡ 46]
ሙስሊሙ በዚህች አለም ኑሮውን ሲኖር በዚህ ታላቅ መንፈስ አንዳች በካይ በማይበክለው ሞት እንኳ ለማያቋርጠው ዘልአለማዊ ለሆነ ደስተኝነት እድለኛ ይሆን ዘንድ ለዘውታሪው ትክክለኛ ህየወቱ እየሰራ አላህ ባዘዘው መልኩ የሚኖር ከሆነ ያለጥርጥር በዚህች አለምም ሆነ ከሞት በኃላ ባለው አለም ደስተኛና ስኬታማ ነው። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦
{ይህች የመጨረሻይቱ አገር ለእነዚያ በምድር ውስጥ ኩራትንና ማመፅን ለማይፈልጉት እናደርጋታለን። ምስጉኒቱም መጨረሻ ለጥንቁቆቹ ናት።}
[አል_ቀሶስ፡ 83]
የላቀው አላህ እንዲህ በማለት እውነትን ነገሮን ነበር፦
{ከወንድ ወይም ከሴት እርሱ አማኝ ኾኖ በጎን የሰራ መልካም ኑሮን በእርግጥ እናኖረዋለን። ይሠሩትም ከነበሩት ነገር በመልካሙ ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን።}
[አን-ነሕል 97]
ባሳለፍነው አንቀፅ እና ተመሳሳይ በሆኑ ሌሎች አንቀፆች አላህ እያሳወቀን ያለው: ውዴታውን ከጅለው በዚህ ሕይወት ውስጥ አላህን በመታዘዝ ለሚሠሩ ደጋግ ወንድና ሴቶች በዚህ ሕይወት ቀደም ብለን ያወሳነው መልካምና ደስተኛ ህይወትን በማኖር ፈጣን ምንዳ፤ ከሞት በኃላ ደግሞ የፀጋ ሀገር በሆነችው ጀነት በማስገባት የዘገየ ምንዳን ይመነዳቸዋል። በዚህ ረገድ መልእክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲህ ይላሉ፦
"የሙእሚን ጉዳይ ምንኛ ያስደንቃል?! ጉዳዩ ሁሉ ለእርሱ መልካም ነው። ይህ ደግሞ ለሙእሚን ካልሆነ በስተቀር ለማንም አይሆንም። መልካም ሲያጋጥመውም አላህን ያመሰግናል መልካምም ይሆንለታል፤ ክፋትም ሲያጋጥመው ይታገስና መልካም ይሆንለታል።" [79]
ሙስሊም (2999)፤ አሕመድ (4/332)፤ ዳሪሚይ (2777) ላይ ዘግበውታል
በዚህም መሰረት ጤናማ አስተምህሮ ያለው በእስልምና ውስጥ ብቻ እንደሆነ፤ የጥሩ እና መጥፎው ትክክለኛ መለኪያው እንዲሁም የተሟላ እና ፍትሃዊው ዘዴ እንደሆነ እንረዳለን። ስለዚህም በስነ ልቦና፣ በህብረተሰብ፣ በትምህርት፣ በፖለቲካ እና በኢኮኖሚክስ እና በሁሉም የሰው ልጅ የአኗኗር ዘይቤዎች፣ አስተምህሮቶችና አመለካከቶች ሁሉ ከእስልምና አንፃር መታረም ብሎም ከእሱ የመነጩ መሆንም አለባቸው። አለበለዚያ ከእሱ ጋር በሚቃረኑት ስኬትን መጎናፀፍ የማይታሰብ ነገር ነው። ኧረ እንደውም እስልምናን የተቃረኑትን የያዙ ሁሉ በዱንያም ሆነ በመጨረሻው ዓለም የመከራ ምንጭ ነው የሚሆንባቸውን ነው የያዙት።
***
ምዕራፍ አምስት - አንዳንድ ውዥንብሮችን ማጋለጥ:
አንደኛ: እስልምናን የሚበድሉት፡ ይበልጥ እስልምናን የሚበድሉ ሰዎች ሁለት አይነት ናቸው።
የመጀመርያዎቹ ምድብ፦ ሙስሊም ነን የሚሉ ሰዎች ሲሆኑ ነገር ግን በንግግራቸው እና በተግባራቸው እስልምናን የሚቃረኑ በመሆናቸው ንፁህ የሆነውን እስልምና የሚቃረን ድርጊት የሚፈፅሙ ናቸው። በመሆኑም እስልምናንም አይወክሉም ተግባራቸውን ከእስልምና ጋር ማያያዝም ትክክል አይደለም። እነዚህም የሚከተሉት ናቸው:
[ሀ] በእምነታቸው (በዓቂዳ) ያፈነገጡ፡- ልክ እንደነዚያ በመቃብሮች “ጠዋፍ” የሚያደርጉና ጉዳያቸውንም በውስጣቸው ባሉት ሰዎች እንዲፈፀምላቸው የሚከጅሉ፤ የመቃብሩ ሰዎች መጥቀምና መጉዳት እንደሚችሉም እንደሚያስቡት [80]... ወዘተ
[80] እንዲሁም በእስልምና ስም ንፁሀንን እንደሚገድሉት እንደ “ኸዋሪጅ” አይነቶቹ ያሉ፤ እነዚህኞቹ አብዛኛውን ጊዜ በእስልምና ጠላቶች የሚጠነሰሱ ናቸው።
[ለ] በሥነ ምግባራቸውና በሃይማኖታቸው ብልሹ የሆኑ፡-
የአላህን መመርያ ወደ ጎን ትተው እንደ ዝሙት፣ አስካሪ መጠጥ መጠጣትና መሰል እርም ነገራቶችን የሚፈፅሙ የአላህንም ጠላቶች የሚወዳጁ የሚመሳሰሉ ናቸው።
[ሐ] እስልምናን ከሚበድሉት (ከሚያጠለሹ) ሰዎች መካከልም ሙስሊሞች ሆነው ነገር ግን በአላህ ላይ ያላቸው እምነት ደካማ፤ ለእስልምና አስተምህሮት ያላቸው ተግባራዊነትም ጎዶሎ በመሆኑ አንዳንድ ግዴታዎችን ባይተውትም አጉድለው ነው የሚሰሩት፤ ከተከለከሏቸው ነገሮችም ወደ ክህደት ደረጃ የማይደርሱ ትላልቅ ወንጀሎችንም ይፈፅማሉ። በዚህም ሁኔታቸው ታዲያ እስልምና የከለከለውን ብሎም እንደ ታላቅ ወንጀል የቆጠረውን አይነት ልማድ ተላምደው የያዙ ናቸው። ለምሳሌ፡- እንደ ውሸት፣ ማጭበርበር፣ ቃል ኪዳንን ማፍረስ እና ምቀኝነት ይህ ሁሉ እነሱ በመፈፀማቸው እስልምናን የሚያጠለሹበት ነው። ምክንያቱም እስልምናን የማያውቁ ሙስሊም ላልሆኑት ሰዎች እስልምና የፈቀደላቸው እስኪያስመስልባቸው ድረስ ነው የሚፈፅሙት።
የሁለተኛው ምድብ ደግሞ፡- የእስልምና ጠላቶች እስልምናንም የሚጠሉ ሆነው እስልምናን የሚበድሉት (የሚያጠለሹ) ናቸው። ከነሱም ውስጥ፡- ኢስላምን ለማጠልሸት ብለው ስለ ኢስላም የሚያጠኑ (ሙስተሽሪቆች) ፣ አይሁዶች፣ ክርስቲያን ሚሲዮናውያን እና የእነሱን አርአያነት የተከተሉት የእስልምና ጠል የሆኑ ሰዎች ናቸው። ተፈጥሯዊ ሀይማኖት በመሆኑ[81] ማንኛውም ተፈጥሯዊ የንፁህ ህሊና ባለቤት ሁሉ የሚቀበለው በመሆኑ፣ በፍፁምነቱና በገራገርነቱ እና በመስፋፋት ፍጥነቱ የተቃጠሉ ናቸው። ማንኛውም ሙስሊም ያልሆነ ሰው በጭንቀት እና በሃይማኖቱ ወይም በተቀበለው አስተምህሮ እርካታ ቢስነት ስሜት ውስጥ ነው የሚኖረው። ምክንያቱም ከእውነተኛው ሙስሊም በስተቀር ሌላው ሀይማኖት አላህ ከፈጠረው ተፈጥሮ ጋር ይቃረናልና። ምክንያቱም ትክክለኛው ሙስሊም በሃይማኖቱ ደስተኛና እርካታ ያለው ሆኖ የሚኖረው እርሱ ብቻ ነውና። ምክንያቱም እስልምና አላህ ያወጣው መመርያ ነውና፤ የአላህ መመርያ ደግሞ አላህ የሰው ልጆችን ከፈጠረበት አፈጣጠር (ህሊና) ጋር የሚገጥም ነው። ስለዚህም ለመላው ክርስትያን፣ ለመላው አይሁድና ለመላው ከእስልምና ውጭ ላለ ሁሉ እንዲህ እንለዋለን፡- ልጆቻችሁ የተወለዱት በተፈጥሮው የእስልምና ሃይማኖት ሲሆን አንተ እና እናታቸው ግን በምታደርጉት ብልሹ የክህደት እንክብካቤ ይሀውም ከእስልምና ሀይማኖት ጋር በሚፃረሩ ሀይማኖቶች እና አንጃዎች እያሳደጋችኃቸው ነው።
[81] የመልእክተኞች መደምደሚያ ሙሐመድ ﷺእንዲህ ብለዋል: "ማንም ተወላጅ የሚወለደው በተፈጥሯዊ ሀይማኖቱ ሆኖ ነው የሚወለደው፤ ነገር ግን ወላጆቹ ወይ አይሁድ፣ ወይ ክርስትያን ወይም ደግሞ እሳት አምላኪ ያደርጉታል።" [ቡኻሪይ (1292)፤ ሙስሊም (2658) ላይ ዘግብውታል። የተጠቀሰው ቃል ግን በሙስሊም ዘገባ ያለው ቃል ነው።] በዚህ ሀዲስ መልእክተኛው ሙሐመድ -ﷺ- አንድ ሰው በእስልምና ተፈጥሮ ላይ እንደሚወለድ ነው እየነገሩን ያሉት። በተፈጥሮውም በእስልምና ያምናል። ስለዚህም አንድ ሰው እንዲሁ በተፈጥሮው እንዲመርጥ ቢተው ያለጥርጥር እስልምናን በመረጠ ነበር። ሰዎች የአይሁድ እምነት ወይም የክርስትናን እምነት አልያም ደግሞ እሳት አምላኪ እምነትን የሚይዙበት አጋጣሚ የአስተዳደግ ጉዳይ እየሆነባቸው ነው።
በርግጥ እነዚህ ኢስላም ጠል ምዕራባውያን እና ሚስዮናውያን እስልምና ላይ እና የመልእክተኞች መደምደሚያ ሙሐመድ ﷺ ላይ እየታወቃቸው ይቀጥፋሉ:
1- አንዳንድ ጊዜ መልእክቱን ሆን ብለው በማስተባበል
2- አንዳንድ ጊዜ ሆን ብለው በማነወር፤ ይሁን እንጅ የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የፈለገ ድብን ይበል እርሳቸው ከነውር የፀዱ ናቸው።
3- እጅግ አዋቂና ጥበበኛ የሆነው አላህ የደነገጋቸውን አንዳንድ ኢስላማዊ ፍትሐዊ ውሳኔዎችን ሆን ብሎ ሰውን ለማሳት በማጣመም
ይሁን እንጅ ጥራት ይገባውና አላህም ሁሌም ተንኮላቸውን ያከሽፍባቸዋል። ምክንያቱም እነርሱ እውነትን ነውና እየታገሉ ያሉት፤ እውነት ደግሞ የበላይ ይሆናል እንጅ የበላይ አይሆንበትም።
{የአላህን ብርሃን በአፎቻቸው ሊያጠፉ ይሻሉ። አላህም ከሓዲዎቹ ቢጠሉም እንኳ ብርሃኑን ገላጭ ነው።}
{እርሱ ያ አጋሪዎቹ ቢጠሉም መልክተኛውን (ሙሐመድን) በቅን መንገድና በእውነተኛ ሃይማኖት ላይ ከሃይማኖት ሁሉ በላይ ይፋ ያደርገው ዘንድ የላከው ነው።}
[አስ_ሶፍ፡ 8_9]
ሶስተኛ፡ የእስልምና ምንጮች፡
አንተ አስተዋይ የሆንክ ሰው ሆይ! እስልምናን በእውነተኛ ማንነቱ ለማወቅ ከፈለግክ ታላቁን ቁርኣን እና የመልእክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ሓዲሦችን ከሶሒሕ ቡኻሪይ፣ ከሶሒሕ ሙስሊም፣ ከኢማሙ ማሊክ ሙወጧእ፣ የኢማም አህመድ ቢን ሀንበል ሙስነድ፣ ሱነን አቢ ዳውድ፣ እና ሱነን አን-ነሳኢ፣ ሱነን አል-ቲርሚዚ፣ ሱናን ኢብኑ ማጃህ እና ሱነን አል-ዳሪሚይ አንበብህ ተረዳ።
እንዲሁም የኢብኑ ሂሻም “ሲረቱን‐ነበዊያህ”፣ “ተፍሲር ኢብኑ ከሢር” የእውቁ ዓሊም ኢስማዒል ቢን ከሢርን ተፍሲር እና የእውቁ ዓሊም ሙሐመድ ኢብኑል ቀይምን “ዛዱል መዓድ ፊ ሀድይ ኸይሪል ዒባድ” እንዲሁም መሰል የእስልምና ኢማሞች መጽሃፎች፣ ወደ አላህ በሚያደርጉት ጥሪ የተውሂድና የእውቀት ጓድ የሆኑ ሰዎች እንደነ ሸይኹል ኢስላም አሕመድ ኢብኑ ተይሚያህ እና አላህ በሳቸውና በአሚረል ሙወሒዲን ሙሐመድ ኢብኑ ሰዑድ አማካኝነት ዲነል ኢስላምንና የእስልምናን ዓቂዳ በአረብ ባህረሰላጤ እንዲሁም በተለያዩ ቦታዎች ሽርክ ከተንሰራፋ በኃላ በድጋሚ እንዲከስም አላህ ሰበብ ያደረጋቸው የ12ኛው ክ/ዘበን እስካሁንም ሙጀዲድ ኢማም ሙሀመድ ኢብኑ አብዱልወሃብ ኪታቦችን ይመልከቱ።
የምዕራባውያንና አንዳንድ በሚጣሩበት ጉዳይ ከእስልምና አስተምህሮት ጋር እየተጋጩ፣ ወይም ለነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ባልደረቦች ወይም ከፊሎቹን በስድብና በማንቋሸሽ እያነወሩ ወይም ደግሞ ወደ አላህ ተውሒድ ዳዕዋ ለሚያደርጉ እንደነ ኢብኑ ተይሚያህ፣ ኢብኑል ቀይም፣ ሙሐመድ ኢብኑ ዓብዱል ወሀብ፣ እያነወሩና እያንቋሸሹ የሚፅፉ ራሳቸውን ወደ እስልምና የሚያስጠጉ አንጃዎች ስለሚፅፏቸው መጻሕፍት ብዙዎቹን በማስመልከት በጥቅሉ ቀደም ብለን አውስተናል። ይህን መሰሎቹ እንዳያታልሉህ እነሱን ከማንበብ ተጠንቀቅ።
ሶስተኛ፡ ኢስላማዊ አስተምህሮቶች፡
ሁሉም ሙስሊሞች በአንድ አስተምህሮ (መዝሀብ) ጥላ ስር ናቸው። እርሱም እስልምና ሲሆን ዋቢያቸውም ቁርኣንና የመልእክተኛው ﷺ ሓዲስ ነው። እስላማዊ መዝሀቦች የሚባሉት እንደ አራቱ መዝሐቦች ማለትም፡ እንደ ሀንበሊ፣ ማሊኪ፣ ሻፊዒይ እና ሀነፊ መዝሀብ የሚባሉትን በማስመልከት እነዚህ ሊቃውንት ኢስላማዊ የፊቅህ ህጎችን በመሰረተ ኢስላም(ኡሱሉል ኢስላም) ያስተማሩባቸው መንገድ ነው። የሁሉም ዋቢዎቻቸውም ቁርኣን እና የመልእክተኛው - ﷺ - ሓዲሥ ነው። በመካከላቸው ያለው ልዩነትም ኢምንት በሆኑ ንኡስ ጉዳዮች ላይ ነው። እያንዳንዱ ዓሊምም ተማሪዎቹን ቁርኣናዊ ወይም ሐዲሳዊ ማስረጃ የሚደግፈው የሌላ ዓሊምም ቢሆን ቃል እንዲይዙ ነው አዟል።
ሙስሊም የአንደኛቸውን አቋም ብቻ አጥብቆ የመያዝ ግዴታ የለበትም። ይልቁኑ ወደ ቁርኣን እና ሐዲስ የመመለስ ግዴታ ነው ያለበት። ራሳቸውን ወደነዚህ መዝሀቦች ከሚያስጠጉት መካከል ብዙዎች ቀብር ዙርያ “ጠዋፍ” በማድረግ፣ ለቀብሩ ባለቤቶች የድረሱልኝ ዱዓቸውን በማሰማት፣ የአላህን ባህሪያቶች በማጣመም ከትክክለኛ ትርጉማቸው በማውጣት በእምነት (በዓቂዳ) በኩል የሚያፈነግጡት ነገር፤ እንከተላቸዋለን የሚሏቸውን ኢማሞችን እንኳ ሳይቀር በእምነት (በዓቂዳ) ጉዳይ እየተቃረኗቸው ነው የሚገኙት። ምክንያቱም የአኢማዎቹ እምነት (ዓቂዳ) ቀደም ብለን የምትድነዋን ቡድን በማስመልከት ባወሳነው መልኩ የሰለፉ ሷሊሕ እምነት ነውና።
አራተኛ፡- እስላማዊ ያልሆኑ አንጃዎች፡
በሙስሊሙ አለም ከእስልምና ውጪ የሆኑ አንጃዎችም አሉ። እነዚህ ቡድኖች ራሳቸውን ወደ ኢስላም የሚያስጠጉና ሙስሊም ነን ብለው የሚሞግቱም ናቸው። ይሁን እንጅ በተጨባጭ ሙስሊሞች አይደሉም። ምክንያቱም በአላህ፣ በአንቀፆቹ እና በአንድነቱ (ተውሒድ) ላይ ያላቸው እምነት የክህደት እምነት በመሆኑ ነው። ከነዚህም አንጃዎች መካከል፡-
1 - ባጢኒዮች:
በስርፀት እና በውህደ‐አካል(reincarnation) ፅንሰሀሳቦች የሚያምኑ እና የቁርአንና ሓዲሥ ጥቅሶች መልእክተኛው ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም ካስተማሩትና ሙስሊሞችም አንድ ወጥ አቋም የሚያንፀባርቁበት ከሆነው ጉልህ አስተምህሮ ጋር የሚጋጭ ድብቅ ሚስጥር እንዳላቸው የሚያምኑ ናቸው። ይህን የሚሞግቱትን ድብቅ ሚስጥር የሚያስቀምጡት ደግሞ ራሳቸው እንዳሰኛቸው ነው[82]። የባጢኒያ እምነት አነሳሱ በፋርስ ያሉ የአይሁድና የእሳት አምላኪ ፈላስፋዎች የእስልምና መንሰራፋት ከአቅማቸው በላይ ሆኖ ማሸነፍ ባቃታቸው ጊዜ ሙስሊሞችን ከእምነታቸው በማንሸራተትና በቁርአኑ ላይ ያላቸውን ምልከታ በመሸርሸር ሙስሊሞችን ለመበተን አልመው ተሰባሰቡ። በመጨረሻም ይሄንን አውዳሚ የሆነ ሀሳብ ይዘው በመምጣት በዚህ ሀሳባቸው ጃሂሉን ለማሳሳትም ራሳቸውን የነብዩ ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም ቤተሰብ እስከማድረግ ደረሱ የነብዩ ቤተሰብ ነን ብለውም ሞገቱ ወደዚያውም ጥሪ ማድረግ ጀመሩ። በዚህ ሴራዊ ጥሪያቸውም ብዙ አላዋቂዎችን ነጥቀው ከእውነት እንዲስቱ አደረጉ።
[82] ባጢኒያህ ብዙ ቅጽል ስሞች አሏቸው፦ በህንድ፣ በሻም፣ በኢራን፣ በኢራቅ እና በሌሎች ብዙ ሀገሮች የተከፋፈሉ ብዙ ጎራዎች አሏቸው። ከቀደምት ዓሊሞች መካከልም በርካቶቹ በዝርዝር ገልፀዋቸዋል። አል-ሻህሪስታኒ “አል-ሚለል ወን-ኒሐል” በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ እንዲሁም በርካታ የኋለኞቹ ዓሊሞችም እንዳብራሩት አዳዲስ አንጃዎችም መከሰታቸውን ገልፀዋል። ከነዚህም መካከል፡ ቃዲያኒዮች፣ በሃኢዮች እና ሌሎችም ይገኙበታል። እነዚህን አንጃዎች ከገለጿቸውም መካከል መሐመድ ሰኢድ ከይላኒይ በ“ዘይሉል ሚለል ወን‐ኒሐል” ኪታባቸው ላይ እና እና በመዲና እስላማዊ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር የሆኑት ሸይክ ዐብዱልቃድር ሸይባህ አል-ሐማድ ስለ ወቅታዊ ሃይማኖቶች፣ አንጃዎችና አስተምህሮቶች በዳሰሱበት ኪታብ ገልፀውታል።
2- ከነዚያ አንጃዎችም (ቃዲያኒያዎች)፡- በዚህ ስም የተሰየሙት ነብይ ነኝ ብሎ እንደሞገተ ብዙዎች ዘንድ ከተሰራጨው ጉላም አሕመድ አልቃዲያኒ ተከታይነታቸው አንፃር ነው። በህንድ እና አካባቢዋ ያሉ ወፈፌዎችን እንዲያምኑበት ጥሪ አደረገላቸው፤ እንግሊዛውያንም ህንድን ቅኝ በገዙበት ጊዜ እሱን እና ተከታዮቹን እየተጠቀሙባቸው እነሱን ደግሞ ልዩ እንክብካቤ ያደርጉላቸው ነበር። ብዙ አላዋቂዎችንም እንዲከተሉት እስከማድረግ ደረጃ ደርሰዋል። ቃዲያኒዎች እስልምናን ተመሳስለው ነገር ግን እሱን ለማጥፋት እና የቻሉትን ከዙሪያው ለማባረር የሚጥሩ ናቸው። መጽሃፍ እንደጻፈ ይታወቃል: “ተስዲቁ በራሂኑ አሕመዲያህ” የተሰኘ መፅሀፍ ፅፏል ተብሎ ብዙዎች ዘንድ ይታወቃል። በዚህ መፅሀፉም ነበር ነብይነትን የሞገተው፣ የእስልምና ጥቅሶችንም ያዛባበት። በኪታቡ ካዛባቸው የእስልምና ጥቅሶች መካከል “ጅሀድ” በእስልምና ተሽሯል ማለቱና
እያንዳንዱ ሙስሊም ከእንግሊዝ ጋር እርቅ መፍጠር አለበት ማለቱ ይገኝበታል። እናም በዚያን ጊዜ እንዲህም የሚባል መጽሃፍ ፅፏል: "ቲርያቁል ቁሉብ" ይህ ጸሃፊ እ. ኤ. አ በ1908 ብዙ ሰዎችን ካሳሳተ በኋላ ሞተ። ከሞተ በኃላም በተልዕኮውና በተሳሳተ አንጃው መሪነት ሃኪም ኑር አል-ዲን የተባለ ጠማማ ሰው ተተካለት።
3- ከእስልምና ውጪ ከሆኑ የባጢኒያ አንጃዎች መካከል ባሃኢ በመባል የሚጠራውና በ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ በሀገረ ኢራን አሊ መሐመድ በተባለ ሰው የተመሰረተው ቡድን ይገኝበታል። ሙሐመድ አሊ አል-ሺራዚ ከሺዓ ኢሥና ዓሸሪያ አንጃ አባል እንደነበር ይነገራል። ከዚያም የሚጠበቀው መህዲ እኔ ነኝ ብሎና የላቀው አላህ በኔ ላይ ሰርጿል ብሎ በመሞገት ራሱን የሰዎች አምላክ አደረገና (የላቀው አላህ ከሀድያንም ቀጣፊዎችም ከሚሉት ሁሉ ጥራት ይገባውና) ለራሱ የሞገተውን አስተምህሮ መርጦ ተገነጠለ። በዚህም አላበቃም ከሞት በኃላ ባለ በትንሳኤ፣ በስራ መተሳሰብ፣ በጀነት፣ በጀሀነም በመካድ በብራህሚን እና በቡድሂስት ካፊሮች ጎዳና ተጓዘ። አይሁዶች፣ ክርስቲያኖችና ሙስሊሞችም አንድ እንደሆኑና በመካከላቸውም ምንም ልዩነት እንደሌለ ሞገተ። ከዚያም የመልእክተኞችን መደምደሚያ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) እንዲሁም ብዙ ኢስላማዊ ፍርዶችንም አስተባበለ። ከዚያም እሱ ከሞተ በኃላም “በሃእ” የተባለ አገልጋዩ ወረሰውና ጥሪውንም አሰራጨለት ተከታዮቹንም አበዛለት። ከዚያ በኃላ አንጃው በስሙ ይጠራ ዘነድ “በሃኢዮች” ይባሉ ጀመር።
4- ከእስልምና ውጭ ከሆኑ አንጃዎች መካከል ሙስሊም እንደሆኑ ቢሞግቱም፣ ቢሰግዱ፣ ቢጾሙ፣ እና ሐጅ ቢያደርጉም ጅብሪል (የአላህ ሰላም በእርሱ ላይ ይሁን) ለዓሊይ (አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸው) እንዲያደርስ የተሰጠውን ተልእኮ ለሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) አሳልፎ በመስጠቱ ሸፍጥ ሰርቷል ብለው የሚሞግቱ ናቸው። አንዳንዶቹ ደግሞ ዓልይን አምላክ ነው ይሉታል፤ እርሱን፣ ልጆቹን፣ የልጅ ልጆቹን፣ ሚስቱን ፋጢማን እና እናቷን ኸዲጃን - አላህ የሁሉንም መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና - በማወደስ ድንበር ያልፋሉ፤ ኧረ እንደውም እነርሱን የአላህ ብጤ አምላክ አድርገዋቸው እነርሱን እስከመማፀን ይደርሳሉ፤ ፍፁም የማይሳሳቱ ከኃጢአትም የነፁ መሆናቸውንና በአላህ ዘንድ ያላቸውም ደረጃ ከመልክተኞች (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) የላቀ እንደሆነ ያምናሉ
እነዚህ አካላት፦ አሁን በሙስሊሞች እጅ ያለው ቁርኣን የተጨመረና የተቀነሰ ነገር አለበት በማለት ለራሳቸው የተለየ የቁርኣን ቅጂ አዘጋጁ። በዛ ላይም ያሻቸውን አንቀጾች በራሳቸው አደረጉበት። ሙስሊሞች ከነቢያቸው በመቀጠል ታላላቅ ደረጃ ያላቸውን እነ አቡበክር እና ዑመርን (አላህ የሁለቱንም መልካም ሥራ ይቀበላቸው) ይዘልፋሉ፤ የሙእሚኖች እናት ዓኢሻንም (አላህ መልካም ሥራዋን ይቀበላት) ይዘልፋሉ። በችግርም በድሎትም ጊዜ የድረሱልኝ ተማፅኗቸውን (ኢስቲጋሣ) ለዓልይ እና ለልጆቹ ያሰማሉ፤ ከአላህ ውጭም ይጠሯቸዋል። ዓልይና ልጆቻቸው ግን ከእነሱ የጠሩ ናቸው። ምክንያቱም ከአላህ ጋር አማልክት አድርገው ስለያዟቸው፣ በአላህም ላይ ስለ ቀጠፉ እና ቃሉንም ስላዛቡ ነው። - የላቀው አላህ እነርሱ ከሚሉት እጅጉን የጠራ ነው- [83]።
[83] የእስልምናን ገጽታ ከሚያጠለሹበት ተግባራቸው ውስጥ ፊታቸውንና ደረታቸውን በጥፊ የሚደልቁት ነገርና ሰውነታቸውን በሰንሰለትና በቢላ የሚመቱት ነገር ተጠቃሽ ነው።
እናም እነዚህ የጠቀስናቸው የካፊር ቡድኖች እስልምናን ከሚሞግቱ ነገር ግን እያፈረሱት ከሚገኙ የኩፍር አንጃዎች መካከል ጥቂቶቹ ናቸው። በመሆኑም አስተዋይ ልቦና ያለህ የትም ቦታ ያለህ ሙስሊም ሆይ! እስልምና ሙግት ብቻ አይደለም። ይለቁንም ቁርአንንና ሶሒሕ መሆናቸው የተረጋገጡ የነብዩ ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም ሓደሦችን በሚገባ አውቆ መተግበር ነው። ታላቁን ቁርአንና የመልእክተኛውን ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም ሓዲሦችን በሚገባ አስተንትናቸው ቀና መንገድ፣ ብርሃንንና የላቀው ጌታ ዘንድ በሚገኘውን የፀጋ ሀገር በጀነትን ደስተኛ ለመሆን የሚያበቃውን ቀጥተኛውን መንገድ ታገኝበታለህ።
***
የመዳን ጥሪ:
አንተ አስተዋይ ልቦና ያለህ ወንድም ሁን ሴት እስካሁንም እስልምናን ያልተቀበልክ ሰው ሆይ! ... ይህንን የመዳን እና የስኬት ጥሪ እንዲህ በማለት ለርሶ አቀርብሎታለሁ:
ከሞተ በኋላ በመቃብር ውስጥ እና ከዚያም በገሃነም እሳት ውስጥ ካለው የኃያሉ አምላክ ቅጣት ራሶን ያድኑ።
አላህን በጌትነቱ፤ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) በመልእክተኛነታቸው እንዲሁም እስልምናን በሃይማኖትነት በማመን ራሶን ያድኑ። በእውነተኝነትም እንዲህ ይበሉ፦ “ላ ኢላሃ ኢለሏህ ሙሓመዱን ረሱሉሏህ” “ከአላህ በቀር በእውነት የሚመለክ ሌላ አምላክ የለም፤ ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ ናቸው።” ከዚያም አምስቱን ሶላቶች ይስገዱ፣ ከገንዘብዎም ዘካን ያውጡ፣ የረመዷን ወርንም ይፁሙ፣ ለማድረጉ ችሎታው ካለዎት ደግሞ ወደ ተከበረው የአላህ ቤት ሐጅ ያድርጉ።
እስልምና መቀበልዎን ለአላህ ያውጁ፤ ምክንያቱም መዳንም ሆነ ደስተኝነት [84] በዚህ ካልሆነ በቀር የለዎትምና።
[84] በቅርቢቱ ዓለም በመልካም ሕይወት ሲሆን በመጨረሻይቱም አለም ደግሞ ጀነት ናት።
ከእርሱ በቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ በሌለው በልዑል አምላክ እምልላችኋለሁ ይህ የእስልምና ሃይማኖት አላህ ከእርሱ በቀር ሌላን ሃይማኖት ከማንም የማይቀበልበት የሆነ ብቸኛ እውነተኛ ሃይማኖት ነው። እኔም አላህ፣ መላእክቱ እና ፍጥረታቱ ሁሉ ምስክር ይሁኑኝ ከአላህ በቀር ሌላ በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውንና እስልምናም እውነተኛ (ሃይማኖት) መሆኑን እኔም ከሙስሊሞች አንዱ መሆኔን እመሰክራለሁ።
አላህን ጥራት ይግባውና በፀጋውና በቸርነቱ እኔን፣ ዝርዮቼንም መላ ሙስሊም ወገኖቼንም እውነተኛ ሙስሊም አድርጎ እንዲገድለን፤ በጀነትም ውስጥ እውነተኛና ታማኝ ከሀኦኑት ነቢያችን ሙሀመድ፣ ከመላው ነብያቶች ጋር እንዲሁም ከነብያችን ቤተሰቦችና ባልደረቦቻቸውም ጋር አንድ ላይ እንዲያሰባስብን አላህን እለምነዋለሁ። በተጨማሪም ይህንን መጽሐፍ ያነበበም ሆነ የሰማ ሁሉ እንዲጠቅምበት የላቀውን አላህ እማፀነዋለሁ። ... የሚጠበቅብኝን (መልዕክት) አላደረስኩምን? አላህ ሆይ ምስክር ሁነኝ።
አላህም የበለጠ ዓዋቂ ነው። የአላህም ሰላትና ሰላም በነብያችን ሙሐመድ በቤተሰቦቻቸውና በባልደረቦቻቸው ላይ ሁሉ ይስፈን። ምስጋና ሁሉ ለዓለማት ጌታ ለአላህ የተገባ ነው።
***