العقيدة الصحيحة وما يضادها
تكلم المؤلف في هذا الكتيب الصغير عن العقيدة الصحيحة التي تتلخص في: الإيمان بالله، وملائكته، وكتبه، ورسله، واليوم الآخر، وبالقدر خيره وشره، فهذه الأمور الستة هي أصول العقيدة الصحيحة عند أهل السنة والجماعة. وقد شرح الشيخ في الكتاب هذه الأصول الستة مستدلًا بالكتاب والسنة وما عليه سلف هذه الأمة، ثم تكلم عن مسألة الإيمان وقرر أنه قول وعمل يزيد بالطاعة وينقص بالمعصية. ثم ذكر مسألة الولاء والبراء وواجب المسلم تجاه أخيه في الدين. ثم شرع في ذكر المنحرفين عن هذه العقيدة الصحيحة مع ذكر أصنافهم، وذكر شبهة المعاصرين وأنها هي نفس شبهة الأولين، وذكر بعض العقائد الكفرية وما زاده المشركون المتأخرون على الأولين. وأكد الشيخ أن النصر لا يأتي إلا بإخلاص العبادة لوجه الله تعالى وحده لا شريك له، ثم ختم هذا الكتيب بذكر نواقض الإسلام.
ትክክለኛ ዐቂዳ እና ተቃራኒው እንዲሁም እስልምናን የሚያፈርሱ ነገሮች
ጸሐፊ
የተከበሩ ሸይኽ ዐብዱልዐዚዝ ቢን ዐብደላህ ቢን ባዝ
በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በሆነው
መቅድም
ምስጋና ሁሉ ለብቸኛው አላህ የተገባ ነው። የአላህ ሰለላትና ሰላም ከእሳቸው በኋላ ነብይ የሌለ በሆኑት ነብይ፣ በቤተሰቦቻቸውና በባልደረቦቻቸውም ላይ ይስፈን።
በመቀጠል፦ ትክክለኛውን ዓቂዳ (እምነት) መያዝ የእስልምና መሰረት እና የሃይማኖቱም ምሰሶ በመሆኑ የሙሓደራችንም (የትምህርታችንም) ርእስ ይኸው እንዲሆን አሰብኩ። ከቁርኣንና ሐዲሥ ሸሪዓዊ ማስረጃዎች መረዳት እንደሚቻለው የትኛውም ቃልም ይሁን ተግባር ትክክል የሚሆነውም ተቀባይነት የሚያገኘውም ትክክለኛ ዓቂዳ (እምነት) ካለው ሰው ሲሆን ነው። ስለዚህም እምነቱ ትክክለኛ ካልሆነ የእርሷ ቅርንጫፍ የሆኑት ንግግርም ተግባራትም ውድቅ ይሆናሉ ማለት ነው። ልክ የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ እንዳለን፦ {ዛሬ መልካሞች ሁሉ ለናንተ ተፈቀዱ፤ የእነዚያም መጽሐፍን የተሰጡት ሰዎች ምግብ (ያረዱት) ለእናንተ የተፈቀደ ነው፤ ምግባችሁም (እርዳችሁ) ለነሱ የተፈቀደ ነው፤ ከምእመናት ጥብቆቹም ከእነዚያ ከእናንተ በፊት መጽሐፍን ከተሰጡት ሴቶች ጥብቆቹም፤ ዘማዊዎችና (ዝሙተኞች) የምስጢር ወዳጅ ያዢዎች ሳትኾኑ ጥብቆች ኾናችሁ መህሮቻቸውን በሰጣችኋቸው ጊዜ (ልታገቡዋቸው የተፈቀዱ ናቸው)፡፡ ከእምነትም የሚመለስ (የሚቀለበስ) ሰው በእርግጥ ሥራው ተበላሸ፡፡ በመጨረሻም ቀን እርሱ ከከሳሪዎቹ ነው።} [አል ማኢዳህ፥5] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {ወደ አንተ እና ካንተም በፊት ወደ ነበሩት (ነብያት)፥ ብታጋራ ሥራህ በእርግጥ ይታበሳል፤ በእርግጥም ከከሓዲዎቹ ትኾናለህ ማለት በእርግጥ ራዕይ ተወርዷል።} [አዙመር፥65] ይህንን የተመለከቱ የቁርኣን አንቀጾች እጅግ በርካታ ናቸው። ግልፅ የሆነው የአላህ ኪታብም ይሁን የታማኙ መልዕክተኛ የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን ትክክለኛው እምነት በአላህ፣ በመላዕክቶቹ፣ በመጽህፍቶቹ፣ በመልዕክተኞቹ፣ በመጨረሻው ቀን እና በበጎም ይሁን መጥፎ የአላህ ውሳኔ (ቀደር) ማመንን የሚያጠቃልል ነው። እነኝህ ስድስቱ ነገሮች አላህም መጽሃፍት ያወረደባቸው መልዕክተኛው ሙሐመድንም የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን፤ የላከባቸው የትክክለኛው የእምነት መሰረቶች ናቸው። ከሩቅ ነገሮች ምስጢር ሆነው ሊታመንባቸው ግዴታ የሆኑ ነገሮች እና አላህና መልእክተኛውም - የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን - ያሳወቁት ሁሉ በነዚህ መሰረቶች ስር ይገኛል። ለእነዚህ ስድስት መርሆች ማስረጃቸው በቁርኣንና በሀዲስ እጅግ በጣም ብዙ ነው። ከነዚህ ማስረጃዎ፤ች መካከልም፦ {መልካም ሥራ፥ ፊቶቻችሁን ወደ ምሥራቅና ምዕራብ አቅጣጫ ማዞር አይደለም፤ ነገር ግን መልካም ሥራ፥ በአላህና በመጨረሻው ቀን፣ በመላእክትም፣ በመጻሕፍትም፣ በነቢያትም፣ ያመነ ሰው (ተግባር) ነው።} [አል-በቀራህ፥177] ልቅና ይገባውና እንዲህም ይላል፦ {መልክተኛው፥ ከጌታው ወደ እርሱ በተወረደው አመነ፤ ምእምኖቹም (እንደዚሁ)፤ ሁሉም፥ በአላህ፣ በመላዕክቱም፣ በመጻሕፍቱም፣ በመልክተኞቹም ከመልእክተኞቹ «በአንድም መካከል አንለይም» (የሚሉ ሲሆኑ) አመኑ።} [አል-በቀራህ፥285] የላቀው አላህ እንዲህም ይላል፦ {እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህና በመልክተኛው በዚያም በመልክተኛው ላይ ባወረደው መጽሐፍ በዚያም ከበፊቱ ባወረደው መጽሐፍ እመኑ፤ በአላህና በመላእክቱም፣ በመጽሐፎቹም፣ በመልክተኞቹም፣ በመጨረሻውም ቀን፣ የካደ ሰው (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ።} [አን-ኒሳእ፥136] የላቀው አላህ እንዲህም ይላል፦ {አላህ በሰማይና በምድር ውስጥ ያለን ሁሉ በእርግጥ የሚያውቅ መሆኑን አታውቅምን ይህ በመጽሐፍ ውስጥ (የተመዘገበ) ነው፡፡ ይህ በአላህ ላይ ገር ነው።} [አል-ሐጅ፡ 70] ለነዚህ መሰረታዊ መርሆች ማስረጃ የሚሆኑ ትክክለኛ ሐዲሦች በርካታ ናቸው። ከነዚህም መካከል ሙስሊም በሰሒሕ ኪታባቸው ላይ ከምእመናን መሪ (አሚረል ሙእሚኒን) ዑመር ኢብኑል ኸጣብ - አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸው - የዘገቡትና ጂብሪል ዐለይሂ ሰላም ነቢዩን - የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን - ስለ እምነት የጠየቀበት የታወቀው ሰሒሕ ሐዲሥ ይገኝበታል፤ በሐዲሡም ጅብሪል ነብዩን የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን ስለ ኢማን ሲጠይቃቸው እንዲህ ብለውታል፦ “ኢማን ማለት በአላህ፣ በመላእክቱ፣ በመጻሕፍቱ፣ በመልዕክተኞቹ እና በመጨረሻው ቀን ማመን እና መልካምም ይሁን መጥፎው የአላህ ውሳኔ ቀደር ማመን ነው።” (1) ቡኻሪይ እና ሙስሊም ከአቢ ሁረይራ ዘግበውታል። እነዚህ ስድስቱ የኢማን መሰረቶች፡ ማንኛውም ሙስሊም ጥራት የተገባው አላህን፣ የውመል ቂያማን እና ሌሎች የሩቅ ሚስጥሮችንም በተመለከተ ማመን ያለበትን ሁሉ የሚያጠቃልሉ ናቸው። [1] ሙስሊም አል-ኢማን በሚለው ርእስ ስር (8)፣ ቲርሚዚ አል-ኢማን በሚለው ርእስ ስር (2610)፣ አን-ነሳኢ አል-ኢማን እና ድንጋጌዎቹ በሚለው ርእስ ስር (4990)፣ አቡ ዳውድ አስ-ሱና (4695)፣ ኢብኑ ማጃህ አል-ሙቀዲማህ በሚለው ርእስ ስር (63)፣ አሕመድ (1/27) ዘግበውታል።
የበላይ በሆነው አላህ ማመን
የላቀው አላህ እውነተኛ አምላክ መሆኑና ያለ ምንም ተጋሪ በብቸኝነት ሊመለክ የሚገባው አምላክ መሆኑን ማመን ነው።
ጥራት ይገባውና በላቀው አላህ ማመን ውስጥ ከሚካተቱ መካከል፡- እርሱ ያለ ምንም ተጋሪ በብቸኝነት ሊመለክ የሚገባው አምላክ መሆኑን ማመን ይገኝበታል። ምክንያቱም የባሮቹ ፈጣሪ፣ በጎ የሚውልላቸው፣ ሲሳይንም የሚለግሳቸው፣ ድብቅም ግልፅ ማንነታቸውን ጠንቅቆ የሚያውቅላቸው፣ ከመካከላቸው መልካሞቹን የሚመነዳ ክፉዎቹንም የሚቀጣላቸው ብቸኛ እርሱ በመሆኑ ነው። ሁለቱን ከባባዶች (ሰዎች እና አጋንንትን) የፈጠረውም ስለዚሁ ነው። እንዲህ በማለትም አዟቸዋል፦ {ጂኒንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም።] [አዝ-ዛሪያት፡ 56] {ከነርሱም ምንም ሲሳይ አልፈልግም፡፡ ሊመግቡኝም አልሻም።} [አዝ-ዛሪያት፡ 57] {አላህ እርሱ ሲሳይን ሰጪ የብርቱ ኀይል ባለቤት ነው።} [አዝ-ዛሪያት፡ 58] ጥራት ይገባውና እንዲህም ይላል፦ {እናንተ ሰዎች ሆይ! የፈጠራችሁን እነዚያንም ከናንተ በፊት የነበሩትን (የፈጠረውን) ጌታችሁን ተገዙ፤ (ቅጣትን) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና።} [አል-በቀራህ፡ 21] {(እርሱ) ያ ለናንተ ምድርን ምንጣፍ ሰማይንም ጣራ ያደረገ ነው፤ ከሰማይም (ከደመና) ውሃን ያወረደ በርሱም ከፍሬዎች ለናንተ ሲሳይን ያወጣ ነው፡፡ እናንተም (ፈጣሪነቱን) የምታውቁ ስትኾኑ ለአላህ ባላንጣዎችን አታድርጉ።} [አል-በቀራህ፡ 22] ይህንኑ እውነታ እንዲያብራሩ እና ወደዚህም ጥሪ እንዲያደርጉ ከሚፃረረውም እንዲያስጠነቅቁ የላቀው አላህ መልእክተኞችን ልኮ መጽሐፎችን አውርዷል። ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፡- {በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ «አላህን ተገዙ፤ ጣዖትንም ራቁ» በማለት መልክተኛን በእርግጥ ልከናል።} [አን-ነሕል፡ 36] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ከአንተ በፊትም እነሆ ከእኔ ሌላ አምላክ የለምና ተገዙኝ በማለት ወደርሱ የምናወርድለት ቢኾን እንጅ ከመልክተኛ አንድንም አልላክንም።} [አል-አንቢያእ: 25] አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦ {አሊፍ ላም ራ፤ (ይህ ቁርኣን) አንቀጾቹ በጥንካሬ የተሰካኩ ከዚያም የተዘረዘሩ የሆነ መጽሐፍ ነው፡፡ ጥበበኛ ውስጠ ዐዋቂ ከሆነው ዘንድ (የተወረደ) ነው።} {(እንዲህ በላቸው)፡- «አላህን እንጂ ሌላን አትገዙ፡፡ እኔ ለእናንተ ከርሱ (የተላክሁ) አስፈራሪና አብሳሪ ነ።»} [ሁድ: 1-2] የእነዚህ አምልኮዎች ጭብጥ አምላክ በሚመለክባቸው አጠቃላይ አምልኮዎች አላህን ብቸኛ አድርጎ ማምለኩ ነው። ድካ በደረሰ ተስፋና ስጋት፣ በዱዓ፣ በሰላት፣ በፆም፣ በእርድ፣ በስለት ከዚህም ውጭ ባሉ የአምልኮ ዓይነቶች ሁሉ በመተናነስ፣ በክጃሎትና በፍርሀት አኳኋን ሆኖ ለላቀው አላህ የተሟላ ውዴታንና ለልቅናው መዋረድን በተላበሰ መልኩ ማምለክ ነው። የተከበረው ቁርአን አብዛኛው ክፍል ይህንን ታላቅ መሰረት አፅንኦት በመስጠት የወረደ ነው። {አላህንም ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ ያጠራህ ኾነህ ተገዛው።} {ንቁ! ፍጹም ጥሩ የኾነው ሃይማኖት የአላህ ብቻ ነው።} [አዝ-ዙመር: 2-3] ጥራት ይገባውና እንዲህም ይላል፦ {ጌታህም (እንዲህ ሲል) አዘዘ፡- እርሱን እንጂ ሌላን አትገዙ።} [አል-ኢስራእ: 23] ተከታዩም የአሸናፊውና ኋያሉ አላህ ቃል፦ {አላህንም ከሓዲዎች ቢጠሉም ሃይማኖትን ለእርሱ አጥሪዎች ሆናችሁ ተገዙት።} [ጋፊር: 14] በሶሒሕ ቡኻሪይና ሙስሊም ከሙዓዝ - አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውው - በተላለፈ ሓዲሥ ነብዩ - የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን - እንዲህ ማለታቸው ተዘግቧል፡- "አላህ በባሮቹ ላይ ያለው መብት በእርሱ ምንንም ሳያጋሩ በብቸኝነት ሊያመልኩት ነው።"(2) [2] አል-ቡኻሪይ አል-ጂሃድ እና ገድል በሚለው ርእስ ስር (2701)፣ ሙስሊም አል-ኢማን በሚለው ርእስ ስር (30)፣ አት-ቲርሚዚይ አል-ኢማን በሚለው ርእስ ስር (2643)፣ ኢብኑ ማጃህ አዝ-ዙህድ በሚለው ርእስ ስር (4296)፣ አሕመድ (5/238) ዘግበውታል።
አላህ በባሮቹ ላይ ግዴታ ባደረገባቸውና በደነገገላቸው ሁሉ ማመን። አምስቱ ግልፅ የእስልምና ማእዘናትን ይመስል፦
አላህ በባሮቹ ላይ ግዴታ ባደረገባቸውና በደነገገላቸው ሁሉ ማመን። አምስቱ ግልጽ የእስልምና ማእዘናትን ይመስል እነዚህም፦ ከአላህ በስተቀር በእውነት አምልኮ የሚገባው አለመኖሩንና ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን መመስከር፣ ሶላት መስገድ፣ ዘካ መስጠት፣ ረመዳንን መፆም፣ የመንገዱን ጣጣ ለቻሉም ወደ ተከበረው የአላህ ቤት ሄዶ ሐጅ ማድረግ እና ሌሎችም እጅግ የጠራ የሆነው እስልምና በደነገጋቸው ግዴታዎች ማመን ነው።
ከእነዚህ ምሶሶዎች ውስጥ ዋነኛውና ትልቁ ከአላህ በስተቀር በእውነት አምልኮ የሚገባው ሌላ አምላክ አለመኖሩንና ሙሐመድም የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን መመስከር ነው። ላኢላሃ ኢለሏህ የሚለው የምስክርነት ቃል ትርጉሙ ከአላህ በስተቀር በእውነት አምልኮ የሚገባው ሌላ አምላክ እንደሌለ መመስከር በመሆኑ አላህን ብቻ መገዛትን እና ሌላ ማንኛውንም ነገር ከመገዛት መቆጠብን ያስፈርዳል። ስለዚህም ከእርሱ በቀር ሌላ የሚመለክ ሁሉ ሰውም ይሁን መልአክ ጂኒም ሌላም ሌላም ቢሆን የሚመለከው በውሸት ነው። በእውነት የሚመለከው የላቀው አላህ ብቻ ነው። ጥራት ይገባውና ልክ እንዲህ እንዳለን፡- {ይህ አላህ እርሱ እውነት በመሆኑ ከእርሱም ሌላ የሚግገዙት ነገር እርሱ ፍጹም ውሸት በመሆኑ አላህም እርሱ የሁሉ በላይ ታላቅ በመኾኑ ነው።} [አል'ሐጅ፡ 62] ጥራት የተገባው አላህ ሁለቱን ከባባድ ፍጥረታት ለዚህች ቀዳሚ መርሕ ብሎ የፈጠረ፣ መልዕክተኞቹንም የላከ ኪታቦቹንም ያወረደ እንደሆኑና በእርሱም እንዳዘዛቸው ቀደም ብለን አሳልፈናል። ከዚህ አንፃር ይህንን ቁም ነገር በደንብ አስተውል፤ ድጋኘህ አስተንትን፤ ይኼኔ ብዙሀኑ ሙስሊሞች ይህን እጅግ መሰረታዊ ነገር ላይ ከባድ ጅህልና ላይ የመሆናቸው እውነታ ፍንትው ብሎ ይታይሃል፤ (ካለማወቃቸው የተነሳ) ከአላህ ጋር በማድረግ ከእርሱ ውጪ ያሉ አካላትን እስከማምለክና የእርሱን ብቸኛ መብት ከእርሱ ውጪ ላሉ አካላት እስከመስጠት ደረጃም ደርሰዋል። አሏሁል ሙስተዓን!
አላህ የዓለም ፈጣሪ፣ የጉዳዮቻቸው አስተናባሪ፣ በዕውቀቱም በኃይሉም የነርሱ አስተዳዳሪ መሆኑን ማመን ይገኝበታል።
ጥራት በተገባው አላህ ከማመን መካከል አላህ የዓለም ፈጣሪ፣ የጉዳዮቻቸው አስተናባሪ፣ በዕውቀቱም በኃይሉም እንደፍላጎቱ አድርጎ የሚያስተዳድራቸው መሆኑን፤ እንዲሁም እርሱ የዱኒያውም የአኺራውም ባለቤት መሆኑን፤ ከእርሱ ውጭ ፈጣሪ የሌለ ከእርሱም ውጭ ጌታ የሌለ ብቸኛ መሆኑንም ማመን ይገኝበታል። ባርያዎቹ በቅርቡም ወደፊትም ሊስተካከሉ ዘንድ ስኬታቸው ጽድቃቸውም ወደሚገኝበት ጥሪ እንዲያደርጉ መልእክተኞቹንም ልኮ መጽሐፎቹንም አውርዷል። ጥራት ይገባውና የላቀው አላህ በዚህ ሁሉ ምንም ተጋሪ የለውም። ልክ እንዲህ እንዳለን፦ {አላህ የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ አስተናባሪ ነው።} [አዝ-ዙመር፡ 62] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ጌታችሁ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ አላህ ነው፡፡ ከዚያም ከዐርሹ በላይ ከፍ አለ፡፡ (አላህ) ሌሊትን በቀን ፈጥኖ የሚፈልገው ሲሆን ይሸፍናል፡፡ ፀሐይንና ጨረቃንም ከዋክብትንም በትእዛዙ የተገሩ ሲሆኑ (ፈጠራቸው)፡፡ ንቁ! መፍጠርና ማዘዝ የእርሱ ብቻ ነው፡፡ የዓለማት ጌታ አላህ (ክብሩ) ላቀ።} [አል-አዕራፍ፡ 54]
በተዋቡ ስሞቹ እና በታላላቅ ባህሪያቱ ያለ ማዛባት፣ ውድቅ ሳያደርጉ፣ ዝርዝር ሁኔታ ውስጥ ሳይገቡና ከማንም ጋር ሳያመሳስሉ ማመንንም ያጠቃልላል።
በአላህ ማመን ውስጥ ከሚካተቱ መካከል፦ በታላቁ ኪታቡ እና ከታማኙ መልዕክተኛው በተረጋገጡ ሐዲሦች የፀደቁ በሆኑ የተዋቡ ስሞቹ እና በታላላቅ ባህሪያቱ ያለ ማዛባት፣ ውድቅ ሳያደርጉ፣ ዝርዝር ሁኔታ ውስጥ ሳይገቡና ከማንም ጋር ሳያመሳስሉ ማመንንም ይጨምራል። የምናምነውም ልክ በተገለፀበት አኳኋን ታላላቅ ፍቺያቸውንም በማመን በማናቸውም ባህሪያቱ ከፍጡራኑም ጋር ባለማመሳሰል ለእርሱ በሚገባው መልኩ ነው። ልክ የላቀው አላህ እንዲህ እንዳለን፡- {የሚመስለው ምንም ነገር የለም።} [አሽ'ሹራ፡ 11] አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ለአላህም አምሳያዎችን አታድርጉ። አላህ (መሳይ እንደሌለው) ያውቃል። እናንተ ግን አታውቁም።} [አን'ነሕል፡ 74] ይህ ደግሞ የአላህ መልእክተኛ ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ባልደረቦች እና ቅን ተከታዮቻቸው የሆኑት የአህለል ሱና ወል-ጀማዓዎች እምነት ነው። ኢማሙ አቡ አል-ሐሰን አል-አሽዓሪይ አላህ ይዘንላቸውና “አልመቃላቱ ዓን አስሓቢል ሐዲሢ ወአህለ ሱናህ” በተሰኘው ኪታባቸው ያስተላለፉት ሌሎችም የዒልምና የኢማን ሰዎችም ያስተላለፉት ነው።
አል-አውዛዒይ አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ ብለዋል፡- አዝ-ዙህሪይ እና መክሑልም የአላህን ባህሪያት ስለሚገልፁ አንቀጾች ተጠይቀው እንዲህ ብለዋል፦ እንደአመጣጡ አሳልፉት። አል-ወሊድ ቢን ሙስሊም አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ ብለዋል፡- ማሊክ፣ አል-አውዛዒይ፣ አል-ለይሥ ቢን ሰዕድ እና ሱፍያን አሥ-ሠውሪይ አላህ ይዘንላቸውና የአላህን ባህሪያት የሚገልፁ አንቀፆች በተመለከተ ተጠይቀው ያሉት: "ዝርዝር ሁኔታ ውስጥ ሳትገቡ ልክ እንደመጣው አፅድቁት።" አል-አውዛዒይ አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ ብለዋል፡- ታቢዒዮች በርከት ብለው በሚገኙበትም አጋጣሚ ጥራት የተገባው አላህ ከዓርሹ በላይ ነው እንልም ነበር፤ በሓዲሥ በተጠቀሱት ባህሪያትም እናምናለን። የማሊክ ሸይኽ የሆኑት ረቢዓህ ኢብኑ አቢ ዐብዱረሕማን ሁለቱንም አላህ ይዘንላቸውና ስለ ኢስቲዋእ ሲጠየቁ እንዲህ አሉ፡- (አል-ኢስቲዋእ የታወቀ ነው፤ አኳኋኑ በአዕምሮ የሚደረስበት አይደለም፤ መልእክቱ ከአላህ ዘንድ የመጣ ነው፤ መልዕክተኛው የሚጠበቅበት ግልጽ አድርጎ ማድረስ ነው፤ ማመኑ የኛ ፋንታ (ግዴታ) ነው።) በዚሁ ጉዳይ ኢማሙ ማሊክ አላህ ይዘንላቸውና በተጠየቁ ጊዜም እንዲህ አሉ: (አል-ኢስቲዋእ የታወቀ ነው፤ አኳኋኑ በአዕምሮ የማይደረስበት ነው፤ ማመኑ ግዴታ ነው፤ ስለ ጉዳዩ -በዚህ መልኩ- መጠየቅ ቢድአ (ፈጠራ) ነው።) ከዚያም ጠያቂውን እንዲህ አሉት: ”መጥፎ ሰው (የቢድዓ) መስለህ ነው የታየሀኝ! “ብለው እንዲወጣላቸው አዘዙ።
ይኸው መልዕክት የሙእሚኖች እናት ከሆነችው ኡሙ ሰላማህ - ረዲየሏሁ ዓንሃ - ተላልፏል። ኢማም አቡ ዐብዱረሕማን ኢብኑል ሙባረክ አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ ብለዋል፡- (የላቀው ጌታችን አላህ በሰማያት ላይ ከፍጡራኑ ተለይቶ ከዓርሹ በላይ መሆኑን እናውቃለን።) ኢማሞች በዚህ ረገድ የተናገሩት ቃል በዚሁ ጥንቅር ብቻ ለማሰባሰብ የማይመች ብዛት አለው። በመሆኑም በርእሰ ጉዳዩ የተላለፉ ሃሳቦችን በተሻለ መልኩ መረዳት የሚፈልግ የሱና ሊቃውንት የፃፉትን ይከልስ። ለምሳሌ፦ በዐብደሏህ ቢን ኢማም አሕመድ የተፃፈውን "አስ-ሱና" የሚለውን ኪታብ፤ በታላቁ ኢማም ሙሐመድ ቢን ኹዛይማህ የተፃፈውን “ተውሒድ” የተሰኘውን ኪታብ፤ እንዲሁም በአቡ አል-ቃሲም አል-ላለካኢይ አጥ-ጦባሪይም የተፃፈውን "አስ-ሱና" የተሰኘውን ኪታብ፤ በአቡበክር ቢን አቢ ዓሲም የተፃፈውን “አስ-ሱና” የተሰኘውን ኪታብ እና ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያህ አላህ ይዘንላቸው ለሐማዊዮች የሰጡትን መልስ ይከልስ። ሸይኹል ኢስላም በመልሱ የአህለ ሱና ዓቂዳን አብራርተው ተቃዋሚዎቻቸው ስለሚያመጡት ሙግት ስህተትነትም ሸሪዓዊ እና አመክንዮአዊ ማስረጃውን የሱና ሰዎችንም ንግግር ትክክለኛነት እና በርእሰ ጉዳዩ የተናገሩትን ብዙ ቃላቶቻቸውንም አስተላልፈዋል። ልክ እንደዚሁ ተድሙሪያ ብለው በሰየሙት አነስ ያለ ይዘት ባለው ኪታባቸው ላይም እንዲሁ የአህለሱና ወልጀማዓን አቋም ባለው ሸሪዓዊም አእምሯዊም ማስረጃዉን አብራርተው፤ እውነታውን ለመረዳት በቅን ልቦና ሐቅ ፈላጊ ሁሉ ሊመራ በሚችል መልኩ እውነታን ግልፅ አድርገው ሃሰትን በሚንድ አኳኋን የሚገባውን ማብራርያ አድርገውበታል። አህሉሱናዎችን በአላህ ስምና ባህርያት ዙርያ ባላቸው አቋም ዓቂዳቸውን የተቃረናቸው ሁሉ በሚያፀድቀውም በሚያወግዘውም አቋሙ ግልፅ በሆነ መልኩ እርስበራሱ የሚጋጭ ከመሆኑም ባሻገር የቁርአንና ሓዲሥ ማስረጃዎችንም አእምሮንም የሚጋጭ አቋም እናዳለው የሚያጠራጥር አይደለም።
አህለ-ሱንና ወል-ጀማዓ ግን ጥራት ለተገባው አላህ በተከበረው ኪታቡ ለራሱ ያፀደቀውን ወይም መልዕክተኛው ሙሐመድ - ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም - ሶሒሕ በሆነ ሓዲሥ ለአላህ ያፀደቁትን ያለምንም ማመሳስል አፅድቀው፤ ጥራት ይገባውና ከፍጡራን ከመመሳስልም ጥርት ባለ መልኩ የጠራ መሆኑን ያፀደቁ ናቸው። በዚህም ከተቃርኖ ርቀው የመጡትን ማስረጃዎችንም ሁሉ በተግባር ላይ ማዋል ቻሉ። ይህ ደግሞ አላህ መልዕክተኞቹ ይዘው የመጡትን ትክክለኛ መመርያ በሚገባ ለሚከተል፤ የሚቻለውን ያክልም እውነታን ፍለጋ ለሚጣጣር ሁሉ ፈለግ ያደረገላቸው ነው። ልክ የላቀው አላህ እንዲህ እንዳለን ፡- {በእርግጥ እውነትን በውሸት ላይ እንጥላለን፡፡ አንጎሉን ያፈርሰዋልም፡፡ ወዲያውም እርሱ ጠፊ ነው።} [አል'አንቢያእ፡ 18] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {በጥያቄም አይመጡብህም እውነተኛውን (መልስ) መልካምን ፍችም የምናመጣልህ ብንኾን እንጅ።} [አል'ፉርቃን፡ 33] አል-ሓፊዝ ኢብኑ ከሢር ረሒመሁላህ ተከተዩን የልዕለ ኋያሉን አላህ አንቀፅ በተመለከተ በታዋቂው የተፍሲር ኪታባቸው የሚከተለውን አውስተዋል፦ {ጌታችሁ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ አላህ ነው፡፡ ከዚያም ከዐርሹ በላይ ከፍ አለ።} [አል'አዕራፍ፡ 54] በዚሁ ጉዳይ ብናወሳው መልካም የሆነን ጥሩ ንግግር አላቸው። ካለው ፋይዳ አንፃር እናወሳዋለን፡ አላህ ይዘንላቸውና እንዲህ በሚል አውስተዋል፡- በዚህ ጉዳይ ሰዎች እጅግ በርከት ያለ ቃል አላቸው። ይህ ቦታ ታዲያ የነሱን ቃል የምናብራራበት አይደለም። ይልቁን እኛ በዚህ ቦታ የምንከተለው የደጋግ ቀደምት አባቶች የነ ኢማም ማሊክ፣ የነ አል-አውዛዒን፣ የነ አሥ-ሠውሪይን፣ የነአል-ለይሥ ቢን ሰዕድን፣ የነ አልሻፊዒይን፣ የነ ኢማም አሕመድን፣ የነ ኢስሓቅ ቢን ራህወይህን እንዲሁም ሌሎችም የጥንትም የዘመናችንም የህዝበ ሙስሊሙ ታላላቅ ኢማሞችን ፈለግ ነው። ይኸውም ያለማጣጣም፣ ያለ ማመሳሰልና ውድቅም ሳናደርግ እንደመጣው ማፅደቅ ነው። አላህን ከፍጡራኑ ጋር ወደሚያመሳስሉ ሰዎች አእምሮ ከሚመጣው ምስል ሁሉ አላህ የጠራ ነው። ምክንያቱም አላህ ከማናቸውም ፍጡራኑ ጋር የማይመሳሰልና ምንም አይነት ፍጥረትም እርሱን የማይመስል በመሆኑ እርሱም ሰሚ እና ተመልካች በመሆኑ ነው። ከዛም ባሻገር ጉዳዩ እንደነ የቡኻሪይ ሸይኽ ኑዐይም ኢብኑ ሐምማድ አል-ኹዘዒይ እንዳሉት: "አላህን ከፍጡራኑ ጋር ያመሳሰለ ከፍሯል፤ አላህ ራሱን የገለፀበትን ባህሪይ ያወገዘም እንዲሁ ከፍሯል፤ አላህ ራሱን ከገለፀበት መገለጫም ይሁን መልዕክተኛው አላህን ከገለፁበት መገለጫ ከፍጡራን ጋር ማመሳሰል የሚባል ነገርም የለም። በመሆኑም በግልፅ የቁርአን አንቀፅና ሶሒሕ በሆነ ሓዲሥ ለአላህ የፀኑ መገለጫዎች ለአላህ በሚገባው መልኩ ያፀደቀ፤ አላህም ከእንከን ያፀዳ መሆኑን ያመነ ቀናውን ጎዳና ተጉዟል።"
በመላእክት ማመን
በመላእክት ማመንን በተመለከተ፡- በነሱ ማመን ሲባል ጥቅል በሆነ መልኩ እና በዝርዝር ማመንን የሚያካትት ነው። ሙስሊም አላህ መላእክትን ሊታዘዙት ዘንድ የፈጠራቸው፤ የተከበሩ ባርያዎች እንደሆኑ የገለፃቸው፤ በቃል እንኳ ቀደም ቀደም የማይሉ እና ለትእዛዙም ታዛዥ የሆኑ መላእክቶች እንዳሉት ያምናል። {በፊታቸው ያለውንና በኋላቸው ያለውንም ሁሉ ያውቃል። ለወደደውም ሰው እንጅ ለሌላው አያማልዱም። እነርሱም እርሱን ከመፍራታቸው የተነሳ ተጨናቂዎች ናቸው።} [አል'አንቢያእ፡ 28] መላእክቶች ብዙ አይነት ናቸው። ከመካከላቸው የዐርሽ ተሸካሚዎች አሉ፤ ከመካከላቸውም የጀነት እና የጀሀነም በር ጠባቂዎች አሉ፤ ከመካከላቸውም የፍጡራንን ስራ የመመዝገብ አደራ የተሰጣቸው አሉ። አላህና መልዕክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በስማቸው የጠቀሱልንን እንደ ጂብሪል፣ ሚካኢል እና የጀሀነም በር ጠባቂው ማሊክን በመሳሰሉት መላእክትም ዘርዘር ባለ መልኩ እናምናለን። ጥሩንባውን የመንፋት ኋላፊነት በተሰጠው ኢስራፊልም እናምናለን። ስለ ኢስራፊል በትክክለኛ ሐዲሶች ላይም ተጠቅሷል። ከዓኢሻ ረዲየሏሁ ዓንሃ በተላለፈ ሶሒሕ ሐዲሥ ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) እንዲህ ብለዋል፡- “መላእክት የተፈጠሩት ከብርሃን ነው፤ ጋኔኖችም ከእሳት ከሆነ ነበልባል ተፈጠሩ። አደም ደግሞ ለእናንተ ከተገለፀላችሁ ነው የተፈጠረው።” (3) ሙስሊም በሶሒሓቸው ላይ ዘግበውታል። [3] ሙስሊም አዝ-ዙህድ ወር-ረቃኢቅ (2996)፣ አሕመድ (6/153) ላይ ዘግበውታል።
በመጻሕፍት ማመን
ልክ እንደዚሁ በኪታቦች ማመንን በተመለከተም ጥራት የተገባው አላህ ለነቢያቱና ለመልዕክተኞቹ እውነታውን እንዲያብራሩ እና ወደ እርሱም ጥሪ እንዲያደርጉ ያግዛቸው ዘንድ ኪታቦችን ያወረደላቸው መሆኑን ማመን ግዴታ ነው። {መልክተኞቻችንን በግልጽ ማስረጃዎች በእርግጥ ላክን። ሰዎችም በትክክል ቀጥ እንዲሉ መጽሐፎችንና ሚዛንን ወደእነርሱ አወረድን} [አል'ሐዲድ፡ 25] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {ሰዎቹ ሁሉ አንድ ሕዝብ ነበሩ፤ (ተለያዩ)። አላህም ነቢያትን አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች አድርጎ ላከ። ከእነርሱም ጋር መጻሕፍትን በሰዎቹ መካከል በዚያ በርሱ በተለያዩበት ነገር ይፈርድ ዘንድ በእውነት አወረደ።} [አል'በቀራህ፡ 213]
እንደ ተውራት፣ ኢንጅል፣ ዘቡር እና ቁርኣን አላህ ስማቸውን በጠቀሰልን ኪታቦችም ዘርዘር ባለ መልኩ እናምናለን። ቁርአን ከመካከላቸው በላጭና የመጨረሻው ሲሆን ከሌሎቹ ሁሉ የበላይ እና አረጋጋጫቸው መሆኑንም ጭምር እናምናለን። ህዝቡ ሁሉ ከመልዕክተኛው ሰለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም ከመጡ ሶሒሕ ሐዲሦች ጋር አጣምረው ሊከተሉትና ሊፋረዱበትም ግዴታቸው ነው። ምክንያቱም ጥራት የተገባው አላህ መልዕክተኛው ሙሐመድ ሰለሏሁ ዓለይሂ ወሰለምን ወደ ሁለቱም ከባባዶች (ሰዎችና ጂኖች) መልዕክተኛ አድርጎ ነውና የላካቸው። ይህንኑ ቁርአንም ሰዎችና አጋንንት ሊፋረዱበት ዘንድ ነው ያወረደላቸው። ለልቦና ፈውስ፣ ለሁሉም ነገርም ማብራርያ፣ ለሙእሚኖችም መመርያ እና እዝነት አድርጎታል። የላቀው አላህ እንዲህ እንዳለን፦ {ይህም ያወረድነው የሆነ የተባረከ መጽሐፍ ነው። ተከተሉትም። ይታዘንላችሁም ዘንድ (ከክህደት) ተጠንቀቁ።} [አል'አንዓም፡ 155] ጥራት ይገባውና እንዲህም ይላል፦ {መጽሐፉንም ለሁሉ ነገር አብራሪ፣ መሪም፣ እዝነትም፣ ለሙስሊሞችም አብሳሪ ኾኖ ባንተ ላይ አወረድነው።} [አን'ነሕል፡ 89] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው፡- «እናንተ ሰዎች ሆይ! እኔ ወደናንተ ወደሁላችሁም የአላህ መልክተኛ ነኝ። (እርሱም) ያ የሰማያትና የምድር ንግሥና ለእርሱ ብቻ የኾነ ነው። እርሱ እንጂ ሌላ አምላክ የለም። ሕያው ያደርጋል። ይገድላልም። በአላህ በዚያም በአላህና በቃላቶቹ በሚያምነው የማይጽፍ የማያነብ ነቢይ በኾነው መልክተኛው እመኑ። ቅንንም መንገድ ትመሩ ዘንድ ተከተሉት።»} [አል'አዕራፍ፡ 158] የእነዚህን መሰል ጽንሰ ሀሳብ ያዘሉ በርካታ የቁርኣን አንቀጾች አሉ።
በመልዕክተኞች ማመን
በመልዕክተኞች ማመንም እንዲሁ በጥቅሉና በዝርዝር ሁኔታ ነው። በዚህ መሰረትም ጥራት የተገባው አላህ ወደ ባሮቹ ከመካከላቸው የሆነ መልዕክተኞችን እንደላከ እናምናለን፤ እነርሱም አብሳሪዎች፣ አስፈራሪዎችና ወደ እውነትም ተጣሪዎች አድርጎ የላካቸው መሆኑን እናምናለን። እነርሱን አምኖ የተቀበላቸው በደስታ ስኬትን ይጎናፀፋል፤ የተቃወማቸው ደግሞ ክስረትን ይከናነባል። የመጨረሻቸውና ከመካከላቸው በላጩ ነብያችን ሙሐመድ ቢን ዐብደላህ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ናቸው። ልክ የላቀው አላህ እንዲህ እንዳለን ማለት ነው፦ {በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ «አላህን ተገዙ፤ ጣዖትንም ራቁ» በማለት መልክተኛን በእርግጥ ልከናል።} [አን'ነሕል፡ 36] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {ከመልክተኞቹ በኋላ ለሰዎች በአላህ ላይ አስረጅ እንዳይኖር አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች የኾኑን መልክተኞች (ላክን)። አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው።} [አን'ኒሳእ፡ 165] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ሙሐመድ ከወንዶቻችሁ የአንድም ሰው አባት አይደለም። ግን የአላህ መልክተኛና የነቢዮች መደምደሚያ ነው።} [አል'አሕዛብ፡ 40] አላህ በስማቸው የጠራልንን ወይም ስማቸው ከአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ዘንድ የተረጋገጡልን ነብያቶችና ሩሱሎች እንደ ኑሕ፣ ሁድ፣ ሷሊሕ፣ ኢብራሂም እና ሌሎችም - በላጭ እና የጠራ የሆነው ሶላት እና ሰላም በእነርሱም በነብያችንም ላይ ይስፈንና - እንደተነገረን በዝርዝር እናምናለን።
በመጨረሻው ቀን ማመን
በመጨረሻው ቀን ማመንን በተመለከተ፡-
ከሞት በኋላ የሚሆነውን በተመለከተ አላህና መልዕክተኛው - ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም - በነገሩን ሁሉ እንደ የቀብር ፈተና፣ የቀብር ቅጣትና ፀጋ፣ እንዲሁም በእለተ ትንሳኤ የሚሆነው ከባባድ መጨናነቅ፣ መከራ፣ የሲራጥ ፈተና፣ የስራ መመዘን፣ በስራ መተሳሰብ፣ ምንዳን ማግኘት፣ የስራ መዝገብ ለእያንዳንዱ ሰው መታደል፣ ከሰዎች መካከል የስራ መዝገቡን በቀኙ የሚቀበል እናደለው ሁሉ በግራ እጁ የሚቀበልም አለ ከዛም አልፎ እጁ ተጠምዞ የኋሊት የሚቀበልም እንዳለ ማመንን የሚያጠቃልል ነው። በተጨማሪም ነብያችን ሙሐመድ ሰለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም በተለገሱት "ሐውድ" ማመን፣ በጀነት እና በጀሀነም ማመን፣ ሙእሚኖች የላቀው አላህን የሚመለከቱና አላህም እነርሱን የሚያነጋግራቸው ስለመሆኑ እና ከዚህም ውጭ በተከበረው ቁርአንና ሶሒሕ በሆኑ ከነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በተረጋገጡ ሐዲሦች የመጡ እውነታዎችን ሁሉ ማመንንም የሚያጠቃልል ነው። በመሆኑም ይህንን ሁሉ እውነት ነው ብሎ መቀበልና አላህና መልዕክተኛው (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ባብራሩት መልኩ ማመን ግዴታ ነው።
በቀደር ማመን
በቀደር ማመን ሲባል በአራት ጉዳዮች ማመንን የሚያጠቃልል ነው።
የመጀመርያው ጥራት የተገባው አላህ የሆነውንም የሚሆነውንም ጠንቅቆ የሚያውቅ እንደሆነ፤ የባሪያዎቹንም ሁኔታ ጠንቅቆ የሚያውቅ እንደሆነ፤ ሲሳያቸውን፣ የህይወት ጊዜያቸውን፣ ስራዎቻቸውን እና ከዚህም ውጭ ጉዳዮቻቸውንም ሁሉ የሚያውቅ እንደሆነ፤ ጥራት ይገባውና ከእርሱ የሚደበቅ አንዳችም ነገር የሌለ መሆኑን ማመን ነው። ልክ እንዲህ እንዳለን ማለት ነው፦ {አላህም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ መሆኑን ዕወቁ።} [አል'በቀራህ፡ 231] አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦ {አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ መሆኑን አላህም በነገሩ ሁሉ በዕውቀት ያካበበ መኾኑን በዕውቀት ያካበበ መኾኑን ታወቁ ዘንድ (ይህንን አሳወቃችሁ)።} [አጥ'ጠላቅ: 12]
ሁለተኛው ጉዳይ (ደረጃ)፡- አስቀድሞ የወሰነውንና የፈረደውን ሁሉ በፅሁፍም የመዘገበው መሆኑን ማመን ነው። ጥራት ይገባውና እንዲህ እንዳለን ማለት ነው፦ {ከእነርሱ (አካል) ምድር የምታጎድለውን በእርግጥ ዐውቀናል፡፡ እኛም ዘንድ ጠባቂ መጽሐፍ አልለ።} [ቃፍ፡ 4] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ነገሩንም ሁሉ ገላጭ መሪ በኾነ መጽሐፍ ውስጥ አጠቃለልነው።} [ሱረቱ ያሲን፡ 12] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {አላህ በሰማይና በምድር ውስጥ ያለን ሁሉ በእርግጥ የሚያውቅ መሆኑን አታውቅምን ይህ በመጽሐፍ ውስጥ (የተመዘገበ) ነው፡፡ ይህ በአላህ ላይ ገር ነው።} [አል'ሐጅ፡ 70]
ሦስተኛው ጉዳይ፡ ነገራቶችን እውን በሚያደርገው ፈቃዱ ማመን ነው። በመሆኑም እርሱ የሻው ነገር ይሆናል፤ እርሱ ያልሻው አንዳችም ነገር አይሆንም። ጥራት ይገባውና እንዲህ እንዳለን ማለት ነው፦ {አላህ የሻውን ይሠራልና።} [አል'ሐጅ፡ 18] አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ነገሩም አንዳችን በሻ ጊዜ ሁን ማለት ነው፡፡ ወዲያው ይሆናልም።} [ሱረቱ ያሲን፡ 82] ጥራት ይገባውና እንዲህም ይላል፦ {አላህም ካልሻ በስተቀር አትሹም፡፡ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና።} [አል'ኢንሳን፡ 30]
አራተኛው ጉዳይ (ደረጃ)፡- ማንኛውንም ግኝት ሁሉ የፈጠረው እርሱ መሆኑን ማመን ነው። ከእርሱ ውጭ ፈጣሪም የለም፤ ከእርሱ ውጭ ጌታም የለም። ጥራት ይገባውና እንዲህ እንዳለን ማለት ነው: {አላህ የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ አስተናባሪ ነው።} [አዝ'ዙመር፡ 62] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {እናንተ ሰዎች ሆይ! በእናንተ ላይ (ያለውን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ ከአላህ ሌላ ፈጣሪ አለን? ከሰማይና ከምድርም ሲሳይን የሚሰጣችሁ አለን? ከእርሱ በስተቀር አምላክ (ሰጪም) የለም፡፡ ታዲያ ወዴት ትዞራላችሁ።} [ፋጢር፡ 3] ከእነዚህ ከፊሎቹን ካስተባበሉ የቢድዓ ሰዎች በተቃራኒ አህለሱናዎች ዘንድ በቀደር ማመን በእነዚህ አራት ጉዳዮች ማመንን ያጠቃልላል።
እምነት ንግግርም ተግባርም ነው፤ አላህን በመታዘዝም ይጨምራል አላህን በማመፅም ይቀንሳል።
እምነት ንግግርም ተግባርም መሆኑን፤ አላህን በመታዘዝም የሚጨምር አላህን በማመፅም የሚቀንስ መሆኑን፤ ማንኛውም ሙስሊም እንደ ዝሙት፣ ስርቆት፣ ወለድ መብላት፣ አስካሪ መጠጥ መጠጣት፣ ወላጆችን መጨቆን፣ እና ሌሎች ከሽርክ እና ከኩፍር ያነሱ ወንጀሎችን በመፈፀሙ ብቻ ሐላል ነው ብሎ እስካላለ ድረስ ከእስልምና ወጥቷል ማለት የማይፈቀደ መሆኑን ማመን በአላህ ማመን ውስጥ የሚካተት ነው። ምክንያቱም የላቀው አላህ እንዲህ ስላለን፦ {አላህ በእርሱ ማጋራትን በፍጹም አይምርም። ከዚህ ሌላ ያለውንም (ኀጢአት) ለሚሻው ሰው ይምራል።} [አን'ኒሳእ፡ 48] እንዲሁም የአላህ መልዕክተኛም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በልቡ ውስጥ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያክል የእምነት ክብደት ያለው ሁሉ አላህ ከእሳት እንደሚያወጣው መናገራቸው ሙተዋቲር (በብዙ ሰነዶች የተዘገበ) በሆነ ሓዲሥ የተረጋገጠ በመሆኑም ነው።
ለአላህ ብሎ መውደድ፣ ለአላህ ብሎ መጥላት፣ ወዳጅነትንም ጠላትነትንም ለአላህ ብሎ መመስረት እምነት ውስጥ የሚካተት ነው።
በአላህ ማመን ውስጥ ከሚካተቱ መካከል፡- ለአላህ ብሎ መውደድ፣ ለአላህ ብሎ መጥላት፣ ወዳጅነትንም ጠላትነትንም ለአላህ ብሎ መመስረትንም የሚያካትት ነው። በመሆኑም ሙእሚን ሁሉ ምእመናንን ሊወዳቸውና ሊወዳጃቸው፤ ከሓዲዎችንም ሊጠላና ጠላት አድርጎ ሊይዛቸውም ይገባል። ከምእመናን መካከል የረሱል (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ሶሓቦች ግንባር ቀደም ናቸው። አህለል ሱናህ ወልጀማዓህ የረሱልን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ሶሓቦች ይወዷቸዋል ይወዳጇቸዋልም። ከነብያት በኋላ ከሰዎች ሁሉ በላጭ እንደሆኑም ያምናሉ። ምክንያቱም ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) እንዲህ ስላሉ፦ «ከየትኛውም ትውልድ በላጩ እኔ ያለሁበት ትውልድ (ላይ የነበሩ ትውልዶች ናቸው)። ከዚያም ቀጣዩ ትውልድ ከዚያም ከሱ በኋላ ያለው ትውልድ ነው።»[4] ሶሒሕ ለመሆኑ ተስማምተውበታል። አህለሱናዎች ከመካከላቸውም በላጩ አቡበከር አስ-ሲዲቅ፣ ከዚያም ዑመር አል-ፋሩቅ፣ ከዚያም ዑሥማን ዙን-ኑረይን፣ ከዚያም ዓሊይ አል-ሙርተዷ - አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና - መሆናቸውን፤ ከዛ በኋላ ደግሞ ከአስሩ በጀነት የተበሰሩ ሰሐቦች የተቀሩት -አላህ ሁሉንም መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና - መሆናቸውን ያምናሉ። በሶሓቦች መካከል በተከሰተው አለመግባባት ዙርያ ይታቀባሉ። ሶሓቦቹ በጉዳዩ ሙጅተሂዶች መኾናቸውንና እውነታውን ላገኘ ድርብ ምንዳዎች ከመካከላቸው ስህተት ላይ የነበረውም አንድ አጅር እንዳለው ያምናሉ። በረሱል (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ያመኑትን የረሱል ቤተሰቦችን አህለሱና ወልጀመዓዎች ይወዷቸዋል ይንከባከቧቸዋልም። የረሱል (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ሚስቶችንም የምእመናን እናት እንደመሆናቸው ወዳጅነታቸውን ይጠብቃሉ፤ አላህ መልካም ስራቸውን ይወድላቸውም ዘንድ ለሁሉም ዱዓእ ያደርጓላቸዋል። የአላህ መልእክተኛ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ባልደረቦችን የሚጠሉ፣ የሚዘልፉና በነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ቤተሰቦች ድንበር የሚያልፉና አላህ ከሰጣቸው ደረጃም ከፍ አድርገው ሌላ ደረጃ ላይ የሚደርጓቸው ከሆኑት የራፊዷዎች አካሄድም ራሳቸውን ያጠራሉ። በተቃራኒው የነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ቤተሰቦች አላህ የሰጣቸውን ደረጃ የሚነፍጉ ከሆኑት ነዋሲቦችም ራሳቸውን እንደሚያጠሩት ሁሉ ማለት ነው። [4] የአል-ቡኻሪይ አሽ-ሸሃዳት በሚለው ርእስ ስር (2509)፣ ሙስሊም ፈዷኢሉ ሶሓባህ በሚለው ርእስ ስር (2533)፣ አት-ቲርሚዚይ አል-መናቂብ በሚለው ርእስ ስር (3859)፣ ኢብኑ ማጃህ አል-አሕካም በሚለው ርእስ ስር (2362)፣ እንዲሁም አሕመድ (1/434) ዘግበዋታል።
በዚህች አጭር ቃል የጠቀስነው በሙሉ አላህ መልእክተኛው ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) የላከበት በሆነው ትክክለኛ እምነት ውስጥ የሚካተት ሲሆን የፊርቀቱ ናጂያ አህል አል-ሱና ወል-ጀማዓህ ዓቂዳም ነው። ይኸውም ነቢዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) እርሷን አስመልክተው እንዲህ ያሉት ነው፦ «የአላህ ጉዳይ (ቂያማ) እስኪመጣ ድረስ አዋርዳለሁ ብሎ የተነሳም የማይገዳቸው በእውነት ላይ የበላይ ከመሆንም ማትዛነፍ የሆነች አንዲት ጭፍራ ከኔ ኡማ አትጠፋም።»[5] እንዲህም ብለዋል፦ «አይሁዶች ለሰባ አንድ ጭፍሮች ተከፋፍለዋል፤ ክርስቲያኖችም ለሰባ ሁለት ጭፍሮች ተከፋፍለዋል፤ ይህ ሙስሊም ህዝብ ደግሞ ለሰባ ሦስት ጭፍሮች ይከፈላሉ። ሁሉም የእሳት ይሆኑና አንዷ ብቻ ትድናለች። ሱሓቦችም 'የአላህ መልዕክተኛ ሆይ! ይህች (የምትድነዋ) ማን ናት?' ብለው ጠየቁ እርሳቸውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) 'እኔና ባልደረቦቼ ባለንበት ሁኔታ የሆኑት ናቸው።' በማለት መለሱ።» [6] አጥብቀን ልንይዘው እና በታማኝነት ልንፀናበት ከተቃራኒውም ልንጠነቀቅ የሚገባን የሆነው ዓቂዳም ይኸው ነው። [5] ሙስሊም አል-ኢማራ በሚለው ርእስ ስር (1920)፣ አት-ቲርሚዚይ አል-ፊተን በሚለው ርእስ ስር (2229)፣ አቡ ዳውድ አል-ፊተን እና አል-ሙላሒም በሚለው ርእስ ስር (4252)፣ ኢብኑ ማጃህ አል-ፊተን (3952)፣ አሕመድ (5/279) ዘግበውታል። [6] ኢብኑ ማጃህ አል-ፊተን በሚለው ርእስ ስር (3992) ዘግበውታል
ከዚህ ትክክለኛ ዐቂዳ ያፈነገጡና በተቃራኒ ጎዳና የሚጓዙ ጭፍሮችን (በጥቂቱ) ለመጥቀስ ያህ፦
ጭፍሮቻቸው (አይነቶቻቸው)
ከዚህ ዓቂዳ ያፈነገጡና በሚቃረናት ጎዳና የሚጓዙ ሰዎች በዓይነትም ብዙ ጭፍሮች ናቸው። ከነሱ መካከል ግኡዝ አካላትን፣ ጣዖታትን፣ መላእክትን፣ ቅዱሳንን፣ አጋንንትን፣ ዛፎችን፣ ድንጋይንና ሌሎችንም አማልክት የሚያመልኩ አሉ። እነኝህ ለረሱል (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ዳዕዋ ምላሽም ያልሰጡ ጭራሽ ቁረይሾች ሌሎች የዓረብ ጭፍሮችም ከነብያችን ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ጋር እንደነበራቸው መስተጋብር የተቃረኗቸው ናቸው። ሙሽሪኮች ሙታኖቻቸው ጉዳያቸውን እንዲፈፅሙላቸው፣ ህሙማኖቻቸውንም እንዲፈውሱላቸው በጠላቶቻቸው ላይም ድል እንዲያጎናፀፏቸው መማፀን፤ እርድና ስለታቸውን የሚያቀርቡላቸው መሆናቸው ከስራዎቻቸው ይገኙበታል። ረሱል (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይሁን) ይህንን ድርጊታቸውን ባወገዙባቸውና አምልኮንም ለአላህ ብቻ ጥርት እንዲያደርጉ ባዘዟቸው ጊዜ እንግዳ አድርገው በመደነቅ እንዲህ ያሉ ናቸው: {«አማልክቶቹን አንድ አምላክ አደረጋቸውን? ይህ አስደናቂ ነገር ነው» (አሉ)።} [ሷድ፡ 5] (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) የሚያምነው እስኪያምንላቸውም ድረስ ወደ አላህ ከመጣራትና ከሽርክ ከማስጠንቀቅ፤ የጥሪያቸውን እውነታ ከማብራራትም አልተወገዱም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን)። ከዚያም ሰዎች በቡድን በቡድን እየሆኑ ወደ አላህ ዲን መትመማቸውን ቀጠሉ፤ የአላህም ዲን ተከታታይ ከሆነ የረሱል (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) ከዚያም የሶሓቦች -ረዲየሏሁ ዓንሁም- እና እነርሱን በቅንነት ከተከተሏቸው ተከታዮቻቸው ዳዕዋ በኋላ የአላህ ዲን በሌሎች ሃይማኖቶች ላይ መንሰራፋቱን ቀጠለ። ከዚያም ብዙዎችን ወደ ጃሂሊያው እምነት እስከመመለስ ድረስ ሁኔታዎች መቀያየር ጀመሩ፤ በብዙ ሰዎች ዘንድም ጅህልና እየጠና ሄደ። በጅህልናቸውም ምክንያትም በነብያቶችን በወልዮች በኩል ድንበር አልፈው እነርሱን መማፀን፣ ድረሱልኝ ማለት፣ የጭንቅ ጥሪያቸውን ወደነርሱ ማሰማት፣ እንዲሁም ከዚህም ውጭ የሆኑ የአምልኮ መገለጫዎችን አሳልፎ እስከመስጠት የሽርክ ደረጃም ደረሱ። የ ላ ኢላሃ ኢለሏህን ትርጉም የዓረብ ሙሽሪኮቹ የተረዱትን ያህል እንኳ ያልተረዱ ጃሂሎች ሆኑ። አላህ ይርዳንና!
ይኸው ሽርክ በጅህልና ጥናት እና ከነብያቶች ዘመን የራቅን በመሆናችን ምክንያት በዘመናችን ጭምር በሰዎች መካከል እየተስፋፋ ያለ ነገር ነው።
በዘመናችን ያሉ እንደውዥንብር የሚነሳው ጉዳይ የጥንቶቹ ዘንድ እንደውዥንብር ሲነሳ የነበረውና ነው። ከፊል የክህደት አመለካከቶችን ለመጥቀስ ያክል፦
የቀደምቶቻቸው ውዥንብር ሆኖ አሁን በዘመናችን ያሉ ዘንድም እንደ ውዥንብር አድርገው ከሚያነሱት መካከል እንዲህ የሚለው ቃላቸውን ይመስል፡- “እነዚህ ከአላህ ዘንድ አማላጆቻችን ናቸው፣ የምንገዛቸው ወደ አላህ እንዲያቃራቡን ብቻ ነው።" የሚለው አባባላቸውን መጥቀስ ይቻላል። አላህ ደሞ ይህንን ውዥንብራቸውን ውድቅ አድርጎባቸዋል። ከእርሱው ውጭ ማንም ይሁን ማንን ያመለከ በአላህ ያጋራና የካደ መሆኑንም ግልፅ አድርጎላቸዋልም። ልክ እንዲህ እንዳለን ማለት ነው፦ {ከአላህም ሌላ የማይጎዳቸውን የማይጠቅማቸውንም ይግገዛሉ። «እነዚህም አላህ ዘንድ አማላጆቻችን ናቸው» ይላሉ።} [ዩኑስ፡ 18] ጣራትና የበላይነት የተገባው አላህ እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ {«አላህን በሰማያትና በምድር ውስጥ የማያውቀው ነገር ኖሮ ትነግሩታላችሁን» በላቸው፡፡ ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ፤ ላቀም።} [ዩኑስ፡ 18] ጥራት ይገባውና በዚህ አንቀፅ ከእርሱ ውጭ ነብይንም ይሁን ወልይን ወይም ሌሎችንም ቢሆን ማምለክ ድርጊቱን የሚፈፅም ያሻውን ስም ቢሰጠውም ከታላቁ ሽርክ የሚመደብ ወንጀል መሆኑን ግልፅ አደረገ። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {እነዚያም ከእርሱ ሌላ (ጣዖታትን) ረዳቶች የያዙት «ወደ አላህ ማቃረብን እንዲያቀርቡን እንጅ ለሌላ አንገዛቸውም» (ይላሉ)።} [አዝ'ዙመር፡ 3] ጥራት የተገባው አላህ እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ {አላህ በዚያ እነርሱ በእርሱ በሚለያዩበት ነገር በመካከላቸው ይፈርዳል። አላህ እርሱ ውሸታም ከሓዲ የኾነን ሰው አያቀናም።} [አዝ'ዙመር፡ 3] በዚህም ጥራት የተገባው አላህ ሌሎችን በዱዓ፣ በፍርሃት፣ በተስፋና በመሳሰሉት የአምልኮ መገለጫዎች መማፀን በእርሱ መካድ መሆኑን ግልፅ አደረገ። ወደ አላህ መቃረብን ያቃርቡናል የሚለው ሙግታቸውንም ውሸትነቱን አጋለጠላቸው።
እንዲሁም መልዕክተኞች ሶለሏሁ ዓለይሂም ወሰለም ይዘውት የመጡትን ትክክለኛ ዓቂዳ የሚቃረኑና የክህደት እምነቶች ከሆኑት መካከልም የዘመናችን እምነተ ቢሶች የሚከተሉት የማርክሲዝምና ሌኒኒዝም እምነት ተከታዮች እና ሌሎች የእምነተ ቢስነትና የክህደት ሰባኪዎች ጥሪ ሁሉ ክህደት ነው። ይህንኑ አቋማቸውን ሲፈልጉ ሶሻሊዝም ይበሉት አልያም ኮሚዩኒዝም ከፈለጉም ባቲዝም ይበሉት ካሻቸውም ሌላ ስም ይስጡት የአቋማቸው ስረ መሰረቱ "አምላክ የሚባል ነገር የለም ህይወት የሚባለው ቁሳዊው አለም ብቻ ነው" እስካሉ ድረስ አቋማቸው የክህደት አቋም ነው። ከአቋማቸው መሰረቶች መካከል ከሞት በኋላ ትንሳኤ ያለ መሆኑን መካድ፣ ጀነት እና ጀሀነምን መካድ፣ በሁሉም ሀይማኖቶችም መካድ፣ መጽሐፋቸውን በጥልቅ የመረመረና ያሉበትን ተጨባጭ በሚገባ ያስተዋለ ሰው አቋማቸው እንዲሁ መሆኑን ያረጋግጣል። ይህ እምነት ደግሞ ሃይማኖቶችን በሙሉ የሚቃረን ለመሆኑ እና ሰዎቹንም በዱኒያም በአኺራም ለከፋ ፍፃሜ የሚዳርግ ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም።
እውነታውን ከሚቃረኑ እምነቶች መካከል አንዳንድ ባጢኒዮችና አንዳንድ ሱፊዮች ወሊይ የሚሏቸውን ሰዎች በማስተናበሩም ይሁን በአለሙ ክንውን ከአላህ ጋር ተጋሪነት እንዳላቸው የሚያምኑት ነገር ይገኝበታል። ሰዎቹንም "ቁጥብ"፣ "ዊትድ"፣ "ገውስ" እና ሌሎች ስያሜዎችንም እያፈለቁ አማልክቶቻቸውን የሚጠሩት ነገርም አለ። ይህ በአላህ ጌትነት የሚደረግ ሽርክ በመሆኑ ከዓረብ ጃሂሊዮች ሽርክም የከፋ ነው። ምክንያቱም የዓረብ ከሃዲያን በአላህ ጌትነት ምንም ተጋሪ እንደሌለው የሚያምኑ ሲሆኑ ሽርክ ሲፈፅሙ የነበሩትም አምልኮን አሳልፈው በመስጠት በኩል ነበር። ስለዚህም ነው ሽርኩን የሚፈፅሙት በተድላ ጊዜ የነበረው። በችግር ጊዜ ግን ጥራት የተገባው አላህ በሚከተለው አንቀፅም እንደነገረን አምልኳቸውን ለአላህ ጥርት ያደርጉ ነበር፦ {በመርከቦች ውስጥ በተሳፈሩ ጊዜም አላህን መገዛትን ለእርሱ ብቻ ያጠሩ ኾነው ይጠሩታል። ወደ የብስ (በማውጣት) ባዳናቸው ጊዜም ወዲያውኑ እነርሱ (ጣዖትን) ያጋራሉ።} [አል'ዓንከቡት፡ 65] የአላህን ጌትነት በተመለከተ ግን ጥራት ለተገባው አምላካችን አላህ ብቻ መሆኑን ያምኑ ነበር፤ ልክ እንዲህ እንዳለን፦ {ማን እንደፈጠራቸውም ብትጠይቃቸው «በእርግጥ አላህ ነው» ይላሉ።} [አዝ'ዙኽሩፍ፡ 87] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {«ከሰማይና ከምድር ሲሳይን የሚሰጣችሁ ማን ነው መስሚያዎችንና ማያዎችንስ የፈጠረ ማን ነው ከሙትም ሕያውን የሚያወጣ ከሕያውም ሙትን የሚያወጣስ ማን ነው ነገሩን ሁሉ የሚያስተናብርስ ማን ነው» በላቸው፡፡ «በእርግጥም አላህ ነው» ይሉሃል፡፡ «ታዲያ (ለምን ታጋራላችሁ) አትፈሩትምን» በላቸው።} [ዩኑስ፡ 31] በዚህ መልኩ የመጡ ቁርአናዊ ማስረጃዎች በርካት ናቸው።
የዘመናችን ሙሽሪኮች ከጥንታዊያኖቹ ምን የጨመሩት ነገር አለ?
የዘመናችን ሙሽሪኮች ከቀድሞዎቹ ሙሽሪኮች በሁለቱም በኩል የባሰባቸው ናቸው፡ አንደኛው፡- ከመካከላቸው አንዳንዶቹ በአላህ ጌትነት ሽርክ የሚፈጽሙ በመሆናቸው፤ ሁለተኛው ደግሞ፡- በግብፅ የሑሰይን እና የበደዊይ እና በሌሎችም ቀብር ላይ የሚያደርጉትን፣ በኤደን የዓይደሩስ ቀብር ላይ የሚያደርጉትን፣ በየመን የሃዲይ ቀብር ላይ የሚያደርጉትን፣ በሻም የኢብኑ ዓረቢይ ቀብር ላይ የሚያደርጉትን፣ በዒራቅ የሸይኽ ዓብዱልቀድር ጀይላኒይ ቀብር ላይ የሚያደርጉትን፣ ከነዚህም ውጭ በአለም አቀፍ ደረጃ የታወቁ ሰዎች መቃብር ዘንድ የሚያደርጉትን የአላህ ሓቅ አሳልፎ እስከመስጠት የደረሰ የብዙሃኑን ድንበር ማለፍ ፊት ለፊት ሁኔታቸውን የተመለከተና የታዘበ ሁሉ እንደሚያውቀው እነዚህኞቹ ሽርክ የሚፈፅሙት በምቾትም በችግርም ጊዜ ነው። በዛ ላይ ድርጊታቸውን እያወገዘ አላህ ነብዩንም ከእርሳቸው በፊት የነበሩት መልዕክተኞችም -የአላህ ሰላትና ሰላም በሁሉም ላይ ይስፈን- የላከበትን ተውሒድ የሚያብራራላቸው ጥቂቱ ብቻ ነው። ኢና ሊላሂ ወኢና ኢለይሂ ራጂዑን! ጥራት የተገባው አላህ ወደ ህሊናቸው እንዲመልሳቸው፣ በመካከላቸውም ቅን ዳዒዎችን እንዲያበዛላቸው፣ የሙስሊም መሪዎችንና ኡለማዎችንም ይህንን ሽርክ እንዲታገሉትና ሽርክንና መዳረሻዎቹንም ጭምር እንዲያጠፉ አላህ እንዲረዳቸው እርሱን እንጠይቀዋለን። እርሱ ሰሚው ቅርብ ነውና።
ትክክለኛውን ዓቂዳ ከሚቃረኑ እምነቶች መካከል የአላህ ስምና ባህሪያትን በተመለከተ ቢድዓ ያመጡ ሰዎች እንደ ጀህሚዮች፣ ሙዕተዚላዎች እና የአላህን ባህሪያት በመካድ፣ የምሉእነት ባህርያቶቹን ውድቅ በማድረግ፣ ጥራት የተገባው አላህን የባዶነት፣ የግኡዛንና ኢአእምሯዊ መገለጫ በሆኑ ባህርያት በመግለፅ ፈለጋቸውን የተከተሉ ሰዎች እምነት ይገኝበታል። እነዚህ ሰዎች ከሚሉት ሁሉ ጥራት የተገባው አምላካችን አላህ ላቀ፦ በዚህም ከፊል ባህርያቱን እየካዱ ከፊሉንም ለሚያፀድቁ አካላት ለምሳሌ እንደ አሽዓሪያዎች ያሉት ባፀደቁት ባህርያት ምክንያት ያወገዙትንም ባህርያት እንዲያፀድቁ የሚገደዱበት ይሆናል። ካልሆነ ግን በዚሁ እምነታቸው መለኮታዊንም አእምሯዊንም ማስረጃ የሚቃረኑ ይሆናሉ። አቋማቸውም እርስ በርሱ የተቃረነ መሆኑን ግልፅ የሚያደርጉበት ይሆናል። አህል አስ-ሱንና ወል-ጀማዓ ግን ጥራት ለተገባው አላህ እርሱም ነኝ ያለውን እንዲሁም መልዕክተኛው ሙሐመድ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) አላህን የገለፁበትን ስምና ባህርይ በተሟላ መልኩ መገለጫው መሆኑን ያፀድቃሉ፤ ፍጡራኑን ከመምሰልም ሆነ ራሱን የገለፀበትን ባህርይ ውድቅ ከማድረግ በመራቅ ከማይገባው ሁሉ እጅግ ጥርት ባለ መልኩ የጠራ መሆኑን ያምናሉ። በዚህም የተባሉትን ሳያዛቡም ውድቅ ሳያደርጉም አምነው፤ ሌሎቹ ካረፉበት እርስ በርስ መጣረስም ድነው የመጡትን ማስረጃዎች ሁሉ ተግባራዊ ማድረግ ቻሉ። ይህንንም ከላይ አብራርተናል። የመዳኛው፣ የዱኒያም የአኺራም ስኬታማነት ጎዳና፣ የዚህች ሕዝብ ቀደምት መሪዎችና ኢማሞች የተጓዙበት ቀጥተኛው መንገድ ይኸው ነው። የኋለኞቹ የሚስተካከሉበትም የመጀመሪያቸው በተስተካከሉበት ብቻ ነው። ማለትም ቁርኣንና ሱናን በመከተል ቁርአንና ሐዲሥን የሚቃረነውንም በመተው ነው።
የላቀው አላህን በብቸኝነት የማምለክ ግዴታነት እና አምላካችን አላህ በጠላቶቻችን ላይ ድል የሚያቀዳጅበት ምክንያቶች ማብራርያ፦
የትኛውም ሰው ላይ ያለበት ትልቁ ኋላፊነት እና ግዴታ የእርሱም፣ የሰማያትና የምድሩም እንዲሁም የታላቁ ዓርሽም አምላክ የሆነውን አላህን ማምለክ ነው። በተከበረው መጽሐፉም ላይ እንዲህ ባይ የሆነውን፡- {ጌታችሁ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀኖች ውስጥ የፈጠረ አላህ ነው፡፡ ከዚያም ከዐርሹ በላይ ከፍ አለ፡፡ (አላህ) ሌሊትን በቀን ፈጥኖ የሚፈልገው ሲሆን ይሸፍናል፡፡ ፀሐይንና ጨረቃንም ከዋክብትንም በትእዛዙ የተገሩ ሲሆኑ (ፈጠራቸው)፡፡ ንቁ! መፍጠርና ማዘዝ የእርሱ ብቻ ነው፡፡ የዓለማት ጌታ አላህ (ክብሩ) ላቀ።} [አል'አዕራፍ፡ 54] ጥራት የተገባው አምላካችን አላህ በሌላኛው አንቀፅ ሁለቱን ከባዶች (ሰውና ጂኒን) እርሱን ሊያመልኩት የፈጠራቸው መሆኑን እንዲህ በማለት ተናግሯል፦ {ጂኒንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም።] [አዝ-ዛሪያት፡ 56] ይህ ሁለቱ ከባባዶች (ሰውና ጂኒን) የተፈጠሩበት አላማ አምልኮን በየትኛውም ዓይነቱ ማለትም ሶላት፣ ፆም፣ ዘካ፣ ሐጅ፣ ሩኩዕም ሱጁድም፣ በካዕባ ዙርያ ጠዋፍ ማድረግ፣ እርድ ማቅረብ፣ ስለት፣ ስጋትና ተስፋ ማሳደር፣ "ኢስቲዓናህ" እና "ኢስቲጋሣ" (በከባድ ጭንቅ ጊዜ ድረስልኝ ብሎ መማፀን)፣ ከክፋት የመጠበቅ እና መሰል የዱዓእ ዓይነቶችና የመሳሰሉትን ዒባዳዎች ሁሉ ለአምላካችን አላህ ብቻ አድርገን እንድናመልከው ነው። በዚህም ጥራት የተገባው አላህ በተከበረው ቁርአን እና በታማኙ ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) አንደበት ያዘዘንን ነገር ሁሉ መታዘዝ፤ የከለከለንን መከልከልም በዚሁ የሚጠቃለል ነው። ጥራት የተገባው አምላካችን አላህ የሰው ልጆችንና አጋንንትን በሙሉ ይህንን የተፈጠሩበትን አላማ ማለትም እርሱን በብቸኝነት እንዲያመልኩት አዟቸዋል። ይሀንኑ አምልኮ እንዲያብራሩና ወደ እርሱም ጥሪ እንዲያደርጉ በኢኽላስም እንዲያዙ ነው መልዕክተኞቹንም ሁሉ የላከው፣ መጻሕፍቱንም ያወረደው። ልክ እንዲህ እንዳለን፡- {እናንተ ሰዎች ሆይ! የፈጠራችሁን እነዚያንም ከናንተ በፊት የነበሩትን (የፈጠረውን) ጌታችሁን ተገዙ፤ (ቅጣትን) ልትጠነቀቁ ይከጀላልና።} [አል-በቀራህ፡ 21] አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ጌታህም (እንዲህ ሲል) አዘዘ፡- እርሱን እንጂ ሌላን አትገዙ። በወላጆቻችሁም መልካምን ሥሩ።} [አል-ኢስራእ፡ 23] በዚህ አንቀጽ ውስጥ የተወሳው ወሰነ የሚለው ቃል ትርጉም አዘዘ አደራውን አስተላለፈ ማለት ነው። የበላይ የሆነው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ አጥሪዎች፣ ቀጥተኞች ኾነው ሊግገዙት፣ ሶላትንም አስተካክለው ሊሰግዱ ዘካንም ሊሰጡ እንጅ ያልታዘዙ ሲኾኑ (ተለያዩ)፡፡ ይህም የቀጥተኛይቱ (ሃይማኖት) ድንጋጌ ነው።} [አል-በይናህ፡ 5] የዚህን ዓይነት መልዕክት ያዘሉ በቁርአን ውስጥ ያሉት ጥቅሶች በርካታ ናቸው። አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህም ብሏል፦ {መልክተኛውም የሰጣችሁን (ማንኛውንም) ነገር ያዙት፡፡ ከእርሱም የከለከላችሁን ነገር ተከልከሉ፡፡ አላህንም ፍሩ፡፡ አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና።} [አል-ሐሽር፡ 7] ጥራት የተገባው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ መልክተኛውንና ከእናንተም የስልጣን ባለቤቶችን ታዘዙ፡፡ በማንኛውም ነገር ብትከራከሩ በአላህና በመጨረሻው ቀን የምታምኑ ብትኾኑ (የተከራከራችሁበትን ነገር) ወደ አላህና ወደ መልክተኛው መልሱት፡፡ ይህ የተሻለ መጨረሻውም ያማረ ነው።} [አን-ኒሳእ፡ 59] አሸናፊና ኋያሉ አላህ እንዲህ ብሏል፦ {መልክተኛውን የሚታዘዝ ሰው በእርግጥ አላህን ታዘዘ።} [አን-ኒሳእ፡ 80]
ጥራት ይገባውና እንዲህምይላል፦ {በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ «አላህን ተገዙ፤ ጣዖትንም ራቁ» በማለት መልክተኛን በእርግጥ ልከናል።} [አን-ነሕል፡ 36] ጥራት ይገባውና እንዲህም ብሏል፦ {ከአንተ በፊትም እነሆ ከእኔ ሌላ አምላክ የለምና ተገዙኝ በማለት ወደርሱ የምናወርድለት ቢኾን እንጅ ከመልክተኛ አንድንም አልላክንም።} [አል-አንቢያእ፡ 25] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {አሊፍ ላም ራ፤ (ይህ ቁርኣን) አንቀጾቹ በጥንካሬ የተሰካኩ ከዚያም የተዘረዘሩ የሆነ መጽሐፍ ነው፡፡ ጥበበኛ ውስጠ ዐዋቂ ከሆነው ዘንድ (የተወረደ) ነው።} {(እንዲህ በላቸው)፡- «አላህን እንጂ ሌላን አትገዙ፡፡ እኔ ለእናንተ ከርሱ (የተላክሁ) አስፈራሪና አብሳሪ ነ።»} [ሁድ: 1-2]
እነዚህ ግልፅ አንቀፆች እና በአምላካዊ መጻሕፍት ይህንኑ ትርጉም የሚያንፀባርቁ ቃላት ሁሉ የሚያመላክቱት በአምልኮ አላህን ብቻ ነጥለን መገዛታችን ምን ያህል አስገዳጅ መሆኑን እና ይህም የሃይማኖቱ መሰረት መሆኑን ነው። በተጨማሪም አጋንንትና ሰዎች የተፈጠሩበት መልዕክተኞችም የተላኩበትና አምላካዊ መጻህፍቶችም የወረዱበት ጥበብ ይኸው መሆኑ ነው። በመሆኑም ማንኛውም ለኋላፊነት የደረሰ ሁሉ ይህንኑ ጉዳይ አፅንኦት ሊሰጠው ይበልጥ ሊገነዘበውም እንዲሁም ራሳቸውን ወደ እስልምና ከሚያስጠጉ ሰዎች ብዙዎቹ ያረፉበት የሆነው ከተቃራኒው ማለትም በነብያቶችና በሷሊሖች ድንበር ማለፍን፣ በመቃብሮቻቸውም ላይ መገንባትን፣ ያንኑ መቃብሮቻቸውንም የአምልኮ ቦታ ዶሪሕ አድርጎ መያዝን፣ በከባድም ይሁን በቀላል ጉዳይ በዱዓእ እነርሱን መማፀንን፣ እነርሱን መጠጊያ አድርጎ መያዝን፣ ጉዳይ እንዲፈፅሙ ህሙማን እንዲፈውሱና ከጭንቅ እንዲገላግሉ ወይም በጠላት ላይ ድልን እንዲያቀዳጁ ወደ እነርሱ መከጀልን ከመሳሰሉት የሽርክ እና የክህደት ዓይነቶችን ሁሉ መራቅና መጠንቀቁ ግዴታ ነው። የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በቁርአን ከተጠቀሰው በሚገጥም መልኩ በቡኻሪይና ሙስሊም ከሙዓዝ ረዲየሏሁ ዓንሁ በተላለፈ ሓዲሥ እንዲህ ማለታቸው ተረጋግጧል፦ "አላህ በባሮቹ ላይ ያለውን መብት ባርያዎችም በአላህ ላይ ያላቸውን መብት ታውቃለህን?" አሉ። እኔም፡- "አላህና መልዕክተኛው ይበልጥ ያውቃሉ" አልኳቸው። ነብዩም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) "አላህ በባሮቹ ላይ ያለው መብት እርሱን በብቸኝነት ሊገዙት እና በርሱም ምንንም ላያጋሩ ነው። የአላህ ባርያዎች በአላህ ላይ ያላቸው መብት ደግሞ በእርሱ ምንንም ያላጋሩትን ላይቀጣቸው ነው።” (7) በሶሒህ አል ቡኻሪይ ኢብኑ መስዑድ ባስተላለፉት ሓዲሥ - ረዲየሏሁ ዓንሁ - ነብዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) እንዲህ ብለዋል፡- «ከአላህ ውጭ ሌላን ሲመፀን የሞተ ሰው እሳት ገባ።» [8] ሙስሊምም ከጃቢር (ረዲየላሁ ዐንሁ) በዘገቡት ሶሒሕ ሐዲሥ ነቢዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) እንዲህ ብለዋል፡- «ከአላህ ምንንም ሳያጋራ የሞተ ሰው ጀነት ገባ። ከአላህ ጋር እያጋራ የሞተ ደግሞ ጀሀነም ገባ።» ይህንን በተመለከተ የመጡ ሐዲሦች በርካታ ናቸው። ጉዳዩም ከታላላቅ ዋና ዋና ጉዳዮች አንዱ ነው። አላህም ነብዩ ሙሐመድን (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) የላካቸው ሰዎች አላህን በብቸኝነት እንዲያመልኩ ጥሪ ሊያደርጉ እና ከሽርክም እንዲያስጠነቅቁ ነው። በመሆኑም እርሳቸውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን)ተልዕኳቸውን በሚገባ እጅግ በተሟላ መልኩ የሚወጡ ነበሩ። በዚህ ጥሪያቸው እጅግ መንገላታትም ደረሰባቸው፤ እሳቸውም (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈን) በትዕግስ ተወጡት። የሳቸው ባልደረቦችም - አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና - እንዲሁ አላህ ከዓረብ ባሕረ ገብ መሬት ጣዖታትን እስኪያስወግድ ድረስ አብረዋቸው በትዕግስት ፅናት በዳዕዋው ዘለቁ። ከዚያም ሰዎች በቡድን በቡድን እየሆኑ ወደ አላህ ሃይማኖት መግባታቸው እውን ሆነ፤ በካዕባ ዙሪያና ውስጥ ያሉት ጣዖታትም መወገዳቸው እውን ሆነ፤ አል - ላት፣ አል-ዑዛ እና መናት የተባሉት ጣኦታትም ጭምር ፈራረሱ፤ በአረብ ጎሣዎች የነበሩት ጣዖታት በሙሉ መሰባበርም ተቻለ፤ ያሏቸው ግኡዝ አማልክትም ብትንትናቸው ወጣ፤ የላቀው አላህ ቃልም ከፍ ብሎ እስልምናም በአረብ ምድር የበላይ ሆነ። ከዚያም ሙስሊሞች በዳዕዋና በጂሃድ ከዐረቢያ ደሴት ወጥተው ከባሮቹ መካከል አላህ ስኬትን ላደላቸው ሰዎች በዳዕዋ መምራት ቻሉ። አላህም ሐቅንና ፍትህን በእነሱ አማካኝነት በአብዛኛዎቹ የአለም ክፍሎች አስፋፋ፤ በዚህም እነርሱ የሐቅና የቀናነት መሪ ኢማም ፤ የፍትህ እና የመስተካከልም ዳዒዎች መሆንን ታደሉ። ኮቴያቸውን በቅንነት ተከትለው የሄዱ ሰዎችም እንዲሁ የቅንነት መሪዎች ሆነው የአላህን ሀይማኖት የሚያስፋፉ ሆኑ፤ ሰዎችንም አላህን በብቸኝነት ወደማለክና በአላህም መንገድ ለመታገል የወቃሽን ወቀሳ ሳይፈሩ በገንዘባቸውም በነፍሳቸውም የሚታገሉ ሙጃሂዶች ሆኑ። አላህም አበረታቸው፤ አጠነከራቸውም በሚጋፈጣቸው ሁሉ ላይም የበላይነትን አጎናፀፋቸው፤ በተከታዩ አንቀፅ የገባላቸውን ቃልኪዳንም ሞላላቸው። {እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን (ሃይማኖቱን) ብትረዱ፤ ይረዳችኋል፡፡ ጫማዎቻችሁንም ያደላድላል።} [ሙሐመድ: 7] ተከታዩም የአሸናፊውና ኋያሉ አላህ ቃል፦ {አላህም ሃይማኖቱን የሚረዳውን ሰው በእርግጥ ይረዳዋል፡፡ አላህ ብርቱ አሸናፊ ነውና።} {(እነርሱም) እነዚያ በምድር ላይ ብናስመቻቸው ሶላትን እንደሚገባ የሚያስተካክሉ፣ ዘካንም የሚሰጡ፣ በደግ ነገርም የሚያዝዙ፣ ከመጥፎ ነገርም የሚከለክሉ ናቸው፡፡ የነገሮቹም ሁሉ መጨረሻ ወደ አላህ ነው።} [አል-ሐጅ፡ 40-41] ይህ ሁሉ ካለፈ በኃላ ታዲያ ሰዎች ተቀየሩ፤ መለያየትና በጂሃድ ጉዳይ መሳነፍን አምጥተው ድሎትና ስሜትን ተከታይነት አስቀደሙ፤ በሰዎቹ ላይ አላህ ከጠበቃቸው በቀር የተወገዙ ነገራቶች ይታዩባቸው ጀመር፤ አላህም ሁኔታቸውን ቀያየረባቸው፤ ጠላቶቻቸውንም በእነርሱ ላይ ሾመባቸው። ለሰሩት ምንዳቸው እንጅ ጌታህ ባሮቹን የሚበድል ሆኖ አይደለም። የላቀው አላህ እንዲህ ብሏል፦ {ይህ (ቅጣት) አላህ በሕዝቦች ላይ የለገሰውን ጸጋ በነፍሶቻቸው ያለውን ነገር እስከሚለውጡ ድረስ የማይለውጥ በመኾኑ ምክንያት ነው፡፡ አላህም ሰሚ ዐዋቂ ነው።} [አል-አንፋል፡ 53] ሁሉም ሙስሊሞች፣ መንግስታት እና ህዝቦች ወደ ኃያሉ አምላክ መመለስ፣ እርሱን በብቸኝነት ወደ ማምለክ፣ ላሳለፉት ስህተታቸውና ኃጢአታቸው ወደ እርሱ መጸጸት እና አላህ ያዘዛቸውን ግዴታዎች በመወጣት ወደ እርሱ መመለስ የሁሉም ግዴታ ነው። አላህ በነርሱ ላይ እርም ያደረገውንም ነገር መራቅ እና በመካከላቸው መመካከርን በማስፈንና በመተጋገዝ ወደ አላህ ተመላሽ መሆን አለባቸው። [7] አል-ቡኻሪይ "አል‐ኢስቲእዛን" በሚለው ርእስ ስር (5912)፣ ሙስሊም "አል-ኢማን" በሚለው ርእስ ስር (30)፣ ቲርሚዚይ "አል-ኢማን" በሚለው ርእስ ስር (2643)፣ ኢብኑ ማጃህ "አዝ-ዙህድ" በሚለው ርእስ ስር (4296)፣ እንዲሁም አሕመድ (5/238) ዘግበውታል። [8] አል-ቡኻሪይ ተፍሲሩል ቁርአን በሚለው ርእስ ስር (4227)፣ ሙስሊም አል-ኢማን በሚለው ርእስ ስር (92)፣ እንዲሁም አሕመድ (1/374) ዘግበውታል። [9] አል-ቡኻሪይ አል-ዒልም በሚለው ርእስ ስር (129)፣ ሙስሊም አል-ኢማን በሚለው ርእስ ስር (32)፣ እንዲሁም አሕመድ (3/157) ዘግበውታል።
በዚህ ረገድ እጅግ አሳሳቢ ከሆኑ ጉዳዮች መካከል ሸሪዓዊ የሆነው "ሐድ" መዘርጋት እና በሰዎች መካከል የሸሪዓን ዳኝነት በሁሉም ነገር ላይ ማስፈን እንዲሁም ወደርሱ እየተፋረዱ ከአላህ ድንጋጌ ጋር የሚጋጩ ሰው ሰራሽ ህጎችን ማስወገድ ነው። በሰው ሰራሽ ህጎች አለመዳኘትና መላው ህዝብ በሸሪዓ እንዲተዳደር ማስገደድ ይገባል። ልክ በዑለሞቹ ላይም ሰዎች ዲናቸውን እንዲገነዘቡና ኢስላማዊ እሴቶችንም ማሰራጨት ላይ ማበረታታት፤ በእውነት ላይም አደራ መባባልና በዛ ላይ በትዕግስት ፀንቶ በመልካም እያዘዙ ከመጥፎም እየከለከሉ ህዝቡን በእውቀት መንከባከብ እንደሚገባቸው ሁሉ ማለት ነው። አስተዳዳሪዎቹንም እንዲሁ የአላህን ሸሪዓ እንዲተገብሩ ማበረታታት ይገባቸዋል። ልክ አውዳሚ የሆኑ ርዕዮተ አለሞችንም እንደ ሶሻሊዝም፣ ባቲዝም፣ ብሔርተኝነትና ሌሎችም ከሸሪዓ ጋር የሚቃረኑ መርሆችና አንጃዎችን ሁሉ መዋጋትም ይገባል። በዚህም የላቀው አላህ ከሙስሊሞች የተበላሸውን ያስተካክለዋል፣ የጠፋውንም ይመልሰዋል፣ አፈንጋጩንም ያስተካክለዋል። ከዚያም የድሮ ግርማቸውን መልሶላቸው በጠላቶቻቸውም ላይ ድልን ያቀዳጃቸዋል። በምድር ላይም ያመቻቻቸዋል፤ ይበልጥ እውነት ተናጋሪው አምላካችን አላህ እንዲህ በማለት እንደተናገረው፦ {ምእመኖቹንም መርዳት በእኛ ላይ ተገቢ ሆነ።} [አር-ሩም፡ 47] የበላይ የሆነው አላህ እንዲህም ብሏል፦ {አላህ እነዚያን ከእናንተ ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን እነዚያን ከእነሱ በፊት የነበሩትን እንደተካ በምድር ለይ በእርግጥ ሊተካቸው፣ ለእነሱም ያንን የወደደላቸውን ሃይማኖታቸውን ሊያደላድልላቸው፣ ከፍርሃታቸውም በኋላ ጸጥታን ሊለውጥላቸው ተስፋን ቃል ሰጥቷቸዋል፡፡ በእኔ ምንንም የማያጋሩ ሆነው ይግገዙኛል፡፡ ከዚያም በኋላ የካደ ሰው እነዚያ እነርሱ አመጸኞች ናቸው።} [አን-ኑር፡ 55] ጥራት ይገባውና እንዲህ ይላል፦ {እኛ መልክተኞቻችንን፣ እነዚያንም ያመኑትን በቅርቢቱ ሕይወት ምስክሮችም በሚቆሙበት ቀን በእርግጥ እንረዳለን።} [ጋፊር: 51] {በደለኞችን ምክንያታቸው በማይጠቅማቸው ቀን (እንረዳለን)፡፡ ለእነርሱም ርግማን አልላቸው፡፡ ለእነርሱም መጥፎ አገር አልላቸው።} [ጋፊር: 52]
የሙስሊም አስተዳዳሪዎችንና ምእመናኑንም እንዲመራልን፣ የሀይማኖቱን ግንዛቤም እንዲቸራቸው፣ ቃላቸውንም በተቅዋ አንድ አይነት እንዲያደርግላቸው፣ ሁሉንም ቀጥተኛውን መንገድ እንዲመራቸው፣ በነርሱ አማካኝነትም ሐቅን ረድቶ ሀሰትን እንዲያዘቅጥልን፣ ሁላቸውንም በመልካምነትና አላህን በመፍራት መተጋገዝ ላይ በእውነትና በትዕግስትም አደራ መባባል ላይ ተውፊቁን እንዲገጥማቸው የምንማፀነው አላህን ነው። እነሆ እርሱ የጉዳዩ ባለቤትና ባለችሎታውም እርሱው ነው። የአላህ ሰላትና ሰላም የአላህ ባርያና መልዕክተኛው በሆኑት፣ ከፍጡራኑም የተመረጡ በሆኑት፣ ነብያችን መሪያችን አለቃችንም ነብዩ ሙሐመድ ቢን ዐብዲላህ በቤተሰቦቻቸውና በባልደረቦቻቸውም የሳቸውን ቀን ፈለግ በተከተለም ላይ ሁሉ ይስፈን። ወሰላሙ ዐለይኩም ወረሕመቱሏሂ ወበረካቱህ።